በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አፍራሽ አመለካከትን መዋጋት ትችላለህ

አፍራሽ አመለካከትን መዋጋት ትችላለህ

አፍራሽ አመለካከትን መዋጋት ትችላለህ

የሚያጋጥሙህን እንቅፋቶች የምትመለከታቸው እንዴት ነው? በርካታ ጠበብቶች እንደሚያምኑት ለዚህ ጥያቄ የምትሰጠው መልስ አዎንታዊ ወይም አፍራሽ አመለካከት ያለህ ሰው ስለመሆንህ ይናገራል። ሁላችንም በሕይወታችን ውስጥ የተለያዩ ከባድ ችግሮች የሚደርሱብን ሲሆን በአንዳንዶቻችን ላይ ደግሞ ችግሩ ያይላል። ታዲያ አንዳንድ ሰዎች ከደረሰባቸው ችግር አገግመውና መንፈሳቸውን አድሰው እንደገና ሲሞክሩ ሌሎች ግን በጥቃቅን ችግሮችም እንኳን ተስፋ የሚቆርጡት ለምንድን ነው?

ለምሳሌ ያህል፣ ሥራ በመፈለግ ላይ ነህ እንበል። ለቃለ መጠይቅ ቀረብህና ተቀባይነት ሳታገኝ ቀረህ። ከዚያ በኋላ ስለዚህ ሁኔታ ምን ይሰማሃል? ምናልባት አንተን በአንተነትህ ሳይቀበሉህ የቀሩ ይመስል ሁኔታውን እንደዘላቂ ችግር ቆጥረህ ‘እንደ እኔ ያለውን ሰው ማንም ስለማይቀጥር ፈጽሞ ሥራ አላገኝም’ ብለህ ታስብ ይሆናል። ይባስ ብሎ ደግሞ ይህ አንድ አጋጣሚ ለሁሉም የሕይወትህ ዘርፍ የሚኖርህን አመለካከት አጨልሞብህ ‘እኔ ጨርሶ የማልረባ ሰው ነኝ፤ ለማንም አልጠቅምም’ እንድትል ሊያደርግህ ይችላል። እንዲህ ያለው አስተሳሰብ አንድ ሰው አፍራሽ አመለካከት እንዳለው በግልጽ የሚያሳይ ነው።

አፍራሽ አመለካከትን መዋጋት

አፍራሽ አመለካከትን መዋጋት የምትችለው እንዴት ነው? የመጀመሪያው አስፈላጊ እርምጃ እንዲህ ያሉትን አሉታዊ አስተሳሰቦች ለይቶ ማወቅ መቻል ነው። ቀጣዩ እርምጃ ደግሞ እነዚህን አሉታዊ አስተሳሰቦች መዋጋት ይሆናል። ተቀባይነት እንዳታገኝ ያደረጉህን ሌሎች ምክንያቶች ለማወቅ ሞክር። ለምሳሌ ያህል፣ ቃለ መጠይቁን ማለፍ ያልቻልከው በእርግጥ ማንም ሊቀጥርህ ስለማይፈልግ ነው? ወይስ ቀጣሪው ሌሎች መሥፈርቶችን የሚያሟላ ሰው ስለፈለገ?

በተጨባጭ እውነታዎች ላይ በማተኮር እንዲህ ያለው አፍራሽ አመለካከት መሠረተ ቢስ መሆኑን ልትገነዘብ ትችላለህ። አንድ ጊዜ ተቀባይነት ስላላገኘህ ብቻ በእርግጥ ጨርሶ አትረባም ማለት ነው? መጠነኛ ስኬት ስላገኘህባቸው መስኮች ማለትም ስለ መንፈሳዊ እንቅስቃሴህ፣ ከቤተሰብህ ወይም ከወዳጆችህ ጋር ስላለህ ግንኙነት ለምን አታስብም? ስለ ወደፊቱ ጊዜ ስታስብ ወደ አእምሮህ የሚመጡትን “ክፉ ሐሳቦች” ቶሎ ከአእምሮህ አውጣቸው። ለመሆኑ ወደፊት ፈጽሞ ሥራ እንደማታገኝ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ? አሉታዊ አስተሳሰብን ከአእምሮህ ለማውጣት ልታደርገው የምትችለው ሌላም ነገር አለ።

አዎንታዊና በግብ ላይ ያተኮረ አስተሳሰብ

በቅርብ ዓመታት ተመራማሪዎች ለተስፋ ጠበብ ያለ ሆኖም ትኩረት የሚስብ ፍቺ ሰጥተውታል። ተስፋ ከግቦችህ ላይ እንደምትደርስ ማመንን ይጨምራል ብለው ይናገራሉ። በሚቀጥለው ርዕስ ላይ እንደምንመለከተው ተስፋ በእርግጥ ግብ ላይ ከመድረስ በላይ የሆኑ ነገሮችንም የሚጨምር ቢሆንም ተመራማሪዎቹ የሰጡት ፍቺ በበርካታ መንገዶች ጠቃሚ ይመስላል። እንዲህ ያለው ተስፋ ይበልጥ አዎንታዊና በግብ ላይ ያተኮረ አስተሳሰብ እንድናዳብር ሊረዳን ይችላል።

ለመጪው ጊዜ ያወጣናቸው ግቦች ላይ እንደርሳለን ብለን ለማመን እንድንችል ግብ የማውጣትና እዚያ ላይ የመድረስ ልምድ ማጎልበት ያስፈልገናል። እንዲህ ዓይነት ልምድ እንደሌለህ ከተሰማህ ለራስህ ስለምታወጣቸው ግቦች በጥሞና ማሰቡ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል። ለመሆኑ ግቦች አሉህ? ብዙውን ጊዜ በሕይወታችን ውስጥ ትልቁን ቦታ የምንሰጠው ምን እንደሆነ እንኳ ቆም ብለን ሳናስብ በዕለታዊ የኑሮ ውጣ ውረዶች በቀላሉ ልንጠመድ እንችላለን። ቅድሚያ ልንሰጣቸው የሚገቡ ነገሮችን በግልጽ ማስቀመጥን በሚመለከት መጽሐፍ ቅዱስ “ከሁሉ የሚሻለውን ለይታችሁ እንድታውቁ” በማለት ከረዥም ጊዜ በፊት ጥሩ አድርጎ የገለጸውን ምክር እናገኛለን።—ፊልጵስዩስ 1:10

ቅድሚያ ልንሰጣቸው የሚገቡንን ነገሮች ከወሰንን በኋላ በተለያዩ መስኮች ለምሳሌ ያህል ከመንፈሳዊ ሕይወታችን፣ ከቤተሰብ ሕይወታችን ወይም ከሥጋዊ ሕይወታችን ጋር በተያያዘ ወሳኝ ግቦችን ማውጣት ቀላል ይሆንልናል። ይሁንና መጀመሪያ ላይ ብዙ ግቦችን አለማውጣቱ እንዲሁም እያንዳንዱ ግብ ልንደርስበት የምንችል መሆኑን ማረጋገጡ አስፈላጊ ነው። አንድ ግብ ላይ ለመድረስ አስቸጋሪ ከሆነብን ሊያስጨንቀን ብሎም ተስፋ ሊያስቆርጠን ይችላል። በመሆኑም ብዙውን ጊዜ የረዥም ጊዜ ግቦችን በአጭር ጊዜ ግቦች መከፋፈል የተሻለ ነው።

“ካንጀት ካለቀሱ እንባ አይገድም” የሚለው የጥንት ብሂል እውነትነት አለው። ወሳኝ የሆኑ ግቦችን ካወጣን በኋላ ከግቦቻችን ላይ ለመድረስ የሚያስችል ወኔና ቁርጠኝነት ሊኖረን ያስፈልጋል። ባወጣናቸው ግቦች አስፈላጊነትና እነርሱ ላይ መድረስ በሚያስገኘው ጥቅም ላይ በማሰላሰል ቁርጠኝነታችንን ማጠናከር እንችላለን። እንቅፋቶች ሊያጋጥሙን እንደሚችሉ የታወቀ ነው፤ ሆኖም እነዚህን መሰናክሎች መውጫ ቀዳዳ እንደሌላቸው ችግሮች ሳይሆን ልንወጣቸው እንደምንችላቸው ፈተናዎች አድርገን ልንመለከታቸው ይገባል።

ሆኖም ግቦቻችን ላይ ለመድረስ ስለሚያስችሉን ተግባራዊ መንገዶችም ማሰብ ያስፈልገናል። ስለ ተስፋ ጠቃሚነት ሰፊ ጥናት ያካሄዱ ሪክ ሲንደር የተባሉ ደራሲ አንድ ሰው ያሰበው ግብ ላይ ለመድረስ የተለያዩ መንገዶችን መፈለግ እንደሚኖርበት ይመክራሉ። በመሆኑም አንዱ መንገድ ውጤታማ ካልሆነ ሌሎች አማራጮችን መሞከር እንችላለን።

በተጨማሪም ሲንደር አንድን ግብ በሌላ ግብ የመተካት ልማድ ማዳበር አስፈላጊ መሆኑን ይመክራሉ። አንድ ግብ ላይ እንዳንደርስ መሰናክል ካጋጠመን እርሱን ይዘን መብሰልሰል ተስፋ ከመቁረጥ በቀር ምንም ፋይዳ አይኖረውም። በሌላ በኩል ግን ያንን ግብ ሊደረስበት በሚችል የተሻለ ግብ መተካት ተስፋችንን የምንጥልበት ነገር ያስገኝልናል።

በዚህ ረገድ መጽሐፍ ቅዱስ ጠቃሚ ምሳሌ ይዞልናል። ንጉሥ ዳዊት ለአምላኩ ለይሖዋ ቤተ መቅደስ የመሥራት ትልቅ ግብ ነበረው። ይሁን እንጂ አምላክ ይህን መብት የሚያገኘው ልጁ ሰሎሞን እንደሆነ ነገረው። ዳዊት በሁኔታው ቅር ከመሰኘት ወይም እኔ ካልሠራሁ ብሎ ችክ ከማለት ይልቅ የነበረውን ግብ ቀየረ። መላ ጉልበቱን ልጁ ወደፊት ግንባታውን ለማጠናቀቅ የሚያስፈልገውን ገንዘብና ቁሳቁስ ለማጠራቀም አዋለ።—1 ነገሥት 8:17-19፤ 1 ዜና መዋዕል 29:3-7

አፍራሽ አመለካከትን በመዋጋት እንዲሁም አዎንታዊና በግብ ላይ ያተኮረ አመለካከት በማዳበር ተስፋችንን ከፍ በማድረግ ረገድ ቢሳካልንም እንኳ አንዳንድ ጊዜ ተስፋ እንቆርጥ ይሆናል። ለምን? በዚህ ዓለም አብዛኛው ጊዜ የተስፋ ቢስነት ስሜት የሚያጋጥመን ከቁጥጥራችን ውጪ ከሆኑ መንስኤዎች በመሆኑ ነው። የሰውን ልጅ እያሰቃዩ ያሉት እንደ ድህነት፣ ጦርነት፣ የፍትሕ መዛባት እንዲሁም በሽታና ሞት የመሳሰሉ አይቀሬ ችግሮች የሚያስከትሉት ስጋት እያሉ እንዴት አድርገን በተስፋ የተሞላ አመለካከት ይዘን መቀጠል እንችላለን?

[በገጽ 17 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ለቃለ መጠይቅ ቀርበህ ተቀባይነት ባታገኝ ወደፊት ጨርሶ ሥራ እንደማታገኝ ይሰማሃል?

[በገጽ 18 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ንጉሥ ዳዊት በነበሩት ግቦች ረገድ ማስተካከያ አድርጓል