በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 64

ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ሠራ

ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ሠራ

ዳዊት ከመሞቱ በፊት አምላክ የሰጠውን የይሖዋን ቤተ መቅደስ ፕላን ለሰሎሞን ሰጥቶታል። ሰሎሞን መግዛት በጀመረ በአራተኛው ዓመት ቤተ መቅደሱን መሥራት ጀመረ፤ ቤተ መቅደሱን ሠርቶ ለመጨረስ ሰባት ዓመት ተኩል ፈጅቷል። በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በቤተ መቅደሱ ሥራ ተሠማርተው ነበር፤ ይህን ሕንፃ ለመገንባት በጣም ብዙ ገንዘብ ወጥቷል። ይህ የሆነው በጣም ብዙ ወርቅና ብር ለግንባታው ሥራ በመዋሉ ነው።

ቤተ መቅደሱ ልክ እንደ ማደሪያው ድንኳን ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች አሉት። ሆኖም እነዚህ ክፍሎች በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የነበሩትን ክፍሎች ሁለት እጥፍ ይሆናሉ። ሰሎሞን የቃል ኪዳኑን ታቦት በቤተ መቅደሱ የውስጠኛ ክፍል ውስጥ አስቀመጠው፤ በማደሪያው ድንኳን ውስጥ የነበሩትን ሌሎች ነገሮች ደግሞ በሌላኛው ክፍል ውስጥ አስቀመጣቸው።

ቤተ መቅደሱ ተሠርቶ ሲያልቅ አንድ ትልቅ በዓል ተዘጋጀ። ሥዕሉ ላይ እንደምታየው ሰሎሞን በቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት ተንበርክኮ ጸለየ። ሰሎሞን ይሖዋን እንዲህ አለው:- ‘ሰማየ ሰማያት እንኳን ሊይዙህ አይችሉም፤ ይህ ቤተ መቅደስማ እንዴት ሆኖ ሊይዝህ ይችላል! ቢሆንም፣ አምላኬ ሆይ፣ ሕዝብህ በዚህ ቦታ ሲጸልዩ እባክህ ጸሎታቸውን ስማ።’

ሰሎሞን ጸሎቱን ሲጨርስ እሳት ከሰማይ ወረደ። ቀርበው የነበሩትን የእንስሳት መሥዋዕቶች በሙሉ አቃጠላቸው። በተጨማሪም ከይሖዋ የመጣ አንድ ደማቅ ብርሃን ቤተ መቅደሱን ሞላው። ይህ ይሖዋ እየሰማ እንዳለና በቤተ መቅደሱና በሰሎሞን ጸሎት እንደተደሰተ ያሳያል። ከዚህ በኋላ ሕዝቡ ለአምልኮ የሚሄዱት ወደ ማደሪያው ድንኳን ሳይሆን ወደ ቤተ መቅደሱ ሆነ።

ሰሎሞን ለረጅም ጊዜ በጥበብ ሲገዛ ቆየ፤ ሕዝቡም ደስተኞች ነበሩ። ይሁን እንጂ ሰሎሞን ከሌሎች አገሮች የመጡ ይሖዋን የማያመልኩ ብዙ ሴቶችን አገባ። ከእነርሱ መካከል አንዷ ጣዖት ስታመልክ ታያለህ? በመጨረሻ ሚስቶቹ ሰሎሞንም ሌሎችን አማልክት እንዲያመልክ አደረጉት። ሰሎሞን ይህ ሲያደርግ ምን እንደተፈጸመ ታውቃለህ? ሕዝቡን እንደ ቀድሞው በደግነትና በአሳቢነት መንፈስ መያዙን ተወ። ጨካኝ ሆነ፤ ሕዝቡም ደስታ አጡ።

ይህ ሁኔታ ይሖዋ በሰሎሞን ላይ እንዲቆጣ አደረገው፤ እንዲህም አለው:- ‘መንግሥትህን ከአንተ ወስጄ ለሌላ ሰው እሰጠዋለሁ። ይህን የማደርገው በአንተ ዘመን ሳይሆን በልጅህ የግዛት ዘመን ይሆናል። ሆኖም ከልጅህ የምወስደው በመንግሥቱ ሥር ያለውን ሕዝብ በሙሉ አይደለም።’ ይህ የተፈጸመው እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።