በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 104

ኢየሱስ ወደ ሰማይ ተመለሰ

ኢየሱስ ወደ ሰማይ ተመለሰ

ቀናት እያለፉ ሲሄዱ ኢየሱስ ለተከታዮቹ ብዙ ጊዜ ታያቸው። በአንድ ወቅት ወደ 500 የሚጠጉ ደቀ መዛሙርቱ አይተውታል። ኢየሱስ ሲገለጥላቸው ስለ ምን ነገር እንደነገራቸው ታውቃለህ? ስለ አምላክ መንግሥት ነው። ይሖዋ ኢየሱስን ወደ ምድር የላከው ስለ መንግሥቱ እንዲያስተምር ነው። በመሆኑም ኢየሱስ ከሞት ከተነሳም በኋላ እንኳ ይህን ማድረጉን ቀጥሎ ነበር።

የአምላክ መንግሥት ምን እንደሆነ ታስታውሳለህ? አዎ፣ መንግሥቱ በሰማይ የሚገኝ እውን የሆነ አስተዳደር ነው፤ አምላክ ንጉሥ እንዲሆን የመረጠው ደግሞ ኢየሱስን ነው። ቀደም ሲል እንደተማርነው ኢየሱስ የተራቡትን በመመገብ፣ የታመሙትን በመፈወስ አልፎ ተርፎም የሞቱትን በማስነሳት በጣም ጥሩ ንጉሥ እንደሚሆን አሳይቷል።

ስለዚህ ኢየሱስ ንጉሥ ሆኖ በሰማይ ለአንድ ሺህ ዓመት ሲገዛ በምድር ላይ ምን ዓይነት ሁኔታ ይኖር ይሆን? አዎ፣ መላዋ ምድር ውብ ገነት ትሆናለች። ጦርነት፣ ወይም ወንጀል፣ ወይም ደግሞ በሽታ አልፎ ተርፎም ሞት አይኖርም። ይህ እንደሚፈጸም እናውቃለን፤ ምክንያቱም አምላክ ምድርን የፈጠረው ሰዎች እየተደሰቱ የሚኖሩባት ገነት እንድትሆን ነው። በመጀመሪያ የኤደን የአትክልት ቦታን ያዘጋጀው በዚህ ምክንያት ነው። ኢየሱስ አምላክ እንዲከናወኑ የሚፈልጋቸው ነገሮች በሙሉ እንዲፈጸሙ ያደርጋል።

ኢየሱስ ወደ ሰማይ የሚመለስበት ጊዜ ደረሰ። ኢየሱስ ለ40 ቀናት ለደቀ መዛሙርቱ ሲገለጥላቸው ቆይቷል። ስለዚህ እንደገና ሕያው እንደሆነ እርግጠኞች ነበሩ። ሆኖም ከደቀ መዛሙርቱ ተለይቶ ከመሄዱ በፊት ‘መንፈስ ቅዱስን እስክትቀበሉ ድረስ በኢየሩሳሌም ቆዩ’ ብሏቸው ነበር። መንፈስ ቅዱስ እንደ ነፋስ ያለ አንቀሳቃሽ የሆነ የአምላክ ኃይል ነው፤ የኢየሱስ ተከታዮች የአምላክን ፈቃድ እንዲያደርጉ ይረዳቸዋል። በመጨረሻም ኢየሱስ ‘እስከ ምድር ዳር ድረስ ስለ እኔ ስበኩ’ አላቸው።

ኢየሱስ ይህን ከተናገረ በኋላ አንድ አስገራሚ ነገር ተፈጸመ። ሥዕሉ ላይ እንደምታየው ኢየሱስ ወደ ሰማይ መውጣት ጀመረ። ከዚያም ዳመና ሸፈነው፤ ከዚያ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ዳግመኛ አላዩትም። ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሄደ፤ እዚያም ሆኖ በምድር ላይ ያሉትን ተከታዮቹን መግዛት ጀመረ።