በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 57

አምላክ ዳዊትን መረጠው

አምላክ ዳዊትን መረጠው

ምን እንደተፈጸመ ታያለህ? ልጁ ይቺን የበግ ግልገል ከድቡ አድኗታል። ድቡ መጣና ግልገሏን ሊበላ ይዟት ሄደ። ይሁን እንጂ ልጁ ተከትሏቸው ሮጠና ግልገሏን ከድቡ አፍ አስጣላት። ድቡ ተመልሶ ሲመጣበት ልጁ ድቡን ያዘውና መትቶ ገደለው! በሌላም ጊዜ እንደዚሁ ከበጎቹ መካከል አንዷን ከአንበሳ አድኗል። ደፋር ልጅ አይደለም? ይህ ልጅ ማን እንደሆነ ታውቃለህ?

ይህ ልጅ ዳዊት ይባላል። በቤተ ልሔም ከተማ ይኖር ነበር። አያቱ የሩትና የቦዔዝ ልጅ የሆነው ኢዮቤድ ነው። እነዚህን ሰዎች አስታወስካቸው? የዳዊት አባት ደግሞ እሴይ ነው። ዳዊት የአባቱን በጎች ይጠብቅ ነበር። ዳዊት የተወለደው ይሖዋ ሳኦልን ንጉሥ እንዲሆን ከመረጠው ከ10 ዓመት በኋላ ነበር።

ከዕለታት አንድ ቀን ይሖዋ ሳሙኤልን እንዲህ አለው:- ‘ልዩ የቅባት ዘይት ይዘህ በቤተ ልሔም ወደሚገኘው ወደ እሴይ ቤት ሂድ። ከልጆቹ አንዱን ንጉሥ እንዲሆን መርጬዋለሁ።’ ሳሙኤል የእሴይን የመጀመሪያ ልጅ ኤልያብን ሲመለከት በልቡ ‘ይሖዋ የመረጠው ይህን መሆን አለበት’ አለ። ይሁን እንጂ ይሖዋ ‘የቁመቱን መርዘምና ቆንጆ መሆኑን አትመልከት። ንጉሥ እንዲሆን አልመረጥኩትም’ አለው።

ስለዚህ እሴይ አሚናዳብ የተባለውን ልጁን ጠራውና ወደ ሳሙኤል አመጣው። ሆኖም ሳሙኤል ‘ይሖዋ ይኼኛውንም አልመረጠውም’ አለ። ቀጥሎ እሴይ ሳማ የተባለውን ልጁን አመጣው። ሳሙኤል ‘ይሖዋ ይህንንም አልመረጠውም’ አለ። እሴይ ሰባት ወንዶች ልጆቹን ሳሙኤል ፊት አቀረባቸው፤ ሆኖም ይሖዋ አንዳቸውንም አልመረጠም። ሳሙኤል ‘ወንዶቹ ልጆችህ በሙሉ እነዚህ ናቸው?’ በማለት ጠየቀው።

‘የመጨረሻው ልጅ ይቀራል፤ ግን በግ እየጠበቀ ነው’ ሲል እሴይ መለሰ። ዳዊትን ሲያመጡት ሳሙኤል ዳዊት መልከ መልካም ልጅ እንደሆነ አስተዋለ። ይሖዋ ‘የመረጥኩት ይህንን ነው፤ እርሱን ቀባው’ አለው። ሳሙኤልም እንደተባለው አደረገ። ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ የሚሆንበት ጊዜ ይመ⁠ጣል።