በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 106

ከእስር ቤት መውጣት

ከእስር ቤት መውጣት

የእስር ቤቱን በር ከፍቶ የያዘውን መልአክ ተመልከት። ከእስር እያስለቀቃቸው ያሉት ሰዎች የኢየሱስ ሐዋርያት ናቸው። እስር ቤት ሊገቡ የቻሉበትን ምክንያት እስቲ እንመልከት።

ይህ የሆነው መንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ላይ ከፈሰሰ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ነው። ነገሩ እንዲህ ነው:- አንድ ቀን ከሰዓት በኋላ ጴጥሮስና ዮሐንስ በኢየሩሳሌም ወደሚገኘው ቤተ መቅደስ ሄዱ። በቤተ መቅደሱ በር አጠገብ ዕድሜውን ሙሉ አካለ ስንኩል የነበረ አንድ ሰው ተቀምጦ ነበር። ወደ ቤተ መቅደሱ ከሚገቡ ሰዎች ገንዘብ መለመን እንዲችል በየቀኑ ሰዎች ተሸክመው ወደዚህ ቦታ ያመጡት ነበር። ጴጥሮስንና ዮሐንስን ሲመለከት ገንዘብ እንዲሰጡት ለመናቸው። ሐዋርያቱ ምን ያደርጉ ይሆን?

ቆሙና ይህን ምስኪን ሰው ተመለከቱት። ጴጥሮስ ‘ገንዘብ የለኝም፤ ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ። በኢየሱስ ስም ተነሣና ተመላለስ!’ አለው። ከዚያም ጴጥሮስ ሰውየውን በቀኝ እጁ ይዞ አስነሳው፤ ሰውየውም ወዲያውኑ ብድግ ብሎ ወዲያና ወዲህ መሄድ ጀመረ። ሰዎቹ ይህን ሲመለከቱ ይህን አስደናቂ ተአምር በማየታቸው ከመገረማቸውም በላይ በጣም ተደሰቱ።

ጴጥሮስ ‘ይህን ተአምር የሠራነው ኢየሱስን ከሞት ባስነሳው በአምላክ ኃይል ነው’ አለ። እሱና ዮሐንስ እየተናገሩ ሳለ አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች መጡ። ጴጥሮስና ዮሐንስ ኢየሱስ ከሞት መነሳቱን ለሕዝቡ እየተናገሩ ስለነበረ የሃይማኖት መሪዎቹ በጣም ተናደዱ። ስለዚህ ያዟቸውና እስር ቤት አስገቧቸው።

በሚቀጥለው ቀን የሃይማኖት መሪዎቹ አንድ ትልቅ ስብሰባ አደረጉ። ጴጥሮስና ዮሐንስ እንዲሁም የፈወሱት ሰው ተጠሩ። የሃይማኖት መሪዎቹ ‘ይህን ተአምር የሠራችሁት በማን ኃይል ነው?’ ብለው ጠየቋቸው።

ኢየሱስን ከሞት ባስነሳው በአምላክ ኃይል ነው ሲል ጴጥሮስ መለሰላቸው። ካህናቱ ይህን አስደናቂ ተአምር መካድ ስለማይችሉ ምን እንደሚያደርጉ ግራ ገባቸው። ስለዚህ ሐዋርያቱን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስለ ኢየሱስ እንዳይናገሩ አስጠንቅቀው ለቀቋቸው።

ቀናት እያለፉ ሲሄዱ ሐዋርያቱ ስለ ኢየሱስ መስበካቸውንና የታመሙትን መፈወሳቸውን ቀጠሉ። ስለ እነዚህ ተአምራት የሚወራው ወሬ በስፋት ተሰራጨ። በመሆኑም በኢየሩሳሌም አካባቢ በሚገኙ ከተሞች የሚኖሩ ሰዎች እንኳ ሳይቀሩ ሐዋርያት እንዲፈውሱላቸው የታመሙ ሰዎችን እየያዙ ይመጡ ነበር። ይህ የሃይማኖት መሪዎቹን እንዲቀኑ አደረጋቸው፤ ስለዚህ ሐዋርያቱን ያዟቸውና እስር ቤት አስገቧቸው። ሆኖም ታስረው ብዙ አልቆዩም።

ሥዕሉ ላይ እንደምታየው ሌሊት የአምላክ መልአክ የእስር ቤቱን በር ከፈተው። መልአኩ ‘ሂዱና በቤተ መቅደሱ ውስጥ ቆማችሁ ለሕዝቡ መናገራችሁን ቀጥሉ’ አላቸው። በሚቀጥለው ቀን ጠዋት የሃይማኖት መሪዎቹ ሐዋርያቱን እንዲያመጡ ሰዎችን ሲልኩ ሐዋርያቱ በቦታው አልነበሩም። በኋላ ሰዎቹ በቤተ መቅደስ ሲያስተምሩ አገኟቸውና ወደ ሳንሄድሪን አዳራሽ ይዘዋቸው መጡ።

የሃይማኖት መሪዎቹ ‘ስለ ኢየሱስ እንዳታስተምሩ አጥብቀን አዘናችሁ ነበር፤ እናንተ ግን ኢየሩሳሌምን በትምህርታችሁ ሞልታችኋታል’ አሏቸው። ሐዋርያቱ ‘ከሰው ይልቅ ለአምላክ ልንታዘዝ ይገባል’ ብለው መለሱላቸው። ስለዚህ ወዲያውኑ “ምሥራቹን” ማስተማራቸውን ቀጠሉ። ይህ ልንከተለው የሚገባ ጥሩ ምሳሌ አይደለም?