በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 18

ያዕቆብ ወደ ካራን ሄደ

ያዕቆብ ወደ ካራን ሄደ

ያዕቆብ እያነጋገራቸው ያሉት እነዚህ ሰዎች እነማን እንደሆኑ ታውቃለህ? ያዕቆብ ለብዙ ቀናት ከተጓዘ በኋላ እነዚህን ሰዎች በአንድ የውኃ ጉድጓድ አጠገብ አገኛቸው። በጎቻቸውን እየጠበቁ ነበር። ያዕቆብ ‘አገራችሁ የት ነው?’ በማለት ጠየቃቸው።

‘ካራን’ አሉት።

‘ላባን ታውቁታላችሁ?’ ሲል ያዕቆብ ጠየቃቸው።

‘አዎ’ ብለው መለሱለት። ‘እንዲያውም ይኸው፣ ልጁ ራሔል የእርሱን በጎች እየነዳች መጣች።’ ከሩቅ እየመጣች ያለችውን ራሔልን አየሃት?

ያዕቆብ ራሔል የአጎቱን በጎች እየነዳች ስትመጣ አየና በጎቹ መጠጣት እንዲችሉ ሄዶ ድንጋዩን ከውኃ ጉድጓዱ ላይ አነሳው። ከዚያም ያዕቆብ ራሔልን ሳማትና ማንነቱን ነገራት። ራሔል በጣም ተደሰተች፤ ወደ ቤት ሄደችና ለአባቷ ለላባ ነገረችው።

ያዕቆብ እርሱ ጋር ለመኖር በመምጣቱ ላባ በጣም ደስ አለው። ያዕቆብ ራሔልን ማግባት እንደሚፈልግ ሲነግረውም ላባ ተደሰተ። ይሁን እንጂ ራሔልን ለማግባት እንዲችል ሰባት ዓመት እንዲያገለግለው ጠየቀው። ያዕቆብ ራሔልን በጣም ይወዳት ስለ ነበረ ላባን ሰባት ዓመት አገለገለው። ይሁን እንጂ የጋብቻው ቀን ሲደርስ ምን እንደተፈጸመ ታውቃለህ?

ላባ በራሔል ፋንታ ትልቋን ልጁን ለያዕቆብ ዳረለት። ያዕቆብ እንደገና ለሰባት ዓመታት ላባን ለማገልገል ሲስማማ ላባ ራሔልንም ሚስት እንድትሆነው ሰጠው። በዚያ ዘመን አምላክ ወንዶች ከአንድ በላይ ሚስቶችን ማግባት እንዲችሉ ፈቅዶላቸው ነበር። በአሁኑ ጊዜ ግን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው አንድ ወንድ ማግባት ያለበት አንዲት ሚስት ብቻ ነው።