በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 60

አቢግያና ዳዊት

አቢግያና ዳዊት

ከዳዊት ጋር ለመገናኘት ወደ እርሱ እየመጣች ያለችው ቆንጆ ሴት ማን እንደሆነች ታውቃለህ? አቢግያ ትባላለች። ጥሩ የማስተዋል ችሎታ ስለነበራት ዳዊት መጥፎ ድርጊት ከመፈጸም እንዲቆጠብ አድርጋዋለች። ይሁን እንጂ ይህን ከመመርመራችን በፊት ዳዊት ምን ሁኔታ እንዳጋጠመው እንመልከት።

ዳዊት ከሳኦል ከሸሸ በኋላ በዋሻ ውስጥ ተደበቀ። ወንድሞቹና የተቀሩት ቤተሰቦቹ አብረውት ሆኑ። በጠቅላላ 400 ሰዎች ከእርሱ ጋር ተቀላቀሉና ዳዊት መሪያቸው ሆነ። ከዚያም ዳዊት ወደ ሞዓብ ንጉሥ ሄደና ‘ወደፊት የሚያጋጥመኝን ሁኔታ እስካውቅ ድረስ እባክህ አባቴና እናቴ አንተ ጋር ይቆዩ’ አለው። ከዚያ በኋላ ዳዊትና አብረውት የነበሩት ሰዎች በኮረብታዎች ውስጥ ተደበቁ።

ዳዊት አቢግያን ያገኛት ከዚህ በኋላ ነበር። ባልዋ ናባል ሀብታምና ትልቅ መሬት ያለው ሰው ነበር። 3, 000 በጎችና 1, 000 ፍየሎች ነበሩት። ናባል ክፉ ሰው ነበር። ሚስቱ አቢግያ በጣም ቆንጆ ነበረች። በተጨማሪም ትክክል የሆነውን ነገር ማድረግ የሚቻልበትን መንገድ ታውቅ ነበር። እንዲያውም አንድ ቀን ቤተሰቧን ከጥፋት አድናለች። ይህን ያደረገችው እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

ዳዊትና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ለናባል ውለታ ውለውለታል። በጎቹን ከአደጋ በመጠበቅ ረድተውታል። ስለዚህ ከዕለታት አንድ ቀን ዳዊት ናባል አንድ ውለታ እንዲውልለት ለመጠየቅ አብረውት ከነበሩት ሰዎች መካከል ጥቂቶቹን ላካቸው። ዳዊት የላካቸው ሰዎች ወደ ናባል ሲደርሱ ናባልና ረዳቶቹ በጎቹን እየሸለቱ ነበር። በዚያ ቀን ድግስ ስለነበረ ናባል ብዙ ጥሩ ጥሩ ምግቦች ነበሩት። በዚህም ምክንያት ዳዊት የላካቸው ሰዎች ‘እኛ ውለታ ውለንልሃል። አንድም በግ አልሰረቅንህም፤ ከዚህ ይልቅ በጎችህን እንጠብቅልህ ነበር። እባክህ አሁን ጥቂት ምግብ ስጠን’ አሉት።

ናባል ‘እንደናንተ ላሉ ሰዎች ምግቤን አልሰጥም’ አላቸው። ክፉ ቃል ተናገራቸው፤ ስለ ዳዊትም ብዙ መጥፎ ነገር ተናገረ። ሰዎቹ ተመልሰው ይህን ሲነግሩት ዳዊት በጣም ተቆጣ። አብረውት የነበሩትን ሰዎች ‘ሰይፋችሁን ታጠቁ!’ አላቸው። ከዚያም ናባልንና ከእርሱ ጋር ያሉትን ሰዎች ለመግደል ጉዞ ጀመሩ።

ናባል የተናገረውን ክፉ ቃል የሰማ አንድ ከናባል ጋር የሚኖር ሰው የሆነውን ነገር ሁሉ ለአቢግያ ነገራት። ወዲያውኑ አቢግያ ምግብ አዘጋጀች። ምግቡን በአህዮች ላይ አስጫነችና ጉዞ ጀመረች። ከዳዊት ጋር ስትገናኝ ከአህያዋ ላይ ወረደችና በግምባርዋ መሬት ላይ ተደፍታ ‘እባክህ ጌታዬ ባሌን ናባልን ችላ በለው። እርሱ ሞኝ ነው፤ ሥራውም የሞኝ ሥራ ነው። ይህን ስጦታ አምጥቼልሃለሁ። እባክህ ተቀበለኝ፤ ለፈጸምነውም በደል ይቅር በለን’ አለች።

ዳዊት ‘አንቺ ጥበበኛ ሴት ነሽ። በበቀል ስሜት ናባልን ከመግደል እንድቆጠብ አድርገሽኛል። አሁን በሰላም ወደ ቤትሽ ሂጂ’ አላት። ከጊዜ በኋላ ናባል ሲሞት አቢግያ የዳዊት ሚስት ሆነች።