በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 97

ኢየሱስ ንጉሥ ሆኖ መጣ

ኢየሱስ ንጉሥ ሆኖ መጣ

ኢየሱስ ሁለቱን ዓይነ ስውር ለማኞች ከፈወሳቸው ከጥቂት ጊዜ በኋላ በኢየሩሳሌም አቅራቢያ ወደምትገኝ ወደ አንዲት አነስተኛ መንደር መጣ። ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ሁለቱን ‘ወደዚያች መንደር ሂዱ፤ እዚያም ስትደርሱ አንድ የአህያ ውርንጭላ ታገኛላችሁ። ውርንጭላውን ፈትታችሁ አምጡልኝ’ አላቸው።

ውርንጭላውን ሲያመጡለት ኢየሱስ ውርንጭላው ላይ ተቀመጠ። ከዚያም በቅርብ ርቀት ላይ ወደምትገኘው ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ። ወደ ከተማዋ ሲቃረብ ብዛት ያለው ሕዝብ እሱን ለመቀበል ወጣ። አብዛኞቹ ሰዎች ከላይ የሚደርቡትን ልብስ አውልቀው በመንገዱ ላይ አነጠፉት። ሌሎቹ ደግሞ የዘንባባ ቅርንጫፎችን ቆርጠው አመጡ። የዘንባባ ቅርንጫፎቹን በመንገዱ ላይ አንጥፈው ‘በይሖዋ ስም የሚመጣው ንጉሥ የተባረከ ይሁን!’ እያሉ ጮኹ።

ከብዙ ዘመናት በፊት በእስራኤል ውስጥ አዳዲስ ነገሥታት ለሕዝቡ ለመታየት በአህያ ውርንጭላ ላይ ሆነው ወደ ኢየሩሳሌም ይሄዱ ነበር። ኢየሱስ እያደረገ ያለው ይህንኑ ነው። እነዚህ ሰዎች ደግሞ ኢየሱስ ንጉሣቸው እንዲሆን እንደፈለጉ እያሳዩ ነው። ይሁን እንጂ ኢየሱስ እንዲነግሥ የሚፈልጉት ሁሉም ሰዎች አልነበሩም። ኢየሱስ ወደ ቤተ መቅደሱ ሲሄድ የተፈጸመው ሁኔታ ኢየሱስ እንዲነግሥ የማይፈልጉ ሰዎች እንደነበሩ ግልጽ ያደርግልናል።

ኢየሱስ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ዓይነ ስውርና አካለ ስንኩል የነበሩ ሰዎችን ፈወሰ። ትንንሾቹ ልጆች ይህን ሲያዩ ኢየሱስን ማወደስ ጀመሩ። ይሁን እንጂ ይህ ካህናቱን አስቆጣቸው፤ ኢየሱስንም ‘ልጆቹ ምን እያሉ እንዳሉ ትሰማለህ?’ አሉት።

ኢየሱስ ‘አዎ፣ ሰምቻቸዋለሁ፤ “አምላክ ከትንንሽ ልጆች አፍ ምስጋናን ያዘጋጃል” ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጻፈውን አላነበባችሁም?’ ብሎ መለሰላቸው። ስለዚህ ልጆቹ የአምላክን ንጉሥ ማወደሳቸውን ቀጠሉ።

እኛም እንደነዚህ ልጆች መሆን እንፈልጋለን፤ አንፈልግም እንዴ? አንዳንድ ሰዎች ስለ አምላክ መንግሥት መናገራችንን እንድናቆም ለማድረግ ይሞክሩ ይሆናል። እኛ ግን ኢየሱስ ለሰዎች ስለሚያደርግላቸው አስደናቂ ነገሮች ለሌሎች መናገራችንን እንቀጥላለን።

ኢየሱስ በምድር ላይ ሳለ ንጉሥ ሆኖ መግዛት የሚጀምርበት ጊዜ ገና አልደረሰም ነበር። ይህ የሚሆነው መቼ ነው? የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ማወቅ ፈልገው ነበር። ቀጥለን ስለዚህ ነገር እንማራለን።