በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 92

ኢየሱስ የሞቱ ሰዎችን አስነሳ

ኢየሱስ የሞቱ ሰዎችን አስነሳ

እዚህ ላይ የምታያት ልጅ 12 ዓመቷ ነው። ኢየሱስ እጅዋን ይዟል፤ እናትና አባቷ ደግሞ አጠገባቸው ቆመዋል። በጣም የተደሰቱት ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? ለምን እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

የልጅቷ አባት ኢያኢሮስ የሚባል አንድ ባለ ሥልጣን ነበር። ከዕለታት አንድ ቀን ልጁ ታመመችና ተኛች። ሆኖም ሊሻላት አልቻለም። ሕመሙ እየባሰባት ሄደ። ልጃቸው ልትሞት ስለደረሰች ኢያኢሮስና ሚስቱ በጣም ተጨነቁ። ከእሷ ሌላ ምንም ልጅ አልነበራቸውም። ስለዚህ ኢያኢሮስ ኢየሱስን ፍለጋ ሄደ። ኢያኢሮስ ኢየሱስ ስለፈጸማቸው ተአምራት ሰምቶ ነበር።

ኢያኢሮስ ኢየሱስን ባገኘው ጊዜ ኢየሱስን ብዙ ሰዎች ከበውት ነበር። ሆኖም ኢያኢሮስ በሕዝቡ መሐል አልፎ ኢየሱስ እግር ላይ ወደቀ። ‘ልጄ በጣም ታማለች፤ እባክህ መጥተህ አድንልኝ’ ሲል ለመነው። ኢየሱስም እሺ አለው።

ሕዝቡ አብረውት ሲጓዙ ወደርሱ ለመቅረብ ይገፋፉ ነበር። ድንገት ኢየሱስ ቆም አለ። ‘የነካኝ ማን ነው?’ ሲል ጠየቀ። ኢየሱስ ኃይል ከእርሱ ሲወጣ ስለ ተሰማው አንድ ሰው እንደነካው አውቆ ነበር። የነካው ግን ማን ነበር? ለ12 ዓመታት በጣም ታማ የነበረች አንዲት ሴት ናት። ወደ ኢየሱስ ቀርባ ልብሱን ነካችና ዳነች!

ኢየሱስ አንድን ሰው በቀላሉ ሊፈውስ እንደሚችል ኢያኢሮስ ማየት ችሎ ስለነበረ ይህ ሁኔታ ከበፊቱ የበለጠ እምነት እንዲያድርበት አድርጎታል። ይሁን እንጂ በዚህ ወቅት አንድ መልእክተኛ መጣ። ኢያኢሮስን ‘ኢየሱስን አታድክመው፤ ልጅህ ሞታለች’ አለው። ኢየሱስ ይህን ሲነጋገሩ ሰምቶ ኢያኢሮስን ‘አይዞህ፤ ልጅህ ትድናለች’ አለው።

በመጨረሻ ኢያኢሮስ ቤት ሲደርሱ ሰዎቹ በጣም አዝነው እያለቀሱ ነበር። ኢየሱስ ግን ‘አታልቅሱ። ልጅቷ ተኝታለች እንጂ አልሞተችም’ አላቸው። እነርሱ ግን እንደ ሞተች አውቀው ስለ ነበር ሳቁበት።

ኢየሱስ የልጅቷን አባትና እናት እንዲሁም ሦስቱን ሐዋርያቱን አስከትሎ ልጅቷ ተኝታበት ወደነበረው ክፍል ገባ። እጅዋን ያዘና ‘ተነሺ!’ አላት። ሥዕሉ ላይ እንደምታየው ልጅቷ እንደገና ሕያው ሆነች። ተነሳችና ወዲያ ወዲህ ተራመደች! እናትና አባቷ በጣም የተደሰቱት በዚህ ምክንያት ነው።

ኢየሱስ የሞተ ሰው ሲያስነሳ ይህ የመጀመሪያው አልነበረም። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ መጀመሪያ ያስነሳው ሰው ናይን በምትባል ከተማ ትኖር የነበረችን የአንዲት መበለት ልጅ እንደሆነ ይናገራል። በኋላ ኢየሱስ የማርያምና የማርታ ወንድም የሆነውን አልዓዛርንም ከሞት አስነስቷል። ኢየሱስ የአምላክ ንጉሥ ሆኖ ሲገዛ ብዙ ሰዎችን ከሞት ያስነሳል። ይህ አያስደስትም?