በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 72

አምላክ ንጉሥ ሕዝቅያስን ረዳው

አምላክ ንጉሥ ሕዝቅያስን ረዳው

ይህ ሰው ወደ ይሖዋ እየጸለየ ያለው ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? እነዚህን ደብዳቤዎች በይሖዋ መሠዊያ ፊት ያስቀመጣቸው ለምንድን ነው? ሰውየው ሕዝቅያስ ነው። በደቡብ የሚገኙት የሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ንጉሥ ነው። አንድ ከባድ ችግር አጋጥሞታል። ይህ የሆነው ለምንድን ነው?

የአሦራውያን ሠራዊት በሰሜን የሚገኙትን 10 ነገዶች አጥፍቶ ነበር። ይሖዋ ይህ እንዲሆን የፈቀደው በዚያ ይኖሩ የነበሩት ሰዎች በጣም መጥፎዎች ስለነበሩ ነው። አሁን ደግሞ የአሦራውያን ሠራዊት ሁለቱን ነገዶች ያቀፈውን መንግሥት ለመውጋት መጥቷል።

በዚህ ወቅት የአሦር ንጉሥ ለንጉሥ ሕዝቅያስ ደብዳቤዎች ላከ። እነዚህ ደብዳቤዎች ሕዝቅያስ በአምላክ ፊት ዘርግቷቸው የሚታዩት ናቸው። ደብዳቤዎቹ ይሖዋን የሚያቃልሉና ሕዝቅያስ ተስፋ እንዲቆርጥ የሚያደርጉ ነበሩ። ሕዝቅያስ ‘ይሖዋ ሆይ፣ ከአሦር ንጉሥ አድነን። ከዚያ በኋላ አሕዛብ ሁሉ አንተ ብቻ አምላክ እንደሆንህ ያውቃሉ’ ብሎ የጸለየው በዚህ ምክንያት ነው። ይሖዋ ሕዝቅያስን ይሰማው ይሆን?

ሕዝቅያስ ጥሩ ንጉሥ ነበር። አሥሩን የእስራኤል ነገዶች ያቀፈውን መንግሥት ያስተዳድሩ ከነበሩት መጥፎ ነገሥታት ወይም መጥፎ ከነበረው አባቱ ከንጉሥ አካዝ የተለየ ነበር። ሕዝቅያስ የይሖዋን ሕግጋት በሙሉ በሚገባ ይጠብቅ ነበር። ስለዚህ ሕዝቅያስ ጸሎቱን ሲጨርስ ነቢዩ ኢሳይያስ የሚከተለውን ከይሖዋ የመጣ መልእክት ላከለት:- ‘የአሦር ንጉሥ ወደ ኢየሩሳሌም አይመጣም። ከወታደሮቹ አንዱም እንኳ ወደ ከተማይቱ አይቀርብም። በከተማይቱም ላይ አንድም ቀስት አይወረውሩም።’

በዚህ ገጽ ላይ የሚገኘውን ሥዕል ተመልከት። እነዚህ ሁሉ የሞቱ ወታደሮች እነማን እንደሆኑ ታውቃለህ? አሦራውያን ናቸው። ይሖዋ መልአኩን ላከና መልአኩ በአንድ ሌሊት 185, 000 የአሦር ወታደሮችን ገደለ። ስለዚህ የአሦር ንጉሥ ተስፋ ቆረጠና ወደ አገሩ ተመለሰ።

ሁለቱን ነገዶች ያቀፈው መንግሥት ከጥፋት ዳነ፤ ሕዝቡም ለጥቂት ጊዜ ሰላም አገኘ። ይሁን እንጂ ሕዝቅያስ ከሞተ በኋላ ልጁ ምናሴ ነገሠ። ምናሴና ከእሱ በኋላ የነገሠው ልጁ አሞን ሁለቱም በጣም መጥፎ ነገሥታት ነበሩ። ስለዚህ ምድሪቱ እንደገና በወንጀልና በዓመፅ ተሞላች። ንጉሥ አሞን በገዛ አገልጋዮቹ ሲገደል ልጁ ኢዮስያስ ሁለቱን ነገዶች ባቀፈው መንግሥት ላይ ነገሠ