በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ተስፋ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

ተስፋ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

ተስፋ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

ቀደም ባለው ርዕስ መጀመሪያ ላይ የተጠቀሰው ዳንኤል የተባለው የካንሰር ሕመምተኛ ተስፋ ባይቆርጥ ኖሮስ? ሕመሙን ተቋቁሞ እስከዛሬ ድረስ በሕይወት መኖር ይችል ነበር? ተስፋ ከፍተኛ ጥቅም እንዳለው ሽንጣቸውን ገትረው የሚሟገቱ ሰዎች እንኳ እንዲህ ብለው ለመናገር አይደፍሩም። ዋናው ቁም ነገር ያለው እዚህ ላይ ነው። ተስፋ ከመጠን በላይ የተጋነነ ግምት ሊሰጠው አይገባም። ተስፋ ለሁሉም ችግሮች መፍትሔ አይደለም።

ዶክተር ናታን ቸርኔ ሲቢኤስ ኒውስ ከተባለ የሬዲዮና የቴሌቪዥን ማሰራጫ ጣቢያ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ በጠና በታመሙ በሽተኞች ረገድ ተስፋ የሚጫወተው ሚና ተጋንኖ መቅረብ እንደማይኖርበት ሲያስጠነቅቁ “የሚፈለገውን ያህል አላሰላሰለችም እንዲሁም ብሩሕ አመለካከት አልያዘችም በማለት ሚስቶቻቸውን የሚቆጡ ባሎች አጋጥመውናል” ብለዋል። አክለውም ሲናገሩ “እንዲህ ያለው አስተሳሰብ አንድ ሰው የዕጢውን ወይም የካንሰሩን እድገት መቆጣጠር ይችላል የሚል የተሳሳተ እምነት ስለፈጠረ ታማሚዎቹ በሽታው ከባሰባቸው የዕጢውን እድገት ለመቆጣጠር ተገቢውን ጥረት አላደረጉም ተብሎ ይታሰባል፤ ይህ ደግሞ ምክንያታዊነት የጎደለው ነው” ብለዋል።

እንደ እውነቱ ከሆነ ለሞት በሚዳርግ በሽታ የተያዙ ሰዎች እልህ አስጨራሽ በሆነ ከባድ ትግል ላይ ናቸው። ስለሆነም የሚወዷቸው ሰዎች ይህ ከባድ ቀንበር ሳያንስ በእነርሱ ላይ የጥፋተኝነት ስሜት መጨመር እንደማይፈልጉ የታወቀ ነው። ታዲያ ተስፋ ምንም ዋጋ የለውም ብለን መደምደም ይኖርብናል?

በጭራሽ። ለምሳሌ ያህል ከላይ የጠቀስናቸው ዶክተር ሕመምንና የሕመም ምልክቶችን ማስታገሥ ስለሚቻልበት መንገድ ልዩ ሥልጠና ወስደዋል። ይህ ዓይነቱ ሕክምና በሽታን በማዳን ወይም ዕድሜን በማራዘም ላይ ሳይሆን በሽተኛው በሕይወት እስከኖረ ድረስ ምቾት እንዲሰማውና ደስተኛ እንዲሆን በማድረግ ላይ ያተኮረ ነው። በዚህ መስክ ላይ የተሰማሩ ዶክተሮች በጠና የታመሙ በሽተኞችን እንኳ ሳይቀር ደስተኛ የሚደርጉ የሕክምና ዓይነቶች ጠቃሚ መሆናቸውን በጥብቅ ያምናሉ። ተስፋ ይህንና ከዚህም ያለፈ ነገር ሊያደርግ እንደሚችል የሚያሳዩ በርካታ ማስረጃዎች አሉ።

ተስፋ ያለው ጠቀሜታ

ዶክተር ጊፎርድ ጆንዝ የተባሉ አንድ የሕክምና መጽሔት አዘጋጅ “ተስፋ ፍቱን መድኃኒት ነው” በማለት ይናገራሉ። እኚህ ሰው በሞት አፋፍ ላይ ለሚገኙ በሽተኞች ስሜታዊ ድጋፍ ማድረግ ያለውን ጠቀሜታ ለማወቅ የተደረጉ የተለያዩ ጥናቶችን መርምረዋል። እንዲህ ዓይነቱ ድጋፍ ተስፋን ለማለምለምና አዎንታዊ አመለካከት ለመያዝ ይረዳል ተብሎ ይታሰባል። በ1989 የተደረገ አንድ ጥናት እንዲህ ያለውን ድጋፍ ያገኙ በሽተኞች ረዥም ዕድሜ እንደኖሩ የጠቆመ ሲሆን በቅርቡ የተደረገ ሌላ ጥናት ግን ውጤቱን አጠራጣሪ አድርጎታል። የሆነ ሆኖ ስሜታዊ ድጋፍ የሚያገኙ በሽተኞች ከማያገኙት ጋር ሲነጻጸሩ የሚያጋጥማቸው የመንፈስ ጭንቀትና የሕመም ስሜት አነስተኛ እንደሆነ ጥናቶች አረጋግጠዋል።

አዎንታዊና አፍራሽ አመለካከት በልብ በሽታ ላይ በሚያስከትለው ውጤት ላይ ያተኮረ አንድ ጥናት እንመልከት። ስለ ሕይወት ያላቸው አመለካከት አዎንታዊ ወይም አፍራሽ መሆኑን ለማየት ከ1,300 በሚበልጡ ሰዎች ላይ ጥንቃቄ የታከለበት ጥናት ተካሂዶ ነበር። ከአሥር ዓመት በኋላ በእነዚህ ሰዎች ላይ በተደረገው ክትትል ከመካከላቸው 12 በመቶ የሚያህሉት የልብ ሕመም እንዳጋጠማቸው ተደርሶበታል። ጥናቱ ከተካሄደባቸው ሰዎች ውስጥ አፍራሽ አመለካከት ያላቸው አዎንታዊ አመለካከት ካላቸው በ2 እጥፍ ገደማ ይበልጣሉ። በሃርቫርድ የኅብረተሰብ ጤና ትምህርት ቤት የጤናና ማኅበራዊ ሁኔታ ረዳት ፕሮፌሰር የሆኑ ሎረ ኩብዛንስኪ የተባሉ ሴት እንደሚከተለው በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል:- “‘አዎንታዊ አስተሳሰብ’ ለጤንነታችሁ ጥሩ ነው ለሚለው አመለካከት የሚቀርበው ማስረጃ በአብዛኛው በምርምር የተደገፈ አልነበረም። በልብ በሽታ ዙሪያ የተደረገው ይህ ጥናት ግን ይህን አመለካከት የሚደግፍ ተጨባጭ የሕክምና ማስረጃ አስገኝቷል።”

ጥሩ ጤንነት እንደሌላቸው ከሚሰማቸው ሰዎች ይልቅ ጥሩ ጤንነት እንዳላቸው የሚሰማቸው ሰዎች ከቀዶ ሕክምና በኋላ ቶሎ እንደሚያገግሙ አንዳንድ ጥናቶች አረጋግጠዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖርና በአዎንታዊ አመለካከት መካከል ግንኙነት እንዳለም ታውቋል። አንድ ጥናት አረጋውያን ስለ እርጅና ያላቸው አዎንታዊና አሉታዊ አመለካከት እንዴት እንደሚነካቸው መርምሯል። አረጋውያን እርጅና ከጥበብና ከካበተ ልምድ ጋር ዝምድና እንዳለው የሚያሳዩ ቃላት በፍጥነት የሚያልፉበት የኮምፒውተር ጨዋታ እንዲጫወቱ ከተደረጉ በኋላ ከበፊቱ የበለጠ ብርታትና ጥንካሬ አግኝተው መራመድ እንደጀመሩ ተደርሶበታል። እንዲያውም የታየው መሻሻል ለ12 ሳምንታት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መሥራት ከሚያስገኘው ውጤት ጋር ተመጣጣኝ ነበር!

ተስፋ፣ ብሩሕ አመለካከትና አዎንታዊ አስተሳሰብ የመሳሰሉት ስሜቶች ለጤና ጠቃሚ መስለው የሚታዩት ለምንድን ነው? ምናልባት የሳይንስ ሊቃውንትና ሐኪሞች እርግጠኛ መልስ ለመስጠት በሚያስችላቸው መጠን ስለ ሰው አእምሮና አካል አላወቁም ይሆናል። የሆነ ሆኖ ጉዳዩን የሚያጠኑ ጠበብቶች በተሞክሮና በእውቀት ላይ ተንተርሰው ምሑራዊ ግምት መስጠት ይችላሉ። ለምሳሌ ያህል በነርቭ ሥርዓት ጥናት ፕሮፌሰር የሆኑ አንድ ሰው እንዲህ ሲሉ ሐሳብ ሰጥተዋል:- “ደስተኛ መሆንና ተስፋን ማለምለም ጥሩ ነው። ደስተኝነት ውጥረትን የሚያስወግድ ደስ የሚል ሁኔታ ስለሆነ ለሰውነትም ይስማማል። ደስተኝነት ሰዎች ምንጊዜም ጤነኞች ሆነው ለመኖር ሊያደርጉት የሚችሉት አንድ ተጨማሪ ነገር ነው።”

ይህ አስተያየት ለሐኪሞች፣ ለሥነ ልቦና ተመራማሪዎችና ለሳይንስ ሊቃውንት አዲስ ሊመስል ቢችልም ለመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ግን አዲስ አይደለም። ከ3,000 ዓመታት ገደማ በፊት ጠቢቡ ንጉሥ ሰሎሞን በመንፈስ አነሳሽነት “ደስተኛ ልብ ጥሩ መድኀኒት ነው፤ የተሰበረ መንፈስ ግን ዐጥንትን ያደርቃል” የሚለውን ሐሳብ በጽሑፍ አስፍሯል። (ምሳሌ 17:22) እዚህ ላይ የተባለውን ልብ በል። ይህ ጥቅስ ደስተኛ ልብ “ጥሩ መድኀኒት ነው” ይላል እንጂ ማንኛውንም ሕመም ይፈውሳል አይልም።

እንዲያውም ተስፋ መድኃኒት ቢሆን ኖሮ እሱን የማያዝ ማን ሐኪም ይኖራል ብሎ መጠየቅ ተገቢ ሊሆን ይችላል። የሆነ ሆኖ ተስፋ ጥሩ ጤንነት ከማስገኘቱም በላይ ሌሎች ጥቅሞች አሉት።

አዎንታዊም ሆነ አፍራሽ አመለካከት በሕይወትህ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ

አዎንታዊ አመለካከት ያላቸው ሰዎች በብዙ መንገዶች እንደሚጠቀሙ ተመራማሪዎች ደርሰውበታል። በትምህርት ቤት፣ በሥራ ቦታ ሌላው ቀርቶ በስፖርቱ መስክ የተሻለ ውጤት ያስመዘግባሉ። ለምሳሌ ያህል፣ በሴት አትሌቶች ላይ አንድ ጥናት ተካሂዶ ነበር። አሠልጣኞቹ ስለ አትሌቶቹ ችሎታ ጥንቃቄ የተሞላበት ግምገማ አቀረቡ። በሌላ በኩል ደግሞ አትሌቶቹ ራሳቸው ስለሚያገኙት ውጤት ያላቸው ተስፋ ተጠና። ስለሚያገኙት ውጤት በትክክል ለመተንበይ ያስቻለው አሠልጣኞቻቸው አትሌቶቹ ከዚያ በፊት ባስመዘገቡት ችሎታ ላይ ተንተርሰው ያቀረቡት ግምገማ ሳይሆን ሴቶቹ ራሳቸው ስለ ውጤታቸው የነበራቸው ተስፋ ነበር። ተስፋ ይህን ያህል ብርቱ ተጽዕኖ እንዲያሳድር ያስቻለው ምንድን ነው?

የአዎንታዊ አመለካከት ተቃራኒ በሆነው አፍራሽ አመለካከት ላይ ጥናት በማድረግ ብዙ እውቀት ለማግኘት ተችሏል። በ1960ዎቹ ዓመታት የተደረጉ አንዳንድ ጥናቶች የእንስሳትን ባሕርይ በሚመለከት ያልተጠበቁ ውጤቶችን አስገኝተዋል። ተመራማሪዎቹ ከእነዚህ ውጤቶች በመነሳት ሰዎች በዕለታዊ ሕይወታቸው በሚገጥሟቸው አንዳንድ ሁኔታዎች ሳቢያ ውለው አድረው “ምንም ነገር ባደርግ አይሳካልኝም” የሚል የተስፋ መቁረጥ ስሜት ሊያዳብሩ እንደሚችሉ ደርሰውበታል። ለምሳሌ ያህል፣ ጥናቱ የተካሄደባቸው ሰዎች ደስ የማይል ድምፅ እንዲሰሙ ተደረጉና የተለያዩ የኤሌክትሪክ ቁልፎችን በየተራ በመጫን ጫጫታውን ማስቆም እንደሚችሉ ተነገራቸው። እነሱም እንደተባሉት አድርገው ድምፁን ማስቆም ቻሉ።

በሁለተኛው ቡድን ውስጥ ላሉትም ይኸው ነገር ተነገራቸው። ሆኖም የኤሌክትሪክ ማጥፊያውን መጫናቸው ምንም ውጤት አላስገኘም። በዚህም ምክንያት በሁለተኛው ቡድን ውስጥ ካሉት መካከል ብዙዎቹ ምንም ማድረግ አንችልም የሚል ስሜት አዳበሩ። በዚያው ዕለት በተደረገ ሌላ ጥናት ላይ እነዚህ ሰዎች ምንም ነገር ቢያደርጉ ልዩነት እንደማያመጣ ስለተሰማቸው ሙከራ ከማድረግ ተቆጠቡ። በዚሁ በሁለተኛው ቡድን ውስጥ ያሉ አዎንታዊ አመለካከት የነበራቸው ሰዎች ግን ምንም ማድረግ አንችልም ብለው ተስፋ አልቆረጡም።

ከእነዚህ ሙከራዎች መካከል አንዳንዶቹን ያዘጋጁት ዶክተር ማርቲን ሴሊግመን አዎንታዊና አፍራሽ አመለካከትን ማጥናት የዕድሜ ልክ ሥራቸው እንዲሆን ለመወሰን ተገፋፍተዋል። በዚህም ምክንያት ምንም ማድረግ እንደማይችሉ ማሰብ የሚቀናቸው ሰዎች ስላላቸው አስተሳሰብ በጥንቃቄ አጠኑ። ከዚያም እንዲህ ያለው አፍራሽ አመለካከት ሰዎች በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎቻቸው እንቅፋት እንደሚሆንባቸው አልፎ ተርፎም ምንም ዓይነት እርምጃ እንዳይወስዱ እንደሚያደርጋቸው ተገነዘቡ። ሴሊግመን አፍራሽ አመለካከትንና የሚያስከትላቸውን ውጤቶች በሚመለከት ሲያጠቃልሉ እንዲህ አሉ:- “ለሃያ አምስት ዓመት ካደረግሁት ጥናት እንደተገነዘብኩት አፍራሽ አመለካከት እንዳላቸው ሰዎች ማንኛውም መጥፎ አጋጣሚ የሚደርስብን በራሳችን ጥፋት እንደሆነ አድርገን የማሰብ ልማድ ከተጠናወተንና ይህንንም ለመለወጥ ምንም ማድረግ እንደማንችል ከተሰማን ለምናደርገው ነገር ሁሉ እንቅፋት ስለሚሆንብን የፈራነው ይደርስብናል።”

ከላይ እንደተጠቀሰው እንዲህ ዓይነቱ መደምደሚያ ለአንዳንዶች አዲስ ቢመስልም ለመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ግን እንግዳ ነገር አይደለም። የሚከተለውን ምሳሌ ልብ በል:- “በመከራ ጊዜ ፈራ ተባ ካልህ፣ ዐቅምህ ምንኛ ደካማ ነው!” (ምሳሌ 24:10) አዎን፣ መጽሐፍ ቅዱስ ተስፋ መቁረጥ አፍራሽ አስተሳሰብ እንዲያድርብህና አስፈላጊውን ነገር እንዳታደርግ አቅም ሊያሳጣህ እንደሚችል ይገልጻል። ታዲያ አፍራሽ አመለካከትን ታግለህ በማሸነፍ አዎንታዊ አመለካከትን ለማዳበርና ተስፋህን ለማለምለም ምን ልታደርግ ትችላለህ?

[በገጽ 14, 15 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ተስፋ ብዙ መልካም ነገሮችን ለማድረግ ያስችላል