በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 26

ኢዮብ ለአምላክ ታማኝ ሆኗል

ኢዮብ ለአምላክ ታማኝ ሆኗል

በበሽታ እየተሠቃየ ያለው ይህ ሰው አያሳዝንህም? ሰውዬው ኢዮብ ይባላል፤ ሴትየዋ ደግሞ ሚስቱ ነች። ኢዮብን ምን እያለችው እንደሆነ ታውቃለህ? ‘አምላክን ስደብና ሙት’ እያለችው ነው። እንዲህ ብላ ልትናገር የቻለችው ለምን እንደሆነና ኢዮብ ብዙ መከራ ሊደርስበት የቻለው ለምን እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

ኢዮብ ይሖዋን የሚታዘዝ ታማኝ ሰው ነበር። በከነዓን አቅራቢያ በምትገኘው ዖፅ በተባለች ምድር ይኖር ነበር። ይሖዋ ኢዮብን በጣም ይወደው ነበር፤ ይሁን እንጂ አንድ የኢዮብ ጠላት ነበር። እርሱ ማን እንደሆነ ታውቃለህ?

ሰይጣን ዲያብሎስ ነው። ሰይጣን ይሖዋን የሚጠላ ክፉ መልአክ እንደሆነ አስታውስ። አዳምና ሔዋን ይሖዋን እንዳይታዘዙ ማድረግ ችሎ ነበር፤ እንዲሁም ሌላ ማንኛውንም ሰው ይሖዋን እንዳይታዘዝ ማድረግ እንደሚችል አድርጎ አስቦ ነበር። ይሁን እንጂ እንደዚያ ማድረግ ችሏልን? አልቻለም። እስቲ እስካሁን ታሪካቸውን የተማርነውን ብዙ ታማኝ ወንዶችና ሴቶች እንኳ አስብ። የስንቶቹን ስም መጥራት ትችላለህ?

ያዕቆብና ዮሴፍ በግብፅ አገር ከሞቱ በኋላ በመላው ምድር ላይ ከማንም ይበልጥ ለይሖዋ ታማኝ የነበረው ሰው ኢዮብ ነበር። ይሖዋ አምላክ፣ ሰይጣን ሁሉንም ሰው ክፉ ማድረግ የማይችል መሆኑን እንዲገነዘብ ለማድረግ ፈልጎ ነበር፤ በመሆኑም ሰይጣንን ‘ኢዮብን ተመልከተው። ምን ያህል ለእኔ ታማኝ እንደሆነ ተመልከት’ አለው።

‘እርሱ ታማኝ የሆነው ስለባረክኸውና ብዙ ጥሩ ነገሮች ስላገኘ ነው። እነዚህን ነገሮች ብትወስድበት ግን ይሰድብሃል’ በማለት ሰይጣን ተከራከረ።

ስለዚህ ይሖዋ እንዲህ አለው:- ‘ያለውን ነገር ሁሉ ውሰድበት። በኢዮብ ላይ መፈጸም የምትፈልገውን ክፉ ነገር ሁሉ አድርግበት። ከዚያ በኋላ ይሰድበኝ እንደሆነና እንዳልሆነ እናያለን። ነገር ግን እንዳትገድለው ተጠንቀቅ።’

በመጀመሪያ ሰይጣን ሰዎች የኢዮብን ከብቶችና ግመሎች እንዲሰርቋቸውና በጎቹ እንዲሞቱ አደረገ። ከዚያም አሥሩን ወንዶችና ሴቶች ልጆቹን በዐውሎ ነፋስ ገደላቸው። ቀጥሎም ሰይጣን ኢዮብን ይህ መጥፎ በሽታ እንዲይዘው አደረገ። ኢዮብ በጣም ተሠቃየ። የኢዮብ ሚስት ‘አምላክን ስደብና ሙት’ ያለችው ለዚህ ነበር። ይሁን እንጂ ኢዮብ ይህን አላደረገም። በተጨማሪም ሦስት አስመሳይ ጓደኞች መጥተው ይህ የደረሰብህ መጥፎ ድርጊት ስለ ፈጸምክ ነው አሉት። ሆኖም ኢዮብ ታማኝነቱን ጠበቀ።

ይህ ይሖዋን በጣም አስደሰተው፤ በኋላም ሥዕሉ ላይ እንደምታየው ይሖዋ ኢዮብን ባረከው። ከበሽታውም አዳነው። ኢዮብ እንደገና 10 ቆንጆ ልጆች ወለደ፤ እንዲሁም በፊት ከነበረው ሁለት እጥፍ የሚሆኑ ከብቶች፣ በጎችና ግመሎች አገኘ።

ልክ እንደ ኢዮብ ምንጊዜም ለይሖዋ ታማኝ ትሆናለህን? ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ አምላክ አንተንም ይባርክሃል። ምድር በሙሉ ልክ እንደ ኤደን የአትክልት ስፍራ ውብ በምትሆንበት ጊዜ ለዘላለም መኖር ትችላለህ።