በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 78

በግድግዳ ላይ በእጅ የተጻፈ ጽሑፍ

በግድግዳ ላይ በእጅ የተጻፈ ጽሑፍ

ሰዎቹን ምን አስደነገጣቸው? በአንድ ትልቅ ግብዣ ላይ ነበሩ። የባቢሎን ንጉሥ በሺህ የሚቆጠሩ ታላላቅ እንግዶችን ጋብዞ ነበር። በኢየሩሳሌም ከሚገኘው ከይሖዋ ቤተ መቅደስ የወሰዷቸውን የወርቅ ጽዋዎችና የብር ጽዋዎች እንዲሁም ጎድጓዳ ሳህኖች እየተጠቀሙባቸው ነው። ይሁን እንጂ በድንገት የአንድ ሰው እጅ ጣቶች በአየር ላይ ብቅ ብለው በግድግዳው ላይ መጻፍ ጀመሩ። ሁሉም በፍርሃት ተዋጡ።

በዚህ ጊዜ ንጉሥ ሆኖ ይገዛ የነበረው የናቡከደነፆር የልጅ ልጅ ብልጣሶር ነበር። ጠቢባኖቹን ወደ ውስጥ እንዲያስገቧቸው በታላቅ ድምፅ አዘዘ። ንጉሡ ‘ይህን ጽሑፍ አንብቦ ትርጉሙን ሊነግረኝ የሚችል ሰው ብዙ ስጦታዎች ይሰጡታል፤ በመንግሥቴም ላይ ሦስተኛው የሥልጣን ማዕረግ ይሰጠዋል’ ሲል ተናገረ። ሆኖም ከጠቢባኖቹ መካከል አንዳቸውም እንኳ በግድግዳው ላይ የተጻፈውን ጽሑፍ ማንበብም ሆነ ትርጉሙን መናገር አልቻሉም።

የንጉሡ እናት ጫጫታውን ሰምታ ወደ ትልቁ የምግብ አዳራሽ ገባች። ንጉሡንም እንዲህ አለችው:- ‘አይዞህ፣ አትደንግጥ። ቅዱሳን አማልክትን የሚያውቅ በመንግሥትህ ውስጥ የሚኖር አንድ ሰው አለ። አያትህ ናቡከደነፆር ንጉሥ በነበረበት ዘመን በጠቢባኖቹ ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ ሾሞት ነበር። ይህ ሰው ዳንኤል ይባላል። ልከህ አስመጣውና ይህ ሁሉ ምን ማለት እንደሆነ ይነግርሃል።’

ስለዚህ ዳንኤል ወዲያውኑ ተጠርቶ መጣ። ዳንኤል ምንም ስጦታ እንደማይቀበል ከገለጸ በኋላ ይሖዋ በአንድ ወቅት የብልጣሶርን አያት ናቡከደነፆርን ከንግሥናው ላይ አንስቶት የነበረው ለምን እንደሆነ መናገር ጀመረ። ‘በጣም ኩሩ ስለነበረ ይሖዋ ቀጣው’ ሲል ዳንኤል ተናገረ።

ዳንኤል ብልጣሶርን እንዲህ አለው:- ‘አንተ በእርሱ ላይ የደረሰውን ሁሉ እያወቅህ ልክ እንደ ናቡከደነፆር ኩሩ ሆነሃል። ከይሖዋ ቤተ መቅደስ የተወሰዱትን ጽዋዎችና ዕቃዎች አምጥተህ ጠጣህባቸው። ከእንጨትና ከድንጋይ የተሠሩትን አማልክት አመሰገንህ፤ ታላቁን ፈጣሪያችንንም አላከበርክም። አምላክ ያንን እጅ ልኮ እነዚህን ቃላት እንዲጽፍ ያደረገው በዚህ ምክንያት ነው።

‘የተጻፈው ጽሑፍ ማኔ፣ ማኔ፣ ቴቄል እና ፋሬስ’ ይላል በማለት ዳንኤል ተናገረ።

‘ማኔ ማለት አምላክ የመንግሥትህን ዘመን ቆጥሮ ፈጸመው ማለት ነው። ቴቄል ማለት በሚዛን ተመዘንህ፤ ቀለህም ተገኘህ ማለት ነው። ፋሬስ ማለት ደግሞ መንግሥትህ ለሜዶንና ለፋርስ መንግሥት ተሰጠ ማለት ነው።’

ዳንኤል እየተናገረ ሳለ ሜዶናውያንና ፋርሳውያን ባቢሎንን ማጥቃት ጀምረው ነበር። ከተማይቱን ያዟትና ብልጣሶርን ገደሉት። በግድግዳው ላይ የተጻፈው ጽሑፍ በዚያችው ሌሊት ፍጻሜውን አገኘ! ይሁን እንጂ በዚህ ጊዜ በእስራኤላውያን ላይ ምን ደርሶባቸው ይሆን? ይህን በኋላ እንመለከተዋለን፤ ከዚያ በፊት ግን ዳንኤል ምን እንደደረሰበት እንመል⁠ከት