ሁለተኛ ዜና መዋዕል 28:1-27

  • አካዝ በይሁዳ ላይ ነገሠ (1-4)

  • አካዝ በሶርያና በእስራኤል ድል ተመታ (5-8)

  • ኦዴድ እስራኤላውያንን አስጠነቀቃቸው (9-15)

  • ይሖዋ ይሁዳን አዋረደ (16-19)

  • አካዝ ጣዖት አመለከ፤ በመጨረሻም ሞተ (20-27)

28  አካዝ+ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 20 ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌምም ሆኖ ለ16 ዓመት ገዛ። አባቱ ዳዊት እንዳደረገው በይሖዋ ፊት ትክክል የሆነውን ነገር አላደረገም።+  ከዚህ ይልቅ የእስራኤልን ነገሥታት መንገድ ተከተለ፤+ አልፎ ተርፎም ከብረት የተሠሩ የባአል ሐውልቶችን* ሠራ።+  በተጨማሪም በሂኖም ልጅ ሸለቆ* የሚጨስ መሥዋዕት ያቀረበ ከመሆኑም ሌላ ይሖዋ ከእስራኤላውያን ፊት ያባረራቸው ብሔራት ይፈጽሙ የነበረውን አስጸያፊ ድርጊት በመከተል+ ወንዶች ልጆቹን በእሳት አቃጠለ።+  ደግሞም ከፍ ባሉት የማምለኪያ ቦታዎች፣ በኮረብቶቹና በእያንዳንዱ የለመለመ ዛፍ ሥር+ ይሠዋ እንዲሁም የሚጨስ መሥዋዕት ያቀርብ ነበር።+  ስለዚህ አምላኩ ይሖዋ በሶርያ ንጉሥ+ እጅ አሳልፎ ሰጠው፤ እነሱም ድል አደረጉት፤ ከሕዝቡም መካከል ብዙዎቹን ማርከው ወደ ደማስቆ+ ወሰዱ። ደግሞም አምላክ በእስራኤል ንጉሥ እጅ አሳልፎ ሰጠው፤ እሱም ከባድ እልቂት አደረሰበት።  የረማልያህ ልጅ ፋቁሄ+ በይሁዳ 120,000 ሰዎችን በአንድ ቀን የገደለ ሲሆን ሁሉም ደፋር ተዋጊዎች ነበሩ፤ ይህም የሆነው የአባቶቻቸውን አምላክ ይሖዋን በመተዋቸው ነው።+  ዚክሪ የተባለው ኤፍሬማዊ ተዋጊም የንጉሡን ልጅ ማአሴያህን፣ የቤተ መንግሥቱን* አዛዥ አዝሪቃምንና የንጉሡ ምክትል የሆነውን ሕልቃናን ገደለ።  በተጨማሪም እስራኤላውያን ከአይሁዳውያን ወገኖቻቸው መካከል 200,000 ሴቶችን፣ ወንዶች ልጆችንና ሴቶች ልጆችን ማረኩ፤ እጅግ ብዙ ምርኮም ወሰዱ፤ የበዘበዙትንም ወደ ሰማርያ+ ይዘው ሄዱ።  ይሁንና በዚያ ኦዴድ የተባለ የይሖዋ ነቢይ ነበር። እሱም ወደ ሰማርያ እየመጣ የነበረውን ሠራዊት ለመገናኘት ወጥቶ እንዲህ አላቸው፦ “እነሆ፣ የአባቶቻችሁ አምላክ ይሖዋ የይሁዳ ሰዎችን በእጃችሁ አሳልፎ የሰጣችሁ በእነሱ ላይ ስለተቆጣ ነው፤+ እናንተም እስከ ሰማይ በሚደርስ ታላቅ ቁጣ ፈጃችኋቸው። 10  አሁንም የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን ሕዝብ ለራሳችሁ ወንድ አገልጋዮችና ሴት አገልጋዮች ልታደርጓቸው ታስባላችሁ።+ እናንተስ ብትሆኑ በአምላካችሁ በይሖዋ ፊት ተጠያቂ አይደላችሁም? 11  እንግዲህ ስሙኝ፤ የይሖዋ ቁጣ በእናንተ ላይ ስለነደደ ከወንድሞቻችሁ መካከል የማረካችኋቸውን ሰዎች መልሱ።” 12  በዚህ ጊዜ ከኤፍሬማውያን አለቆች መካከል አንዳንድ ሰዎች ይኸውም የየሆሃናን ልጅ አዛርያስ፣ የመሺሌሞት ልጅ ቤራክያህ፣ የሻሉም ልጅ የሂዝቂያ እና የሃድላይ ልጅ አሜሳይ ከጦርነቱ የተመለሱትን ሰዎች በመቃወም 13  እንዲህ አሏቸው፦ “ምርኮኞቹን ወደዚህ አታምጧቸው፤ በይሖዋ ፊት በደለኞች ታደርጉናላችሁ። በደላችን ብዙ ሆኖ ሳለ፣ በኃጢአታችንና በበደላችን ላይ ልትጨምሩብን ታስባላችሁ? በእስራኤል ላይ ቁጣ ነዷልና።” 14  ስለዚህ የታጠቁት ወታደሮች ምርኮኞቹንና የበዘበዙትን ነገር+ ለመኳንንቱና ለመላው ጉባኤ አስረከቡ። 15  ከዚያም በስም ተጠቅሰው ኃላፊነት የተሰጣቸው ሰዎች ተነስተው ምርኮኞቹን ተረከቡ፤ ራቁታቸውን ለነበሩት ሁሉ ከምርኮው ልብስ ሰጧቸው። ልብስ አለበሷቸው፤ እንዲሁም ጫማ ሰጧቸው፤ የሚበሉትና የሚጠጡት ነገር አቀረቡላቸው፤ ለገላቸውም ዘይት ሰጧቸው። ከዚህም ሌላ የደከሙትን በአህያ ላይ አስቀምጠው ወንድሞቻቸው ወደሚገኙባት የዘንባባ ዛፎች ከተማ ወደሆነችው ወደ ኢያሪኮ ወሰዷቸው። ከዚያም ወደ ሰማርያ ተመለሱ። 16  በዚህ ጊዜ ንጉሥ አካዝ፣ የአሦር ነገሥታት እንዲረዱት ጠየቀ።+ 17  ኤዶማውያንም በድጋሚ መጥተው ይሁዳን በመውረር ጥቃት ሰነዘሩ፤ ምርኮኞችንም ወሰዱ። 18  ፍልስጤማውያን+ ደግሞ በይሁዳ የሚገኙትን የሸፌላንና+ የኔጌብን ከተሞች ወረሩ፤ ቤትሼሜሽን፣+ አይሎንን፣+ ገዴሮትን፣ ሶኮንና በሥሯ* ያሉትን ከተሞች፣ ቲምናንና+ በሥሯ ያሉትን ከተሞች እንዲሁም ጊምዞንና በሥሯ ያሉትን ከተሞች ያዙ፤ በዚያም ተቀመጡ። 19  ይሖዋ በእስራኤል ንጉሥ በአካዝ የተነሳ ይሁዳን አዋረደ፤ ምክንያቱም አካዝ የይሁዳን ሰዎች መረን ለቆ ነበር፤ ይህም ንጉሡ ለይሖዋ የነበረውን ታማኝነት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲያጓድል አደረገው። 20  በመጨረሻም የአሦር ንጉሥ ቴልጌልቴልፌልሶር+ እሱን ከመርዳት ይልቅ በእሱ ላይ ዘምቶ አስጨነቀው።+ 21  አካዝ የይሖዋን ቤት እንዲሁም የንጉሡን ቤትና*+ የመኳንንቱን ቤቶች አራቁቶ ለአሦር ንጉሥ ስጦታ አበረከተ፤ ይህ ግን ምንም የፈየደለት ነገር የለም። 22  ንጉሥ አካዝ በተጨነቀ ጊዜ በይሖዋ ላይ ታማኝነት የጎደለው ድርጊት መፈጸሙን ይበልጥ ገፋበት። 23  እሱም “የሶርያ ነገሥታት አማልክት እነሱን ስለሚረዷቸው፣ እኔንም እንዲረዱኝ መሥዋዕት አቀርብላቸዋለሁ”+ በማለት ላሸነፉት+ የደማስቆ አማልክት+ መሥዋዕት ያቀርብ ጀመር። ይሁንና እነሱ፣ ለእሱም ሆነ ለመላው እስራኤል እንቅፋት ሆኑ። 24  በተጨማሪም አካዝ የእውነተኛውን አምላክ ቤት ዕቃዎች ሰበሰበ፤ ከዚያም የእውነተኛውን አምላክ ቤት ዕቃዎች ሰባበረ፤+ የይሖዋን ቤት በሮች ዘጋ፤+ በኢየሩሳሌምም በየመንገዱ ማዕዘን ላይ መሠዊያዎችን ለራሱ ሠራ። 25  በይሁዳ ከተሞች ሁሉ ለሌሎች አማልክት የሚጨስ መሥዋዕት የሚቀርቡባቸው ከፍ ያሉ የማምለኪያ ቦታዎችን ሠራ፤+ በዚህም የአባቶቹን አምላክ ይሖዋን አስቆጣ። 26  የቀረው ታሪክ፣ ከመጀመሪያ አንስቶ እስከ መጨረሻ ድረስ ያከናወነው ነገር ሁሉ በይሁዳና በእስራኤል ነገሥታት መጽሐፍ ውስጥ ተጽፏል።+ 27  በመጨረሻም አካዝ ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፤ እነሱም በኢየሩሳሌም ከተማ ቀበሩት፤ ሆኖም የቀበሩት በእስራኤል ነገሥታት የመቃብር ስፍራ አልነበረም።+ በእሱም ምትክ ልጁ ሕዝቅያስ ነገሠ።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ቀልጠው የተሠሩ የባአል ሐውልቶችን።”
የቃላት መፍቻው ላይ “ገሃነም” የሚለውን ተመልከት።
ቃል በቃል “የቤቱን።”
ወይም “በዙሪያዋ።”
ወይም “ቤተ መንግሥቱንና።”