በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 47

በእስራኤል የነበረ ሌባ

በእስራኤል የነበረ ሌባ

ይህ ሰው ድንኳኑ ውስጥ ምን እየቀበረ እንዳለ ተመልከት! አንድ የሚያምር ካባ፣ ወርቅና ብር እየቀበረ ነው። እነዚህን ነገሮች የወሰደው ከኢያሪኮ ከተማ ነው። ይሁን እንጂ በኢያሪኮ የነበሩ ነገሮች ምን መሆን ነበረባቸው? ታስታውሳለህ?

መጥፋት ነበረባቸው፤ ወርቁና ብሩ ደግሞ ወደ ይሖዋ የማደሪያ ድንኳን ግምጃ ቤት መግባት ነበረበት። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች አምላክን አልታዘዙም። የአምላክ ንብረት የሆነውን ነገር ሰርቀዋል። ሰውየው አካን ይባላል፤ ከእርሱ ጋር ያሉት ደግሞ ቤተሰቦቹ ናቸው። የተፈጸመውን ነገር እስቲ እንመልከት።

አካን እነዚህን ነገሮች ከሰረቀ በኋላ ኢያሱ ከጋይ ከተማ ሰዎች ጋር እንዲዋጉ የተወሰኑ ሰዎችን ላከ። የላካቸው ሰዎች ግን በውጊያው ተሸነፉ። አንዳንዶቹ ተገደሉ፤ የተቀሩት ደግሞ ሸሹ። ኢያሱ በጣም አዘነ። መሬት ላይ በግምባሩ ተደፍቶ ‘ይህ እንዲደርስብን የፈቀድከው ለምንድን ነው?’ በማለት ወደ ይሖዋ ጸለየ።

ይሖዋ እንዲህ ሲል መለሰለት:- ‘ተነሥ! እስራኤላውያን ኃጢአት ሠርተዋል። መጥፋት የነበረባቸውንም ሆነ ወደ ይሖዋ የማደሪያ ድንኳን መግባት የነበረባቸውን ነገሮች ወስደዋል። አንድ የሚያምር ካባ ሰርቀው ደብቀዋል። የተሰረቀውን ዕቃና ሌባውን እስክታጠፋ ድረስ አልባርክህም።’ ይሖዋ ኢያሱን ይህ መጥፎ ሰው ማን እንደሆነ አሳይሃለሁ አለው።

ስለዚህ ኢያሱ ሕዝቡን ሁሉ ሰበሰበ፤ ይሖዋም መጥፎውን ሰው አካንን አጋለጠው። አካን እንዲህ አለ:- ‘ኃጢአት ሰርቻለሁ። አንድ የሚያምር ካባ፣ ወርቅና ብር አየሁ። እነዚህን ነገሮች በጣም ስለተመኘኋቸው ወሰድኋቸው። በድንኳኔ ውስጥ ተቀብረው ታገኟቸዋላችሁ።’

እነዚህን ነገሮች አግኝተው ወደ ኢያሱ ሲያመጧቸው ኢያሱ አካንን ‘ይህን ሁሉ መከራ ያመጣህብን ለምንድን ነው? እነሆ ይሖዋ በአንተም ላይ መከራ ያመጣብሃል!’ አለው። ሕዝቡ ሁሉ አካንንና ቤተሰቡን በድንጋይ ወግረው ገደሏቸው። ይህ ሁኔታ የእኛ ያልሆነውን ነገር ፈጽሞ መውሰድ እንደሌለብን አያሳይምን?

ከዚያ በኋላ እስራኤላውያን ጋይን ለመውጋት እንደገና ሄዱ። በዚህ ጊዜ ይሖዋ ሕዝቡን ስለረዳቸው በውጊያው አሸነፉ።