በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 103

በተዘጋ ክፍል ውስጥ

በተዘጋ ክፍል ውስጥ

ጴጥሮስና ዮሐንስ የኢየሱስ አስከሬን ከነበረበት መቃብር ተመልሰው ሲሄዱ ማርያም ብቻዋን እዚያው ቀረች። ማልቀስ ጀመረች። ከዚያም ከዚህ በፊት ባለው ሥዕል ላይ እንዳየነው ጎንበስ ብላ ወደ ውስጥ ተመለከተች። እዚያ ውስጥም ሁለት መላእክት ተመለከተች! ‘ለምን ታለቅሻለሽ?’ ብለው ጠየቋት።

ማርያም ‘ጌታዬን ወሰዱት፤ የት እንዳደረጉት አላውቅም’ አለቻቸው። ከዚያም ማርያም ዞር ስትል አንድ ሰው አየች። ‘ማንን እየፈለግሽ ነው?’ አላት።

ማርያም ይህ ሰው አትክልተኛው ስለመሰላት የኢየሱስን አስከሬን የወሰደው እሱ ሊሆን ይችላል ብላ አሰበች። ስለዚህ ‘የወሰድከው አንተ ከሆንክ የት እንዳደረግከው ንገረኝ’ አለችው። ሆኖም ይህ ሰው ኢየሱስ ነበር። ማርያም የማታውቀው አካል ለብሶ ነበር። በስሟ ሲጠራት ግን ማርያም ኢየሱስ መሆኑን አወቀች። ሮጣ ሄደችና ደቀ መዛሙርቱን ‘ጌታን አየሁት!’ አለቻቸው።

ከዚያ በኋላ በዚያው ቀን ሁለት ደቀ መዛሙርት ኤማሁስ ወደሚባል መንደር ሲጓዙ አንድ ሰው ከእነርሱ ጋር አብሮ መጓዝ ጀመረ። ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ በመገደሉ በጣም አዝነው ነበር። ሆኖም ሰውየው አብሯቸው ሲጓዝ ብዙ የሚያጽናና ነገር ከመጽሐፍ ቅዱስ ጠቀሰላቸው። በመጨረሻ ጉዞአቸውን አቁመው ምግብ ሊመገቡ ሲሉ ደቀ መዛሙርቱ ይህ ሰው ኢየሱስ እንደሆነ አወቁ። ከዚያም ኢየሱስ ተሰወረ፤ እነዚህ ሁለት ደቀ መዛሙርት ስለ እርሱ ለሐዋርያቱ ለመንገር በፍጥነት ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው ሄዱ።

በዚህ ወቅት ኢየሱስ ለጴጥሮስም ታየው። ሌሎቹ ይህን ሲሰሙ በጣም ተደሰቱ። ከዚያም እነዚህ ሁለት ደቀ መዛሙርት ወደ ኢየሩሳሌም ሄዱና ሐዋርያቱን አገኟቸው። ኢየሱስ በመንገድ ላይ እንዴት እንደታያቸው ነገሯቸው። ይህን እየተናገሩ ሳሉ ምን አስደናቂ ነገር እንደተፈጸመ ታውቃለህ?

ሥዕሉን ተመልከት። በሩ ተዘግቶ የነበረ ቢሆንም ኢየሱስ እዚያው ክፍሉ ውስጥ ብቅ አለ። ደቀ መዛሙርቱ ምንኛ ተደስተው ይሆን! ይህ አስደሳች ቀን አይደለም? ኢየሱስ ለተከታዮቹ ስንት ጊዜ እንደተገለጠላቸው መቁጠር ትችላለህ? አምስት ጊዜ ነው አይደል?

ኢየሱስ ሲገለጥላቸው ሐዋርያው ቶማስ አብሯቸው አልነበረም። ስለዚህ ደቀ መዛሙርቱ ‘ጌታን አየነው!’ ብለው ነገሩት። ሆኖም ቶማስ ራሱን ኢየሱስን ካላየሁ ላምን አልችልም አለ። ከስምንት ቀናት በኋላ ደቀ መዛሙርቱ እንደገና በአንድ የተዘጋ ክፍል ውስጥ አንድ ላይ ተሰባስበው ነበር፤ በዚህ ወቅት ቶማስም አብሯቸው ነበር። ኢየሱስ በድንገት እነርሱ የነበሩበት ክፍል ውስጥ ብቅ አለ። በዚህ ጊዜ ቶማስ አመነ።