በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ አምስት

ልጆቻችሁን ከሕፃንነታቸው ጀምሮ አሠልጥኗቸው

ልጆቻችሁን ከሕፃንነታቸው ጀምሮ አሠልጥኗቸው

1, 2. ወላጆች ልጆቻቸውን በሚያሳድጉበት ጊዜ ከማን እርዳታ ለማግኘት መጣር ይኖርባቸዋል?

ከዛሬ 3,000 ዓመታት ገደማ በፊት አንድ ወላጅ “ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው” ሲል አድናቆቱን በደስታ ስሜት ገልጿል። (መዝሙር 127:​3) በእርግጥም ወላጅነት የሚያስገኘው ደስታ ትዳር የያዙ አብዛኞቹ ሰዎች የሚያገኙት ውድ የሆነ የአምላክ ስጦታ ነው። ይሁን እንጂ ወላጆች ከደስታው ጋር ተያይዘው የሚመጡ ኃላፊነቶች እንዳሉም ወዲያው መገንዘባቸው አይቀርም።

2 በተለይ በአሁኑ ጊዜ ልጆችን ማሳደግ ከባድ ኃላፊነት ነው። ያም ሆኖ ግን ብዙዎች ይህን ኃላፊነት በተሳካ ሁኔታ ተወጥተዋል፤ በመንፈስ አነሳሽነት የጻፈው መዝሙራዊ ይህን ኃላፊነት በተሳካ ሁኔታ መወጣት የሚቻልበትን መንገድ ሲጠቁም “እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ፣ ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ” ሲል ተናግሯል። (መዝሙር 127:​1) የይሖዋን መመሪያዎች በጥብቅ ከተከተላችሁ የተሻላችሁ ወላጆች ትሆናላችሁ። መጽሐፍ ቅዱስ “በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፣ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ” ይላል። (ምሳሌ 3:​5) ልጅ የማሳደግን የ20 ዓመት ፕሮጀክት ስትያያዙት የይሖዋን ምክር ለመስማት ፈቃደኞች ናችሁን?

የመጽሐፍ ቅዱስን አመለካከት መያዝ

3. አባቶች ልጆችን በማሳደግ ረገድ ምን ኃላፊነት አለባቸው?

3 በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ብዙ አባ ወራዎች ልጆችን ማሠልጠን በአብዛኛው የሴቶች ሥራ እንደሆነ አድርገው ያስባሉ። እርግጥ ነው፣ የአምላክ ቃል የአባት ዋነኛ ድርሻ መሠረታዊ የሆኑ ነገሮችን በማሟላት ቤተሰቡን ማስተዳደር እንደሆነ ይናገራል። ይሁን እንጂ ከዚህም በተጨማሪ በቤት ውስጥ የራሱ ኃላፊነቶች እንዳሉት ይገልጻል። መጽሐፍ ቅዱስ “በስተ ሜዳ ሥራህን አሰናዳ፣ ስለ አንተ በእርሻ አዘጋጃት፤ ከዚያም በኋላ ቤትህን ሥራ” ሲል ይናገራል። (ምሳሌ 24:​27) በአምላክ አመለካከት መሠረት አባትና እናት ልጆችን በማሠልጠን ረገድ የጋራ ኃላፊነት አለባቸው።​—⁠ምሳሌ 1:​8, 9

4. ወንዶች ልጆች ከሴቶች ልጆች የላቁ እንደሆኑ አድርገን መመልከት የሌለብን ለምንድን ነው?

4 ልጆቻችሁን የምትመለከቷቸው እንዴት ነው? በየጊዜው የሚወጡት ዘገባዎች እንደሚያሳዩት በእስያ የሚገኙ ወላጆች “በአብዛኛው ሴት ልጅ መውለድ አይፈልጉም።” በላቲን አሜሪካ በአሁኑ ጊዜም እንኳ “የተማሩ ናቸው የሚባሉ ቤተሰቦች” ሳይቀሩ ለወንዶች ልጆች እንደሚያደሉ ይነገራል። ሐቁ ግን ከዚህ የተለየ ነው፤ ልጃገረዶች ዝቅተኛ ደረጃ የሚሰጣቸው ልጆች አይደሉም። የታወቀው የጥንት አባት ያዕቆብ እስከዚያን ጊዜ ድረስ ተወልደው የነበሩትን ሴቶች ልጆቹን ጨምሮ ዝርያዎቹን በጠቅላላ “እግዚአብሔር ለእኔ . . . የሰጠኝ ልጆች” ሲል ገልጿቸዋል። (ዘፍጥረት 33:​1-5፤ 37:​35) ኢየሱስም ልክ እንደዚሁ ወደ እሱ ቀርበው የነበሩትን “ሕፃናት” (ወንዶችንም ሴቶችንም) በሙሉ ባርኳቸዋል። (ማቴዎስ 19:​13-15) ኢየሱስ የይሖዋን አመለካከት እንዳንጸባረቀ እርግጠኞች መሆን እንችላለን።​—⁠ዘዳግም 16:​14

5. አንድ ባልና ሚስት ምን ያህል ልጆች ቢወልዱ የተሻለ እንደሚሆን በሚነጋገሩበት ጊዜ የትኞቹን ነገሮች ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርባቸዋል?

5 እናንተ በምትኖሩበት ማኅበረሰብ አንዲት ሴት ብዙ ልጆች እንድትወልድ ይፈለጋልን? አንድ ባልና ሚስት ምን ያህል ልጆች መውለድ እንዳለባቸው የመወሰን መብት ያላቸው ራሳቸው ናቸው። ወላጆች ብዙ ልጆች ወልደው በኋላ በሚገባ መመገብ፣ ማልበስና ማስተማር ቢያቅታቸውስ? ስለዚህ ምን ያህል ልጆች መውለድ እንዳለባቸው በሚወስኑበት ጊዜ ይህን ጉዳይ ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርባቸዋል። የወለዷቸውን ልጆች በሙሉ የማስተዳደር አቅም የሌላቸው አንዳንድ ባልና ሚስቶች ከልጆቻቸው መካከል የተወሰኑትን እንዲያሳድጉላቸው ለዘመዶቻቸው ይሰጣሉ። እንዲህ ማድረጉ ጥሩ ነውን? በፍጹም። ወላጆች እንዲህ ማድረጋቸው ለልጆቻቸው ካለባቸው ኃላፊነት ነፃ አያደርጋቸውም። መጽሐፍ ቅዱስ “ለእርሱ ስለ ሆኑት ይልቁንም ስለ ቤተ ሰዎቹ የማያስብ ማንም ቢሆን፣ ሃይማኖትን የካደ ከማያምንም ሰው ይልቅ የከፋ ነው” ይላል። (1 ጢሞቴዎስ 5:​8) ኃላፊነት የሚሰማቸው ባልና ሚስቶች ‘የራሳቸው ለሆኑት ሁሉ አስፈላጊ የሆነውን ነገር’ ማሟላት እንዲችሉ ‘የቤተሰባቸውን’ ቁጥር ለመመጠን ጥረት ያደርጋሉ። ቤተሰባቸውን ለመመጠን የወሊድ መቆጣጠሪያ ዘዴ መጠቀም ይችላሉን? ይህም ቢሆን የእነርሱ የግል ውሳኔ ነው፤ ይህን ዘዴ ለመጠቀም ከመረጡም በየትኛው የወሊድ መቆጣጠሪያ ቢጠቀሙ የተሻለ ሊሆን እንደሚችል የሚወስኑትም ራሳቸው ናቸው። “እያንዳንዱ የራሱን ሸክም መሸከም አለበት።” (ገላትያ 6:​51980 ትርጉም) ይሁን እንጂ ማንኛውንም ዓይነት ውርጃ ሊያስከትል የሚችል የወሊድ መቆጣጠሪያ ከመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር ይጋጫል። “የሕይወት ምንጭ” ይሖዋ አምላክ ነው። (መዝሙር 36:​9) ስለዚህ አንድን ሕይወት ከተጸነሰ በኋላ ማጨናገፍ ይሖዋን እንደ ማቃለል የሚቆጠር ከመሆኑም በላይ ከነፍስ ግድያ ወንጀል ተለይቶ የሚታይ አይደለም።​—⁠ዘጸአት 21:​22, 23፤ መዝሙር 139:​16፤ ኤርምያስ 1:​5

ልጃችሁ የሚያስፈልጉትን ነገሮች ማሟላት

6. አንድ ልጅ ሥልጠና ሊሰጠው የሚገባው ከመቼ ጀምሮ ነው?

6 ምሳሌ 22:​6 “ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው [“አሠልጥነው፣” NW]” ይላል። ልጆችን ማሠልጠን ወላጆች ሊወጡት የሚገባ ሌላው ትልቅ ግዴታ ነው። ይሁን እንጂ ሥልጠናው መሰጠት ያለበት ከመቼ ጀምሮ ነው? ቀደም ብሎ መጀመር አለበት። ጢሞቴዎስ ‘ከሕፃንነቱ ጀምሮ’ ሥልጠና እንዳገኘ ሐዋርያው ጳውሎስ ገልጿል። (2 ጢሞቴዎስ 3:​15) እዚህ ቦታ ላይ የገባው የግሪክኛ ቃል አንድን ጨቅላ ሕፃን አልፎ ተርፎም ገና በማኅፀን ውስጥ ያለን ልጅ ሊያመለክት ይችላል። (ሉቃስ 1:​41, 44፤ ሥራ 7:​18-20) ስለዚህ ጢሞቴዎስ ሥልጠና ያገኘው በጣም ትንሽ ልጅ ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ ነው፤ ይህም ተገቢ ነበር። የሕፃንነት ዕድሜ ልጅን ማሠልጠን የሚጀመርበት ከሁሉ የተሻለ ጊዜ ነው። ጨቅላ ሕፃን እንኳ የእውቀት ጥማት አለው።

7. (ሀ) ሁለቱም ወላጆች ከሕፃን ልጃቸው ጋር የጠበቀ ዝምድና መመሥረታቸው አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? (ለ) በይሖዋና በአንድያ ልጁ መካከል ምን ዓይነት ዝምድና አለ?

7 አንዲት እናት “ከልጄ ጋር ፍቅር የያዘኝ ገና እንደተወለደ ነው” ስትል ገልጻለች። አብዛኞቹ እናቶች እንደዚህ ናቸው። ይህ በእናቲቱና በሕፃኑ መካከል የሚፈጠረው አስደሳች ፍቅር ልጁ ከተወለደ በኋላ አብረው ብዙ ጊዜ ማሳለፍ ሲጀምሩ እየጠነከረ ይሄዳል። ልጅዋን ጡት ማጥባቷ ደግሞ ይህን ፍቅር ይበልጥ ያጠነክረዋል። (ከ⁠1 ተሰሎንቄ 2:​7 ጋር አወዳድር።) ልጅዋን መደባበሷና ማነጋገሯ የሕፃኑን ስሜታዊ ፍላጎት ለማሟላት በጣም ወሳኝ የሆነ ነገር ነው። (ከ⁠ኢሳይያስ 66:​12 ጋር አወዳድር።) ይሁን እንጂ አባትየውስ? እሱም ከሕፃኑ ጋር የተቀራረበ ግንኙነት መመስረት ይኖርበታል። ይሖዋ ራሱ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ነው። በምሳሌ መጽሐፍ ውስጥ ይሖዋ በሚከተለው ሁኔታ ከተገለጸው አንድያ ልጁ ጋር ያለው ዝምድና ተጠቅሷል:- “እግዚአብሔር የመንገዱ መጀመሪያ አደረገኝ፣ . . . ዕለት ዕለት ደስ አሰኘው ነበርሁ።” (ምሳሌ 8:​22, 30፤ ዮሐንስ 1:​14) በተመሳሳይም አንድ ጥሩ አባት ልጁ ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ ሞቅ ያለ ፍቅራዊ ዝምድና መመሥረት ይችላል። “ፍቅራችሁን ደጋግማችሁ ግለጹላቸው” ሲል አንድ ወላጅ ተናግሯል። “ስለታቀፈ ወይም ስለተሳመ የሞተ ልጅ የለም።”

8. ወላጆች በተቻለ መጠን ወዲያውኑ ለሕፃናት ምን ዓይነት የአእምሮ ማነቃቂያ ሊሰጧቸው ይገባል?

8 ይሁን እንጂ ሕፃናት ከዚህም በተጨማሪ ሌላ የሚያስፈልጋቸው ነገር አለ። ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ አእምሯቸው እውቀት ለመሰብሰብ ዝግጁ ነው፤ ዋነኛ የእውቀት ምንጭ ሆነው የሚያገለግሉት ደግሞ ወላጆች ናቸው። ቋንቋን እንደ ምሳሌ እንውሰድ። አንድ ልጅ የመናገርና የማንበብ ችሎታው “በመጀመሪያዎቹ ዓመታት ከወላጆቹ ጋር በሚኖረው ግንኙነት ላይ የተመካ ነው የሚል እምነት እንዳለ” ተመራማሪዎች ይናገራሉ። ልጃችሁን ከሕፃንነቱ ጀምሮ አነጋግሩት፤ ጽሑፎችም አንብቡለት። ወዲያውኑ ልጁ እናንተን ለመኮረጅ ጥረት ማድረግ ይጀምራል፤ ብዙም ሳይቆይ ልጁን ፊደል ማስተማር የምትችሉበት ደረጃ ላይ ትደርሳላችሁ። በዚህ መንገድ ትምህርት ቤት ከመግባቱ በፊት የማንበብ ችሎታ ሊያዳብር ይችላል። በተለይ በአገራችሁ የአስተማሪዎች እጥረት ካለና በአንድ ክፍል ውስጥ ብዙ ተማሪዎች ተጨናንቀው የሚማሩ ከሆነ አስቀድማችሁ ልጃችሁን በዚህ መንገድ ማሠልጠናችሁ ጠቃሚ ነው።

9. ወላጆች ሊያስታውሱት የሚገባ ከሁሉ የላቀ ግብ ምንድን ነው?

9 ክርስቲያን ወላጆች ከሁሉ ይበልጥ የሚያሳስባቸው የልጃቸውን መንፈሳዊ ፍላጎት የማሟላቱ ጉዳይ ነው። (ዘዳግም 8:​3ን ተመልከት።) ይህን የሚያደርጉበት ዓላማ ምንድን ነው? ልጃቸው የክርስቶስ ዓይነት ስብዕና እንዲያዳብር፣ በሌላ አነጋገር “አዲሱን ሰው” እንዲለብስ ነው። (ኤፌሶን 4:​24) ይህን ማድረግ እንዲችሉ ደግሞ ትክክለኛ የግንባታ ቁሳቁሶችንና ትክክለኛ የግንባታ ዘዴዎችን በሚገባ ማጥናት አለባቸው።

በልጆቻችሁ አእምሮ ውስጥ እውነትን ቅረጹ

10. ልጆች ምን ዓይነት ባሕርያትን ማዳበር ያስፈልጋቸዋል?

10 የአንድ ሕንፃ የጥራት ደረጃ በአብዛኛው ለግንባታ በዋሉት ቁሳቁሶች ዓይነት ላይ የተመካ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያናዊ ባሕርያትን ለመገንባት የሚያገለግሉት ከሁሉ የተሻሉ የግንባታ ቁሳቁሶች ‘ወርቅ፣ ብርና የከበሩ ድንጋዮች’ እንደሆኑ ገልጿል። (1 ቆሮንቶስ 3:​10-12) እነዚህ ነገሮች እንደ እምነት፣ ጥበብ፣ ማስተዋል፣ ታማኝነት፣ አክብሮትና ለይሖዋና ለሕጎቹ ፍቅራዊ አድናቆት ማሳየትን የመሳሰሉ ባሕርያትን ያመለክታሉ። (መዝሙር 19:​7-11፤ ምሳሌ 2:​1-6፤ 3:​13, 14) ወላጆች ልጆቻቸው እነዚህን ባሕርያት ከሕፃንነታቸው ጀምሮ እንዲያዳብሩ ሊረዷቸው የሚችሉት እንዴት ነው? ከረጅም ጊዜ በፊት የተሰጠውን የሚከተለውን ሥርዓት በመከተል ነው።

11. እስራኤላውያን ወላጆች ልጆቻቸው አምላካዊ ባሕርያትን እንዲያዳብሩ ይረዷቸው የነበረው እንዴት ነው?

11 የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር ከመግባቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት ይሖዋ እስራኤላውያን ወላጆችን እንዲህ ብሏቸው ነበር:- “እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ። በልጆችህም አእምሮ ውስጥ ቅረጸው፣ በቤትህም ስትቀመጥ፣ በመንገድም ስትሄድ፣ ስትተኛም፣ ስትነሣም ተጫወተው።” (ዘዳግም 6:​6, 7 NW) አዎ፣ ወላጆች ለልጆቻቸው ምሳሌ፣ ጓደኛና አስተማሪ መሆን ያለባቸው ከመሆኑም በላይ ከልጆቻቸው ጋር የሐሳብ ልውውጥ ማድረግ አለባቸው።

12. ወላጆች ጥሩ ምሳሌ መሆናቸው በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

12 ምሳሌ ሁኑ። ይሖዋ በመጀመሪያ “ይህን ቃል በልብህ ያዝ” ብሏል። ከዚያም “ለልጆችህም አስተምረው” ሲል አክሎ ተናግሯል። ስለዚህ አምላካዊ ባሕርያት በመጀመሪያ በወላጅ ልብ ውስጥ ጠልቀው መግባት አለባቸው። ወላጆች እውነትን መውደድና በእውነት መንገድ መመላለስ ይኖርባቸዋል። የልጃቸውን ልብ መንካት የሚችሉት እንዲህ ካደረጉ ብቻ ነው። (ምሳሌ 20:​7) ለምን? ምክንያቱም ልጆች ይበልጥ ተጽዕኖ የሚያሳድርባቸው የሚሰሙት ነገር ሳይሆን የሚያዩት ነገር ነው።​—⁠ሉቃስ 6:​40፤ 1 ቆሮንቶስ 11:​1

13. ክርስቲያን ወላጆች ለልጆቻቸው ትኩረት በመስጠት ረገድ የኢየሱስን ምሳሌ መኮረጅ የሚችሉት እንዴት ነው?

13 ጓደኛ ሁኑ። ይሖዋ እስራኤላውያን ወላጆችን ‘በቤታችሁ ስትቀመጡና በመንገድ ስትሄዱ ከልጆቻችሁ ጋር ተጫወቱ’ ብሏቸው ነበር። ይህም ወላጆች ምንም ያህል ሥራ የሚበዛባቸው ቢሆን ከልጆቻቸው ጋር የተወሰነ ጊዜ ማሳለፍ ይጠይቅባቸዋል። ኢየሱስ ከልጆችም ጋር ጊዜ ማሳለፍ እንዳለበት ተሰምቶት እንደነበረ ከሁኔታው መረዳት ይቻላል። በምድራዊ አገልግሎቱ መገባደጃ ላይ “እንዲዳስሳቸውም ሕፃናትን ወደ እርሱ አመጡ።” ኢየሱስ የሰጠው ምላሽ ምን ነበር? “አቀፋቸውም እጁንም ጭኖ ባረካቸው።” (ማርቆስ 10:​13, 16) እስቲ አስቡት፣ የኢየሱስ ምድራዊ ሕይወት እየተገባደደ የነበረበት ወቅት ነው። ያም ሆኖ ግን ጊዜውንና ፍቅሩን አልነፈጋቸውም። እንዴት ያለ ግሩም ትምህርት ነው!

14. ወላጆች ከልጃቸው ጋር ጊዜ ማሳለፋቸው ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?

14 ከልጆቻችሁ ጋር የሐሳብ ልውውጥ አድርጉ። ከልጃችሁ ጋር አብራችሁ ጊዜ ማሳለፋችሁ የሐሳብ ልውውጥ ማድረግ እንድትችሉ ይረዳችኋል። የሐሳብ ልውውጥ ባደረጋችሁ መጠን የዚያኑ ያህል የልጃችሁ ስብዕና ምን ያህል እየዳበረ እንዳለ በይበልጥ ትገነዘባላችሁ። ይሁን እንጂ የሐሳብ ልውውጥ ማድረግ ማለት መናገር ማለት ብቻ እንዳልሆነ አስታውሱ። “የማዳመጥን ችሎታ ማዳበር ነበረብኝ” ስትል አንዲት በብራዚል የምትኖር እናት ተናግራለች። “ከልቤ የማዳመጥን ልማድ ማዳበር አስፈልጎኛል።” ልጅዋ ስሜቱን ለእርሷ ማካፈል በመጀመሩ ትዕግሥቷ ጥሩ ውጤት ሊያስገኝ ችሏል።

15. መዝናኛን በተመለከተ የትኞቹን አስፈላጊ ነገሮች ማስታወስ ይገባል?

15 ልጆች ‘የሚስቁበትና የሚጫወቱበት፣’ ማለትም የሚዝናኑበት ጊዜ ያስፈልጋቸዋል። (መክብብ 3:​1, 4፤ ዘካርያስ 8:​5) ወላጆችና ልጆች አብረው መዝናናታቸው በጣም ጠቃሚ ነው። በብዙ ቤተሰቦች እንደ መዝናኛ የሚቆጠረው ነገር ቴሌቪዥን መመልከት መሆኑ በጣም ያሳዝናል። አንዳንድ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ሊያዝናኑ ቢችሉም እንኳ ብዙዎቹ ጥሩ ሥነ ምግባርን የሚያበላሹ ናቸው። በተጨማሪም ቴሌቪዥን መመልከት በቤተሰብ መካከል ጥሩ የሐሳብ ልውውጥ እንዳይኖር እንቅፋት ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ለምን ከልጆቻችሁ ጋር ሌሎች አስደሳችና ጠቃሚ የሆኑ ነገሮችን አታደርጉም? መዝሙር መዘመር፣ የተለያዩ ጨዋታዎችን መጫወት፣ ከጓደኞቻችሁ ጋር ጊዜ ማሳለፍ ወይም ደግሞ አስደሳች ቦታዎችን መጎብኘት ትችላላችሁ። እንዲህ ዓይነቶቹ እንቅስቃሴዎች የሐሳብ ልውውጥ እንድታደርጉ ይረዷችኋል።

16. ወላጆች ልጆቻቸውን ስለ ይሖዋ ምን ማስተማር አለባቸው? ይህን ማድረግ ያለባቸውስ እንዴት ነው?

16 አስተማሪ ሁኑ። ይሖዋ “[ይህን ቃል] በልጆችህ አእምሮ ውስጥ ቅረጸው” ብሏል። በጥቅሱ ዙሪያ ያለው ሐሳብ ምን እና እንዴት እንደምታስተምሯቸው ይጠቁማችኋል። በመጀመሪያ “አንተም አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም ኃይልህ ውደድ።” (ዘዳግም 6:​5) ከዚያም “ይህን ቃል . . . አስተምረው።” (በሰያፍ የጻፍነው እኛ ነን።) ለይሖዋና ለሕጎቹ ልባዊ ፍቅር እንዲያድርባቸው የሚያደርግ ትምህርት ስጧቸው። (ከዕብራውያን 8:​10 ጋር አወዳድር።) “መቅረጽ” ተብሎ የተተረጎመው ኢንከልኬት የተባለው የእንግሊዝኛ ቃል እየደጋገሙ ማስተማር ማለት ነው። ስለዚህ ይሖዋ ልጆቻችሁ አምላካዊ ባሕርይ እንዲያዳብሩ መርዳት የምትችሉበት ዋነኛው መንገድ ዘወትር ስለ እሱ በመናገር እንደሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ መግለጹ ነው። ይህ ደግሞ ከልጆቻችሁ ጋር ቋሚ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማድረግን ይጨምራል።

17. ወላጆች በልጃቸው ልብ ውስጥ ምን ነገር ማዳበር ሊያስፈልጋቸው ይችላል? ለምንስ?

17 እውቀትን በልጆች ልብ ውስጥ መትከል ቀላል እንዳልሆነ አብዛኞቹ ወላጆች ያውቃሉ። ሐዋርያው ጴጥሮስ መሰል ክርስቲያኖችን “አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ” ሲል አጥብቆ መክሯቸዋል። (1 ጴጥሮስ 2:​2) “ተመኙ” የሚለው አነጋገር ብዙዎች የመንፈሳዊ ነገሮች ጥማት እንደሌላቸው የሚያመለክት ነው። ወላጆች ልጃቸው እንዲህ ዓይነት ምኞት እንዲኖረው ለማድረግ የሚያስችሉ መንገዶች መፈለግ ሊኖርባቸው ይችላል።

18. ወላጆች ሊኮርጁአቸው የሚገቡ አንዳንድ የኢየሱስ የማስተማሪያ ዘዴዎች ምንድን ናቸው?

18 ኢየሱስ የሰዎችን ልብ ለመንካት በምሳሌዎች ይጠቀም ነበር። (ማርቆስ 13:​34፤ ሉቃስ 10:​29-37) ይህ የማስተማሪያ ዘዴ በተለይ በልጆች ላይ ጥሩ ውጤት ያመጣል። የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች መማሪያ መጽሐፌ በተባለው መጽሐፍ ላይ ያሉትን ዓይነት ማራኪና አስደሳች ታሪኮች በመጠቀም የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶችን አስተምሯቸው። * ልጆቹም እንዲሳተፉ አድርጉ። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጹ ክንውኖችን በሥዕልና በድራማ መልክ በመሥራት የራሳቸውን የፈጠራ ችሎታ እንዲጠቀሙ አድርጓቸው። ኢየሱስ በጥያቄዎችም ይጠቀም ነበር። (ማቴዎስ 17:​24-27) በቤተሰብ ጥናታችሁ ወቅት ይህን የኢየሱስ ዘዴ ተጠቀሙበት። አንድን የአምላክ ሕግ እንዲሁ በደፈናው ከመግለጽ ይልቅ ይሖዋ ይህን ሕግ የሰጠው ለምንድን ነው? ይህን ሕግ መጠበቃችን ምን ያስገኝልናል? ይህን ሕግ ባንጠብቅ ምን ይደርስብናል? የሚሉትን ዓይነት ጥያቄዎች ጠይቋቸው። እነዚህን የመሳሰሉ ጥያቄዎች አንድ ልጅ የአምላክ ሕጎች ተግባራዊና ጠቃሚ መሆናቸውን እንዲገነዘብ ይረዱታል።​—⁠ዘዳግም 10:​13

19. ወላጆች ከልጆቻቸው ጋር ባላቸው ግንኙነት የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች ከተከተሉ ልጆቻቸው የትኞቹን ታላላቅ ጥቅሞች ማግኘት ይችላሉ?

19 ለልጃችሁ ምሳሌ፣ ጓደኛና አስተማሪ በመሆን እንዲሁም ከልጃችሁ ጋር የሐሳብ ልውውጥ በማድረግ ከሕፃንነቱ ጀምሮ ከይሖዋ አምላክ ጋር የተቀራረበ የግል ዝምድና እንዲኖረው ልትረዱት ትችላላችሁ። ይህ ዝምድና ልጃችሁ ክርስቲያን በመሆኑ እንዲደሰት ያደርገዋል። የእኩዮች ተጽዕኖና ፈተናዎች ሲያጋጥሙት ከእምነቱ ጋር በሚስማማ መንገድ ለመመላለስ ጥረት ያደርጋል። ሁልጊዜ ይህን ውድ ዝምድና ከፍ አድርጎ እንዲመለከት እርዱት።​—⁠ምሳሌ 27:​11

ተግሣጽ የግድ አስፈላጊ ነው

20. ተግሣጽ ምንድን ነው? መሰጠት ያለበትስ እንዴት ነው?

20 ተግሣጽ አእምሮንና ልብን የሚያርም ማሠልጠኛ ነው። ልጆች ዘወትር ተግሣጽ ሊሰጣቸው ይገባል። አባቶች “[ልጆቻቸውን] በጌታ ምክርና በተግሣጽ” እንዲያሳድጉ ጳውሎስ ምክር ሰጥቷል። (ኤፌሶን 6:​4) ወላጆች ልክ እንደ ይሖዋ ፍቅራዊ በሆነ መንገድ ተግሣጽ መስጠት ይኖርባቸዋል። (ዕብራውያን 12:​4-11) ፍቅራዊ የሆነ ተግሣጽ አንድን ነጥብ ግልጽና አሳማኝ በሆነ መንገድ በማስረዳት ሊሰጥ ይችላል። በመሆኑም “ተግሣጽን ስሙ” ተብለናል። (ምሳሌ 8:​33) ተግሣጽ መሰጠት ያለበት እንዴት ነው?

21. ወላጆች ልጆቻቸውን ሲገሥጹ የትኞቹን መሠረታዊ ሥርዓቶች ማስታወስ ይኖርባቸዋል?

21 አንዳንድ ወላጆች ለልጆች ተግሣጽ መስጠት ማለት በልጆቻቸው ላይ በኃይል መጮኽ፣ መቆጣት፣ አልፎ ተርፎም መሳደብ ማለት ብቻ እንደሆነ አድርገው ያስባሉ። ጳውሎስ ስለዚሁ ጉዳይ ሲናገር “አባቶች ሆይ፣ ልጆቻችሁን . . . አታስቆጡአቸው” ሲል አስጠንቅቋል። (ኤፌሶን 6:​4) ሁሉም ክርስቲያኖች ‘ለሰው ሁሉ ገር እንዲሆኑና የሚቃወሙትን በየዋህነት እንዲቀጡ’ ጥብቅ ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል። (2 ጢሞቴዎስ 2:​24-26) ክርስቲያን ወላጆች ጥብቅ የመሆንን አስፈላጊነት የሚገነዘቡ ቢሆንም እንኳ ልጆቻቸውን በሚገሥጹበት ጊዜ እነዚህን ቃላት ለማስታወስ ይጥራሉ። እርግጥ፣ አንዳንድ ጊዜ በቃል ከሚሰጠው ተግሣጽ በተጨማሪ ቅጣትም ሊያስፈልግ ይችላል።​—⁠ምሳሌ 22:​15

22. አንድ ልጅ መቀጣት ካለበት ምን ነገር እንዲገነዘብ መርዳት ይገባል?

22 የተለያዩ ልጆች የተለያየ ዓይነት ተግሣጽ ሊያስፈልጋቸው ይችላል። አንዳንዶቹ ልጆች ‘በቃል ብቻ የሚታረሙ’ አይደሉም። እንዲህ ዓይነቶቹ ልጆች ባለመታዘዛቸው ምክንያት አልፎ አልፎ የሚሰጣቸው ቅጣት ሕይወት አድን ሊሆንላቸው ይችላል። (ምሳሌ 17:​10፤ 23:​13, 14፤ 29:​19) ይሁን እንጂ አንድ ልጅ በሚቀጣበት ጊዜ የተቀጣበትን ምክንያት ማወቅ ይኖርበታል። “በትርና ተግሣጽ ጥበብን ይሰጣሉ።” (ምሳሌ 29:​15፤ ኢዮብ 6:​24) ከዚህም በተጨማሪ ቅጣቱ ገደብ ሊኖረው ይገባል። ይሖዋ ሕዝቡን “በመጠን እቀጣሃለሁ” ብሏቸው ነበር። (ኤርምያስ 46:​28፤ በሰያፍ የጻፍነው እኛ ነን።) ሰውነቱ ሰንበር እስኪያወጣና እስኪጎዳ ድረስ ልጅን በኃይል መግረፍን ወይም መደብደብን መጽሐፍ ቅዱስ ፈጽሞ አይደግፍም።​—⁠ምሳሌ 16:​32

23. አንድ ልጅ ወላጆቹ ሲቀጡት ምን ነገር ለመረዳት መቻል ይኖርበታል?

23 ይሖዋ ሕዝቡን እንደሚገሥጻቸው ባስጠነቀቃቸው ጊዜ በመጀመሪያ “እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ” ብሏቸው ነበር። (ኤርምያስ 46:​28) እንደዚሁም ተገቢ በሆነ በማንኛውም መንገድ የሚሰጥ የወላጅ ተግሣጽ ልጁ ፈጽሞ እንደተጠላ ሆኖ እንዲሰማው የሚያደርግ መሆን የለበትም። (ቆላስይስ 3:​21) ከዚህ ይልቅ ልጁ ተግሣጽ የተሰጠው ወላጁ ‘ከእሱ ጋር’ ማለትም ከእሱ ጎን በመሆኑ ምክንያት እንደሆነ እንዲገነዘብ ማድረግ ያስፈልጋል።

ልጃችሁን ከአደጋ ጠብቁ

24, 25. በአሁኑ ጊዜ ልጆችን ከየትኛው በጣም አስፈሪ የሆነ ነገር መጠበቅ ያስፈልጋል?

24 ብዙ ትልልቅ ሰዎች የልጅነት ትዝታቸው በጣም አስደሳች ነው። የልጅነት ሕይወታቸው ምንም ስጋት የሌለበት እንደነበር ያስታውሳሉ፤ ምንም ዓይነት ሁኔታ ቢፈጠር ወላጆቻቸው እንደሚጠብቋቸውና እንደሚንከባከቧቸው ሙሉ ትምክህት ነበራቸው። ወላጆች ልጆቻቸው እንዲህ ዓይነት ስሜት እንዲሰማቸው ይፈልጋሉ። ይሁን እንጂ በአሁኑ ጊዜ ባለው የተበላሸ ዓለም ውስጥ ልክ ቀደም ባሉት ጊዜያት እንደነበረው ልጆች ደህንነታቸው ተጠብቆ እንዲያድጉ ማድረግ ቀላል አይደለም።

25 ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየተስፋፋ የመጣው አንዱ በጣም አስፈሪ የሆነ ነገር በልጆች ላይ የሚፈጸመው ወሲባዊ ጥቃት ነው። በማሌዥያ ወሲባዊ ጥቃት የሚፈጸምባቸው ልጆች ቁጥር በአሥር ዓመት ውስጥ በአራት እጥፍ አድጓል። በጀርመን በየዓመቱ ወደ 300,000 የሚጠጉ ልጆች በጾታ የመነወር ድርጊት የሚፈጸምባቸው ሲሆን በደቡብ አሜሪካ በሚገኝ አንድ አገር ውስጥ በተካሄደው ጥናት ደግሞ ይህ ድርጊት የሚፈጸምባቸው ልጆች ቁጥር በጣም አስደንጋጭ ሆኖ ተገኝቷል። በዚህ አገር በአንድ ዓመት ውስጥ 9,000,000 የሚያክሉ ሕፃናት በጾታ እንደሚነወሩ ተገምቷል! የሚያሳዝነው ደግሞ ከእነዚህ ልጆች መካከል አብዛኞቹ የተነወሩት በራሳቸው ቤት ውስጥ፣ በሚያውቋቸውና በሚያምኗቸው ሰዎች ነው። ወላጆች ለልጆቻቸው ጠንካራ ከለላ ሊሆኑላቸው ይገባል። ወላጆች ልጆቻቸውን ከዚህ ድርጊት ሊጠብቋቸው የሚችሉት እንዴት ነው?

26. የልጆች ደህንነት እንዲጠበቅ ማድረግ የሚቻልባቸው አንዳንድ መንገዶች ምንድን ናቸው? እውቀት አንድን ልጅ ሊጠብቀው የሚችለውስ እንዴት ነው?

26 በተሞክሮ እንደታየው ብዙውን ጊዜ ለወሲባዊ ጥቃት የሚጋለጡት ስለ ጾታ ምንም የማያውቁ ልጆች በመሆናቸው አንዱ ትልቁ የመከላከያ እርምጃ ገና ትንንሽ እያሉም እንኳ ልጆችን ስለ ጾታ ማስተማር ነው። እውቀት “ከክፉ መንገድ . . . ጠማማ ነገርን ከሚናገሩም ሰዎች” ሊጠብቅ ይችላል። (ምሳሌ 2:​10-12) ሊጠብቅ የሚችለው የትኛው እውቀት ነው? ከአደጋ ሊጠብቅ የሚችለው በሥነ ምግባር ደረጃ ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር የሚገልጹትን የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ማወቁ ነው። በተጨማሪም አንድ ልጅ አንዳንድ ትልልቅ ሰዎች መጥፎ ነገር እንደሚሠሩና ሰዎች ትክክል ያልሆነ ነገር እንዲሠራ ሲጠይቁት መታዘዝ እንደሌለበት ማወቁ ከአደጋ ይጠብቀዋል። (ከ⁠ዳንኤል 1:​4, 8 እና 3:​16-18 ጋር አወዳድሩ።) እንዲህ ዓይነቱን ትምህርት መስጠት ያለባችሁ አንዴ ብቻ አይደለም። አብዛኞቹ ትንንሽ ልጆች አንድን ትምህርት በደንብ ማስታወስ እንዲችሉ ደጋግሞ ማስተማር ያስፈልጋል። ልጆች እያደጉ ሲሄዱ አባት ሴት ልጁ፣ እናት ደግሞ ወንድ ልጅዋ እርቃናቸውን በሚሆኑበት ጊዜ ገለል በማለት ፍቅራዊ አክብሮት ሊያሳዩአቸው ይገባል። በዚህ መንገድ ትክክል ለሆነው ነገር ጠንካራ አቋም እንዲኖራቸው ሊረዷቸው ይችላሉ። በተጨማሪም ልጆቻችሁ በጾታ እንዳይነወሩ መከላከል ከምትችሉባቸው ከሁሉ የተሻሉ መንገዶች አንዱ ወላጆች እንደ መሆናችሁ መጠን ልጆቻችሁን በቅርብ መከታተል ነው።

መለኮታዊ መመሪያ ለማግኘት ጣሩ

27, 28. ወላጆች ልጅ የማሳደግ ፈታኝ ሁኔታ ሲጋረጥባቸው ከሁሉ የላቀ እርዳታ ሊያገኙ የሚችሉት ከማን ነው?

27 ልጅን ከሕፃንነቱ ጀምሮ ማሠልጠን በጣም ፈታኝ እንደሆነ አይካድም፤ ሆኖም አማኝ የሆኑ ወላጆች ይህን ፈተና ብቻቸውን መጋፈጥ የለባቸውም። ጥንት በመሳፍንት ዘመን ማኑሄ የተባለ አንድ ሰው የልጅ አባት የሚሆንበት ጊዜ መቃረቡን ሲያውቅ የልጁን አስተዳደግ በተመለከተ ይሖዋ መመሪያ እንዲሰጠው ጠይቋል። ይሖዋም ላቀረባቸው ጸሎቶች መልስ ሰጥቶታል።​—⁠መሳፍንት 13:​8, 12, 24

28 ዛሬም በተመሳሳይ አማኝ የሆኑ ወላጆች ልጆቻቸውን በሚያሳድጉበት ጊዜ ይሖዋን በጸሎት ሊያነጋግሩት ይችላሉ። ወላጅ መሆን ከባድ ሥራ ነው፤ ሆኖም ታላላቅ በረከቶችን ያስገኛል። በሐዋይ የሚኖሩ አንድ ክርስቲያን ባልና ሚስት እንዲህ ሲሉ ተናግረዋል:- “ልጆቻችሁ አደገኛ ወደ ሆነው አፍላ የጉርምስና ዕድሜ ክልል ውስጥ ከመግባታቸው በፊት በሚገባ ማሠልጠን የምትችሉባቸው 12 ዓመታት አሏችሁ። የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች ሥራ ላይ ለማዋል ከፍተኛ ጥረት ካደረጋችሁ ይህ አደገኛ የዕድሜ ክልል ልጆቻችሁ ይሖዋን ከልባቸው ለማገልገል ቁርጥ ውሳኔ ሲያደርጉ በመመልከት ደስታና ሰላም የምታጭዱበት ጊዜ ይሆንላችኋል።” (ምሳሌ 23:​15, 16) ልጃችሁ እንዲህ ዓይነት ውሳኔ ላይ ሲደርስ እናንተም ልክ እንደ መዝሙራዊው “ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው” ብላችሁ በደስታ ስሜት ለመናገር ትገፋፋላችሁ።

^ አን.18 ኒው ዮርክ በሚገኘው የመጠበቂያ ግንብ መጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር የታተመ።