በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 108

ወደ ደማስቆ በሚወስደው መንገድ ላይ

ወደ ደማስቆ በሚወስደው መንገድ ላይ

መሬት ላይ የወደቀው ማን እንደሆነ ታውቃለህ? ሳውል ነው። ሳውል እስጢፋኖስን ሲወግሩ የነበሩትን ሰዎች ልብስ ሲጠብቅ የነበረው ሰው እንደሆነ አስታውስ። ይህን ደማቅ ብርሃን ተመልከት! እየተፈጸመ ያለው ነገር ምንድን ነው?

እስጢፋኖስ ከተገደለ በኋላ ሳውል የኢየሱስ ተከታዮች ዋነኛ አሳዳጅ ሆነ። በየቤቱ በመሄድ እየጎተተ አውጥቶ እስር ቤት ይጨምራቸው ነበር። ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ብዙዎቹ ወደ ሌሎች ከተሞች ሸሽተው በዚያ “ምሥራቹን” መስበክ ጀመሩ። ይሁን እንጂ ሳውል የኢየሱስን ተከታዮች ለማግኘት ወደ ሌሎች ከተሞች ሄደ። አሁን ወደ ደማስቆ እየተጓዘ ነው። ይሁን እንጂ እየሄዱ ሳለ የሚከተለው አስገራሚ ነገር አጋጠማቸው:-

ድንገት ከሰማይ አንድ ብርሃን በሳውል ዙሪያ ቦግ አለ። ሥዕሉ ላይ እንደምናየው ሳውል መሬት ላይ ወደቀ። ከዚያም አንድ ድምፅ ‘ሳውል፣ ሳውል! ለምን ታሳድደኛለህ?’ ከሳውል ጋር የነበሩት ሰዎች ብርሃኑን አይተዋል ድምፁንም ሰምተዋል፤ ሆኖም የተባለው ነገር ሊገባቸው አልቻለም ነበር።

ሳውል ‘ጌታ ሆይ፣ ማን ነህ?’ ሲል ጠየቀ።

‘አንተ የምታሳድደኝ ኢየሱስ ነኝ’ ሲል መለሰለት። ኢየሱስ ይህን ያለው ሳውል የኢየሱስን ተከታዮች ሲያሳድድ እሱን እንዳሳደደ ሆኖ ስለሚሰማው ነው።

በዚህ ጊዜ ሳውል ‘ጌታ ሆይ፣ ማድረግ ያለብኝ ነገር ምንድን ነው?’ ሲል ጠየቀ።

ኢየሱስም ‘ተነሳና ወደ ደማስቆ ሂድ፤ እዚያ ስትደርስ ምን ማድረግ እንዳለብህ ይነገርሃል’ አለው። ሳውል ተነስቶ ዓይኑን ሲገልጥ ምንም ነገር ማየት አልቻለም። ታውሮ ነበር! ስለዚህ አብረውት የነበሩት ሰዎች እጁን ይዘው እየመሩ ወደ ደማስቆ ወሰዱት።

ኢየሱስ በደማስቆ ከነበሩት ደቀ መዛሙርቱ አንዱን ‘ሐናንያ ሆይ፣ ተነሳ። ቀጥተኛ ወደሚባለው መንገድ ሂድ። በይሁዳ ቤትም ሳውል የሚባል ሰው ጠይቅ። ልዩ አገልጋዬ እንዲሆን መርጬዋለሁ’ አለው።

ሐናንያም የተባለውን አደረገ። ሳውልን ሲያገኘው እጁን ጫነበትና ‘ጌታ እንደገና ማየት እንድትችልና በመንፈስ ቅዱስ እንድትሞላ ወደ አንተ ላከኝ’ አለው። ወዲያውኑ ከሳውል ዓይኖች ላይ ቅርፊት የመሰለ ነገር ወደቀና እንደገና ማየት ቻለ።

ሳውል ለብዙ አገር ሕዝቦች በመስበክ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል። ይህ ሰው ሐዋርያው ጳውሎስ የሚል ስም ተሰጥቶታል። ስለ እርሱ ብዙ የምንማረው ነገር ይኖራል። ከዚያ በፊት ግን አምላክ ጴጥሮስን ምን እንዲያደርግ እንደላከው እንመልከት