በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ፍጥረት ቀድሟቸዋል

ፍጥረት ቀድሟቸዋል

ፍጥረት ቀድሟቸዋል

“ሽመላ እንኳ በሰማይ፣ የተወሰነ ጊዜዋን ታውቃለች።”—ኤርምያስ 8:7

ርምያስ በየዓመቱ ስለሚሰደዱ ሽመላዎች የጻፈው ከ2,500 ዓመታት በፊት ነበር። ዛሬም ቢሆን ሰዎች ወደ ሌሎች አካባቢዎች በሚፈልሱ ፍጥረታት በእጅጉ ይደነቃሉ። ለምሳሌ፣ ሳልመን የተባሉ ዓሣዎች በውቅያኖስ ውስጥ በሺህ የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮችን ዋኝተው ወደ ተወለዱበት ወንዝ ሲመለሱ ሌዘርባክ የተባሉ የውኃ ውስጥ ዔሊዎች ደግሞ አስደናቂ ጉዞ ያደርጋሉ። እንቁላሎቿን በኢንዶኔዥያ የምትጥል አንዲት ዔሊ 20,000 ኪሎ ሜትሮች ተጉዛ በዩናይትድ ስቴትስ በሚገኘው የኦሪገን የባሕር ዳርቻ ላይ ተገኝታለች። እነዚህ የባሕር ውስጥ ዔሊዎች እንቁላል ለመጣል አብዛኛውን ጊዜ ወደዚያው የኢንዶኔዥያ አካባቢ ይመለሳሉ።

አንዳንድ ፍጥረታት ወደ ቀድሞ መኖሪያቸው በመመለስ ረገድ ከሚፈልሱት እንስሳት የሚልቅ አቅጣጫን የማወቅ አስደናቂ ችሎታ አላቸው። ለምሳሌ፣ ተመራማሪዎች 18 አልባትሮሶችን በፓስፊክ ውቅያኖስ ከምትገኘው አነስተኛ ደሴት በአውሮፕላን ወስደው በሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደሚገኙ የተለያዩ ቦታዎች ይኸውም አንዳንዶቹን በፓስፊክ ውቅያኖስ ምዕራባዊ ዳርቻ ሌሎቹን ደግሞ በምሥራቃዊ ዳርቻ ለቀቋቸው። አብዛኞቹ ወፎች ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ወደነበሩበት ቦታ ተመልሰዋል።

ርግቦች ማደንዘዣ ከተወጉ ወይም በሚሽከረከር በርሜል ውስጥ ከተደረጉ በኋላ 150 ኪሎ ሜትር ያህል ርቀት ላይ ወደሚገኝ የማያውቁት ቦታ ተወስደው ተለቀቁ፤ ይሁንና አቅጣጫቸውን ለማስላት ጥቂት ከዞሩ በኋላ በመጡበት አቅጣጫ በትክክል መብረር ችለዋል። ርግቦቹ ዓይናቸው አጥርቶ እንዳያይ ሌንስ ከተደረገላቸው በኋላም እንኳ ወደ ቀድሞ መኖሪያቸው መብረር በመቻላቸው ተመራማሪዎች ርግቦቹ ቤታቸው የሚገኝበትን አቅጣጫ ማስላት የቻሉት የጉዞ ጠቋሚ መረጃዎችን በማገናዘብ እንደሆነ ደርሰውበታል።

ሞናርክ የሚባሉት ቢራቢሮዎች በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ በጣም ሰፊ አካባቢዎች ተነስተው ከአንድ ሺህ የሚበልጡ ኪሎ ሜትሮችን ከተጓዙ በኋላ በሜክሲኮ ወደሚገኝ አንድ አነስተኛ አካባቢ ይደርሳሉ። ሜክሲኮ ሄደው የማያውቁ ቢሆንም እንኳ መንገዳቸውን ሳይስቱ አብዛኛውን ጊዜ ቅድመ አያቶቻቸው ከዓመት በፊት ሰፍረውበት በነበረው በዚያው ዛፍ ላይ ይሰፍራሉ። ይህ ችሎታቸው ዛሬም ተመራማሪዎችን ግራ እንዳጋባ ነው።

ሰዎች የሚጠቀሙባቸው አውቶማቲክ አቅጣጫ ጠቋሚ መሣሪያዎች ሙሉ በሙሉ በሳተላይቶች ላይ የተመኩ ሊሆኑ ይችላሉ፤ ብዙ እንስሳት ግን አቅጣጫቸውን ለማወቅ የተለያዩ ዘዴዎችን የሚጠቀሙ ይመስላል። ከዘዴዎቹ መካከል በመሬት ላይ የሚገኙ የተለያዩ ምልክቶችንና ፀሐይን መመልከት፣ መግነጢሳዊ መስኮችን፣ የተለዩ ሽታዎችን አልፎ ተርፎም ድምፆችን ማገናዘብ ይገኙበታል። ጄምስ ጉልድ የተባሉ የባዮሎጂ ፕሮፌሰር እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፦ “ሕልውናቸው አቅጣጫቸውን በትክክል በማወቅ ላይ የተመካ እንስሳት በተፈጥሮ ያገኟቸው ብዙ ችሎታዎች አሏቸው። . . . የተለያዩ አማራጭ ዘዴዎች ያሏቸው ሲሆን ይበልጥ አስተማማኝ ሆኖ ያገኙትን ዘዴ ይጠቀማሉ።” እንስሳት ያላቸው አቅጣጫን የማወቅ ችሎታ እጅግ የተራቀቀ መሆኑ ዛሬም ተመራማሪዎችን ግራ ማጋባቱን ቀጥሏል።