በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሁለት ዓይነት ሕይወት​—መናገር ያለብኝ ለምንድን ነው?

ሁለት ዓይነት ሕይወት​—መናገር ያለብኝ ለምንድን ነው?

ምዕራፍ 16

ሁለት ዓይነት ሕይወት​መናገር ያለብኝ ለምንድን ነው?

□ የአልኮል መጠጥ መጠጣት

□ ወላጆችህ መጥፎ እንደሆኑ ከሚያስቧቸው ወጣቶች ጋር መሆን

□ መጥፎ ሙዚቃ ማዳመጥ

□ መረን በለቀቁ ፓርቲዎች ላይ መገኘት

□ በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት

□ ዓመፅ ወይም ብልግና የሚንጸባረቅባቸው ፊልሞችን መመልከት አሊያም በዓመፅ የተሞሉ የቪዲዮ ጨዋታዎችን መጫወት

□ ጸያፍ ቃላት መጠቀም

ቀደም ባለው ገጽ ላይ የተዘረዘሩትን ነገሮች መለስ ብለህ ተመልከት። ከወላጆችህ ተደብቀህ እንደነዚህ ያሉትን ድርጊቶች ትፈጽማለህ? ከሆነ የምታደርገው ነገር ስህተት መሆኑን ሳታውቅ አትቀርም። እንዲያውም በምትፈጽመው መጥፎ ድርጊት የተነሳ ሕሊናህ ይወቅስህ ይሆናል። (ሮም 2:15) ያም ቢሆን ድርጊትህን ለወላጆችህ መናገር የሚለውን ነገር ማሰቡ ራሱ ይከብድህ ይሆናል። ለወላጆችህ መናገር የሚያስከትለውን ውጤት ስታስብ “ወላጆቼ ነግሬያቸው ከሚጎዱ ባያውቁት ይሻላል” የሚለው ሰበብ ምክንያታዊ ሊመስልህ ይችላል። ይሁን እንጂ እንዲህ ስታደርግ ሁለት ዓይነት ሕይወት እየመራህ እንደሆነ ተገንዝበሃል? እንዲህ ዓይነት አካሄድ ለመከተል ያነሳሳህ ምን ሊሆን ይችላል?

በራስ የመመራት ፍላጎት

ይዋል ይደር እንጂ “ሰው ከአባቱና ከእናቱ [መለየቱ]” እንደማይቀር መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። (ዘፍጥረት 2:24) ሴቶችን በተመለከተም እውነታው ተመሳሳይ ነው። በመሆኑም ትልቅ ሰው ለመሆን፣ በራስህ አስተሳሰብ ለመመራትና የራስህን ውሳኔ ለማድረግ መፈለግህ ያለ ነገር ነው። ይሁንና ወላጆች ጥበብ የጎደለው ወይም የተሳሳተ እንደሆነ የሚያስቡትን ድርጊት እንዳይፈጽሙ ልጆቻቸውን ሲከለክሏቸው አንዳንድ ወጣቶች ያምፃሉ።

በእርግጥ አንዳንድ ወላጆች ከሚገባው በላይ ጥብቅ ይመስሉ ይሆናል። ሜሮን የተባለች ወጣት “ፊልም የሚባል ነገር አናይም” በማለት ምሬቷን ገልጻለች። አክላም “አባቴ ማንኛውንም ዓይነት ሙዚቃ እንዳንሰማ ከልክሎናል ማለት እችላለሁ” ብላለች። አንዳንድ ወጣቶች የተጣለባቸው ገደብ ምክንያታዊ እንዳልሆነ ስለሚሰማቸው የበለጠ ነፃነት ያላቸው በሚመስሉት እኩዮቻቸው መቅናት ይጀምራሉ።

ታሚ የተባለች ወጣት፣ አንዳንዶች ሁለት ዓይነት ሕይወት የሚመሩበት ሌላው ምክንያት አብረዋቸው በሚማሩት ልጆች ዘንድ ተቀባይነት ለማግኘት ስለሚፈልጉ መሆኑን ገልጻለች። እንዲህ ስትል ታስታውሳለች፦ “በትምህርት ቤት ውስጥ ጸያፍ ቃላትን መጠቀም ጀመርኩ። እንዲህ በማድረጌ እንደ ሌሎቹ ልጆች እንደሆንኩ ተሰማኝ። ትንሽ ቆይቼ ደግሞ ማጨስ ጀመርኩ። በተጨማሪም ጥንብዝ ብዬ እስክሰክር ድረስ እጠጣ ነበር። ወላጆቼ ጥብቅ ስለሆኑና የፍቅር ጓደኛ እንዲኖረኝ ስለማይፈቅዱልኝ ከእነሱ ተደብቄ የወንድ ጓደኞች መያዝ ጀመርኩ።”

ፒተር የተባለ በአሥራዎቹ ዕድሜ የሚገኝ ወጣትም ተመሳሳይ ነገር አድርጎ ነበር። እንዲህ ብሏል፦ “ያደግሁት በይሖዋ ምሥክሮች ቤተሰብ ውስጥ ነው። ይሁንና ሌሎች እንዳያሾፉብኝ በጣም እፈራ ነበር።” ታዲያ ፒተር ምን አደረገ? “በሌሎች ዘንድ ተወዳጅ ለመሆን ጥረት ማድረግ ጀመርኩ። በሃይማኖታዊ በዓሎች ወቅት ምንም ዓይነት ስጦታ የማልቀበልበትን ምክንያት ለማስረዳት የውሸት ሰበብ እፈጥር ነበር።” ፒተር በትንሽ ነገር ታማኝነቱን ማጉደሉ ብዙም ሳይቆይ ከባድ የሥነ ምግባር ብልግና ወደ መፈጸም መራው።

የተሰወረ ነገር የለም

ሁለት ዓይነት ሕይወት መምራት ዛሬ የተጀመረ ነገር አይደለም። በጥንት ዘመን የኖሩ አንዳንድ እስራኤላውያንም ሳይታወቅባቸው ሁለት ዓይነት ሕይወት ለመምራት ሞክረው ነበር። ሆኖም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ በማለት አስጠንቅቋቸዋል፦ “ሐሳባቸውን ከእግዚአብሔር ለመደበቅ፣ ወደ ጥልቅ ጕድጓድ ለሚወርዱ ሥራቸውንም በጨለማ ለሚያከናውኑ፣ ‘ማን ያየናል? ማንስ ያውቅብናል’ ለሚሉ ወዮላቸው!” (ኢሳይያስ 29:15) እስራኤላውያን አምላክ መጥፎ ድርጊታቸውን እንደሚመለከት ዘንግተው ነበር። አምላክ እሱ በወሰነው ጊዜ ለጥፋታቸው ቅጣት እንዲቀበሉ አድርጓል።

ዛሬም ቢሆን ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። የሠራኸውን መጥፎ ድርጊት ከወላጆችህ መደበቅ ብትችልም እንኳ ከይሖዋ አምላክ እይታ ማምለጥ አትችልም። ዕብራውያን 4:13 “ከእሱ እይታ የተሰወረ አንድም ፍጥረት የለም፤ ይልቁንም ተጠያቂዎች በሆንበት በእሱ ዓይኖች ፊት ሁሉም ነገር የተራቆተና ገሃድ የወጣ ነው” ይላል። ታዲያ ለመደበቅ መሞከር ምን ጥቅም አለው? በሃይማኖታዊ ስብሰባዎች ላይ በምትገኝበት ጊዜ መንፈሳዊ ሰው መስለህ በመታየት አምላክን ማሞኘት እንደማትችል አትዘንጋ። ይሖዋ ‘በከንፈራቸው እያከበሩት ልባቸው ግን ከእሱ እጅግ የራቀ’ ሰዎች እነማን እንደሆኑ ለይቶ ያውቃል።​—ማርቆስ 7:6

ሁለት ዓይነት ሕይወት የሚመሩ ሰዎች ይሖዋን እንደሚያሳዝኑት ታውቃለህ? እውነት ይሖዋ በሰው ልጆች ሊያዝን ይችላል? አዎን ያዝናል! የጥንቶቹ እስራኤላውያን የአምላክን ሕግ በተላለፉ ጊዜ ‘የእስራኤልን ቅዱስ እንዳስቆጡት’ ወይም እንዳሳዘኑት ተገልጿል። (መዝሙር 78:41) ዛሬም ወላጆቻቸው “በይሖዋ ተግሣጽ እንዲሁም የእሱን አስተሳሰብ በውስጣቸው በመቅረጽ” ያሳደጓቸው ልጆች በድብቅ መጥፎ ድርጊት ሲፈጽሙ አምላክ ምን ያህል ያዝን!​—ኤፌሶን 6:4

የፈጸምከውን ነገር ተናገር

በድብቅ ስትፈጽም የነበረውን ድርጊት ለአምላክም ሆነ ለወላጆችህ የመናገር ኃላፊነት አለብህ፤ ጥፋትህን መናገርህ ለራስህም ቢሆን ይጠቅምሃል። ይህን ማድረግ ሊያሳፍርህና ቅጣት ሊያስከትልብህ እንደሚችል አይካድም። (ዕብራውያን 12:11) ለምሳሌ፣ የመዋሸትና የማታለል ልማድ ካለህ ወላጆችህ በአንተ ላይ የነበራቸውን እምነት እንዲያጡ አድርገሃቸዋል። ስለዚህ ለተወሰነ ጊዜ ከቀድሞው ይበልጥ ጥብቅ ቢሆኑብህ ሊገርምህ አይገባም። ያም ቢሆን ከሁሉ የተሻለው እርምጃ ጥፋትህን መናገር ነው። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው?

እስቲ የሚከተለውን ምሳሌ ተመልከት፦ ከቤተሰብህ ጋር ከከተማ ወጣ ብላችሁ በእግራችሁ እየተንሸራሸራችሁ ነው እንበል። ወላጆችህ ከአጠገባቸው እንዳትርቅ ቢነግሩህም ትእዛዛቸውን በመጣስ እነሱ ሳያዩህ በሌላ አቅጣጫ መሄድ ጀመርክ፤ ብዙም ሳይቆይ ከወላጆችህ ጋር ተጠፋፋችሁ። ከዚያም ረግረግ መሬት ላይ ስትጓዝ ሳታስበው ማጥ ውስጥ ገባህና መስመጥ ጀመርክ። ታዲያ በዚህ ጊዜ ሥራህ ስለሚያሳፍርህ እርዳታ ለማግኘት ከመጣራት ወደኋላ ትላለህ? ወላጆችህ የሰጡህን ማስጠንቀቂያ ችላ በማለትህ ይቀጡኛል ብለህ ትጨነቃለህ? በፍጹም! ከዚህ ይልቅ ጩኸትህን እንደምታቀልጠው ምንም ጥርጥር የለውም።

በተመሳሳይ ሁለት ዓይነት ሕይወት እየመራህ ከሆነ አፋጣኝ እርዳታ ያስፈልግሃል። ወደኋላ ተመልሰህ ያደረግከውን ማስተካከል እንደማትችል አስታውስ። የወደፊት ሕይወትህን ማስተካከል ግን ትችላለህ። ስለፈጸምከው ድርጊት መናገርና አካሄድህን ማስተካከል በጣም ከባድ እንደሚሆንብህና ሥቃይ እንደሚያስከትልብህ ምንም ጥርጥር የለውም፤ ያም ቢሆን በአንተም ሆነ በቤተሰብህ ላይ ተጨማሪ ጉዳት ከማምጣትህ በፊት የእርዳታ ጥሪ ማሰማትህ የጥበብ እርምጃ ነው። ባደረግኸው ነገር ከልብህ ከተጸጸትክ ይሖዋ ምሕረት ያደርግልሃል።​—ኢሳይያስ 1:18፤ ሉቃስ 6:36

ስለዚህ ለወላጆችህ እውነቱን ንገራቸው። በድርጊትህ ስሜታቸው ሊጎዳ እንደሚችል ተረዳላቸው። የሚሰጡህን ተግሣጽ ተቀበል። እንዲህ ካደረግህ ወላጆችህን ብቻ ሳይሆን ይሖዋንም ታስደስታለህ። ከዚህም በተጨማሪ ሕሊናህ ንጹሕ ስለሚሆን እፎይታ ታገኛለህ።​—ምሳሌ 27:11፤ 2 ቆሮንቶስ 4:2

በሚቀጥለው ምዕራፍ

አብረውህ ከሚማሩት ልጆች ጋር የሚያመሳስሏችሁ ብዙ ነገሮች አሉ። ይሁንና ስለ ትምህርት ቤት ጓደኝነት ልታውቀው የሚገባው ነገር ምንድን ነው?

ቁልፍ ጥቅስ

“ኀጢአቱን የሚሰውር አይለማም፤ የሚናዘዝና የሚተወው ግን ምሕረትን ያገኛል።”​—ምሳሌ 28:13

ጠቃሚ ምክር

የሠራኸውን ስህተት አቅልለህ መመልከት የለብህም፤ በሌላ በኩል ደግሞ ስለ ራስህ አፍራሽ አመለካከት እንዳታዳብር ተጠንቀቅ። ይሖዋ ይቅር ለማለት ዝግጁ የሆነ አምላክ መሆኑን አስታውስ።​—መዝሙር 86:5

ይህን ታውቅ ነበር?

የጥፋተኝነት ስሜት አንድ ሰው ስህተቱን እንዲያስተካክል ሊያነሳሳው ስለሚችል ጠቃሚ ሊሆን ይችላል። ከኃጢአት ጎዳናው የማይመለስ ሰው ግን ሕሊናው በተገቢው መንገድ እንዳይሠራ ያደርጋል። የዚህ ሰው ሕሊና በእሳት ተቃጥሎ ጠባሳ እንዳወጣ ቆዳ ይደነዝዛል።​—1 ጢሞቴዎስ 4:2

ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

ሁለት ዓይነት ሕይወት እየመራሁ ከሆነ ስለ ጉዳዩ ልነግራቸው የምፈልጋቸው ሰዎች ․․․․․

የሚሰጠኝን ማንኛውንም ተግሣጽ ለመቀበል እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

ምን ይመስልሃል?

● አንዳንድ ወጣቶች ሁለት ዓይነት ሕይወት የሚመሩት ለምንድን ነው?

● ሁለት ዓይነት ሕይወት መምራት ከሚያስከትላቸው ጉዳቶች አንዳንዶቹ የትኞቹ ናቸው?

● እንዲህ ካለው አካሄድ መላቀቅ ምን ጥቅሞች አሉት?

[በገጽ 140 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ወጣቶች፣ ላቅ ያሉ የሥነ ምግባር መሥፈርቶችን የሚከተሉ ክርስቲያኖች መሆናቸውን ለሌሎች ማሳወቅ እንዳለባቸው ይሰማኛል። በተቻለ መጠን ሳይዘገዩ ይህን ማድረግ አለባቸው። ሳይናገሩ በቆዩ መጠን ማንነታቸውን ማሳወቁ ከባድ ይሆንባቸዋል።”​—ሊንዳ

[በገጽ 141 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሁለት ዓይነት ሕይወት በመምራት ማጥ ውስጥ ገብተህ እየሰመጥክ ከሆነ የእርዳታ ጥሪ ማሰማት ይኖርብሃል