በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 1

ፈጣሪ ለሰው ገነትን ሰጠው

ፈጣሪ ለሰው ገነትን ሰጠው

አምላክ ግዑዙን አጽናፈ ዓለም እንዲሁም በምድር ላይ ሕይወትን ፈጠረ፤ ፍጹም የሆኑ ወንድና ሴት ፈጥሮ ውብ በሆነች ገነት ውስጥ ካስቀመጣቸው በኋላ ሊፈጽሟቸው የሚገቡ ትእዛዛትን ሰጣቸው

“በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማያትንና ምድርን ፈጠረ።” (ዘፍጥረት 1:1) ይህ ዓረፍተ ነገር እስከ ዛሬ ከተጻፉት ሁሉ ይበልጥ ታዋቂ የሆነ የመግቢያ ሐሳብ እንደሆነ ሲገለጽ ይሰማል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ በዚህ ጥቅስ ላይ በሰፈሩት ቀላልና ያማሩ ቃላት አማካኝነት በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ትልቁን ቦታ ከያዘው አካል ይኸውም ሁሉን ቻይ አምላክ ከሆነው ከይሖዋ ጋር ያስተዋውቀናል። በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሚገኘው የመጀመሪያው ጥቅስ፣ አምላክ የምንኖርባትን ፕላኔት ጨምሮ በጣም ሠፊ የሆነው ግዑዝ አጽናፈ ዓለም ፈጣሪ እንደሆነ ይገልጻል። በቀጣዮቹ ቁጥሮች ላይ እንደሰፈረው አምላክ በምሳሌያዊ መንገድ ቀናት ተብለው በተጠሩት ረጅም ዘመናት ውስጥ በዓለም ላይ ያሉትን አስደናቂ ነገሮች ሁሉ በመፍጠር ምድርን መኖሪያችን እንድትሆን አዘጋጅቷታል።

አምላክ በምድር ላይ ከፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ የሚበልጠው ሰው ነው። ሰው፣ እንደ ፍቅርና ጥበብ ያሉትን የይሖዋ ባሕርያት ማንጸባረቅ የሚችል በአምላክ አምሳል የተሠራ ፍጡር ነው። አምላክ ከምድር አፈር ወስዶ ሰውን አበጀው። ከዚያም ለፈጠረው ሰው አዳም የሚል ስም ያወጣለት ሲሆን በገነት ውስጥ ማለትም በኤደን የአትክልት ስፍራ እንዲኖር አደረገው። አምላክ ይህን የአትክልት ስፍራ የሚያማምሩና ፍሬ የሚያፈሩ ዛፎች የሞሉበት እንዲሆን አድርጎ አዘጋጅቶት ነበር።

አምላክ፣ ሰው አጋር እንደሚያስፈልገው ያውቅ ነበር። በመሆኑም ከአዳም የጎድን አጥንቶች አንዱን በመውሰድ ሴትን ከሠራ በኋላ ለአዳም ሚስት እንድትሆነው ሰጠው፤ በኋላ ላይ ይህች ሴት ሔዋን ተባለች። አዳምም “እነሆ፤ ይህች ዐጥንት ከዐጥንቴ፣ ሥጋም ከሥጋዬ ናት” በማለት አጋር በማግኘቱ እጅግ መደሰቱን በግጥም መልክ ገለጸ። አምላክም እንዲህ አለ፦ “ስለዚህ ሰው ከአባቱና ከእናቱ ተለይቶ ከሚስቱ ጋር ይጣመራል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ።”—ዘፍጥረት 2:22-24፤ 3:20

አምላክ ለአዳምና ለሔዋን ሁለት ትእዛዛት ሰጣቸው። አንደኛ፣ መኖሪያቸው የሆነችውን ምድር እንዲያለሟትና እንዲንከባከቧት እያደርም በዘሮቻቸው እንዲሞሏት ነገራቸው። ሁለተኛ፣ በዚያ ሠፊ የአትክልት ስፍራ ከነበሩት ዛፎች መካከል “መልካምና ክፉን ከሚያሳውቀው ዛፍ” ፍሬ ብቻ እንዳይበሉ አዘዛቸው። (ዘፍጥረት 2:17) ይህንን ትእዛዝ ከጣሱ ይሞታሉ። አምላክ እነዚህን ትእዛዛት በመስጠት ባልና ሚስቱ እሱን እንደ ገዥያቸው አድርገው እንደተቀበሉት የሚያሳዩበት አጋጣሚ እንዲኖራቸው አደረገ። እነዚህ ባልና ሚስት የተሰጣቸውን ትእዛዛት ማክበራቸው ለአምላክ ያላቸውን ፍቅርና አመስጋኝነት ለማሳየትም ያስችላቸዋል። ደግነት የሚንጸባረቅበትን የአምላክን አገዛዝ እንዲቀበሉ የሚያነሳሷቸው ብዙ ምክንያቶች ነበሯቸው። ፍጹማን ስለነበሩ ምንም እንከን አልነበረባቸውም። መጽሐፍ ቅዱስ “እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፤ እነሆም፣ እጅግ መልካም ነበረ” በማለት ይነግረናል።—ዘፍጥረት 1:31

በዘፍጥረት ምዕራፍ 1 እና ምዕራፍ 2 ላይ የተመሠረተ።