በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 42

አንዲት አህያ ተናገረች

አንዲት አህያ ተናገረች

አህያ ስትናገር ሰምተህ ታውቃለህ? ‘ኧረ ሰምቼ አላውቅም። እንስሳት መናገር አይችሉም’ ትል ይሆናል። መጽሐፍ ቅዱስ ግን አፍ አውጥታ ስለተናገረች አንዲት አህያ ይገልጻል። ይህ ሊሆን የቻለው እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

እስራኤላውያን ወደ ከነዓን ምድር ለመሄድ ተዘጋጅተው ነበር። የሞዓብ ንጉሥ ባላቅ እስራኤላውያንን በጣም ፈራቸው። ስለዚህ እስራኤላውያንን መጥቶ እንዲረግምለት በለዓም ወደተባለ አንድ ብልጥ ሰው መልእክት ላከ። ባላቅ በለዓምን ብዙ ገንዘብ እሰጥሃለሁ ብሎ ቃል ገባለት፤ ስለዚህ በለዓም አህያው ላይ ተቀመጠና ከባላቅ ጋር ለመገናኘት ጉዞ ጀመረ።

ይሖዋ በለዓም ሕዝቡን እንዲረግምበት አልፈለገም። ስለዚህ መንገድ ዘግቶበት በለዓምን እንዲያስቆመው አንድ ረጅም ሰይፍ የያዘ መልአክ ላከ። በለዓም መልአኩን ማየት አልቻለም ነበር፤ አህያው ግን መልአኩን አየችው። ስለዚህ አህያይቱ በተደጋጋሚ ከመልአኩ ለመሸሽ ሞከረች፤ በመጨረሻም በመንገዱ ላይ ተኛች። በለዓም በጣም ተናደደና አህያውን በዱላ መታት።

ከዚያም ይሖዋ አህያዋ ስትናገር በለዓም እንዲሰማ አደረገ። ‘ምን አድርጌህ ነው የምትመታኝ?’ በማለት አህያይቱ ጠየቀችው።

‘ሞኝ ስላደረግሽኝ ነው፤ ሰይፍ ይዤ ቢሆን ኖሮ እገድልሽ ነበር!’ አላት።

‘ከዚህ በፊት እንዲህ አድርጌብህ አውቃለሁ?’ ስትል አህያይቱ ጠየቀችው።

‘እንዲህ አድርገሽብኝ አታውቂም’ ሲል በለዓም መለሰላት።

ከዚያም ይሖዋ በለዓም መንገዱ ላይ ሰይፍ ይዞ የቆመውን መልአክ እንዲመለከት አደረገው። መልአኩ እንዲህ አለው:- ‘አህያህን የመታኻት ለምንድን ነው? መንገድህን የዘጋሁት እስራኤላውያንን ሄደህ እንዳትረግማቸው ነው። አህያህ ከእኔ ባትሸሽ ኖሮ እገድልህ ነበር፤ አህያህን ግን አልነካትም ነበር።’

በለዓምም ‘ኃጢአት ሠርቻለሁ። መንገዱ ላይ እንደቆምክ አላወቅሁም ነበር’ አለ። መልአኩ በለዓም እንዲሄድ ፈቀደለት፤ በለዓምም ከባላቅ ጋር ለመገናኘት ሄደ። ከዚህም በኋላ እንኳ እስራኤላውያንን ለመርገም ሞክሮ ነበር፤ ይሁን እንጂ በዚያ ፋንታ ይሖዋ ሦስት ጊዜ እስራኤላውያንን እንዲባርክ አደረገው።