በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 94

ኢየሱስ ትንንሽ ልጆችን ይወዳል

ኢየሱስ ትንንሽ ልጆችን ይወዳል

ኢየሱስ እዚህ ላይ አንድ ትንሽ ልጅ አቅፎ ይታያል። ኢየሱስ ለልጆች እንደሚያስብ ከሁኔታው መረዳት ትችላለህ። እየተመለከቱት ያሉት ሰዎች ሐዋርያቱ ናቸው። ኢየሱስ ምን እያላቸው ነው? እስቲ እንመልከት።

ኢየሱስና ሐዋርያቱ ረጅም ጉዞ አድርገው ገና መመለሳቸው ነበር። በመንገድ ላይ ሳሉ ሐዋርያቱ እርስ በርሳቸው ይከራከሩ ነበር። ስለዚህ ከጉዞው በኋላ ኢየሱስ ‘በመንገድ ላይ ሲያከራክራችሁ የነበረው ነገር ምንድን ነው?’ ብሎ ጠየቃቸው። እርግጥ ኢየሱስ ይከራከሩበት የነበረው ነገር ምን እንደሆነ ያውቃል። ሆኖም ይህን ጥያቄ የጠየቃቸው ሐዋርያቱ ይነግሩት እንደሆነና እንዳልሆነ ለማወቅ ብሎ ነው።

ሐዋርያቱ መልስ አልሰጡትም፤ ምክንያቱም በመንገድ ላይ ይከራከሩ የነበረው ከመካከላችን ታላቅ የሚሆነው ማን ነው በሚል ነበር። አንዳንዶቹ ሐዋርያት ከሌሎቹ ከፍ ብለው ለመታየት ይፈልጉ ነበር። ኢየሱስ ታላቅ ለመሆን መፈለግ ተገቢ እንዳልሆነ እንዴት ያስተምራቸው ይሆን?

ትንሹን ልጅ ጠራና በሁሉም ፊት አቆመው። ከዚያም ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው:- ‘እውነት እላችኋለሁ፤ ካልተለወጣችሁና እንደ ልጆች ካልሆናችሁ ወደ አምላክ መንግሥት መግባት አትችሉም። በአምላክ መንግሥት ውስጥ ታላቅ የሚሆነው እንደዚህ ልጅ ያለ ሰው ነው።’ ኢየሱስ እንዲህ ያለው ለምን እንደሆነ ታውቃለህ?

ትንንሽ ልጆች ታላቅ የመሆን ወይም ከሌሎች በልጦ የመታየቱ ጉዳይ አያሳስባቸውም። ስለዚህ ሐዋርያት በዚህ ረገድ ልጆችን መምሰል ይኖርባቸዋል። ታላቅ ለመሆን ወይም ከሌሎች በልጦ ለመታየት በመፈለግ መጣላት የለባቸውም።

ኢየሱስ ለትንንሽ ልጆች ምን ያህል እንደሚያስብ ያሳየባቸው ሌሎች ጊዜያትም ነበሩ። ይህ ከሆነ ከጥቂት ወራት በኋላ አንዳንድ ሰዎች ልጆቻቸውን ወደ ኢየሱስ አመጡአቸው። ሐዋርያቱ ሊያርቋቸው ሞከሩ። ኢየሱስ ግን ሐዋርያቱን ‘ልጆች ወደ እኔ እንዳይመጡ አትከልክሏቸው፤ የአምላክን መንግሥት የሚወርሱት እንደነዚህ ያሉ ሰዎች ናቸው’ አላቸው። ከዚያም ኢየሱስ ልጆቹን አቀፋቸውና ባረካቸው። ኢየሱስ ትንንሽ ልጆችን እንደሚወድ ማወቁ አያስደስትም?