በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 16

መሲሑ መጣ

መሲሑ መጣ

ይሖዋ፣ ከረጅም ጊዜ በፊት ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ የናዝሬቱ ኢየሱስ መሆኑን አሳወቀ

ሰዎች ተስፋ የተሰጠበትን መሲሕ ለይተው ማወቅ እንዲችሉ ይሖዋ ይረዳቸው ይሆን? አምላክ የመሲሑን ማንነት ለማሳወቅ ምን እንዳደረገ እስቲ እንመልከት። ወቅቱ የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ተጽፈው ከተጠናቀቁ ከአራት መቶ ዓመታት ገደማ በኋላ ነው። በሰሜናዊው የገሊላ አውራጃ፣ በናዝሬት ከተማ የምትኖር ማርያም የተባለች አንዲት ወጣት አስገራሚ መልእክት የያዘ እንግዳ መጣባት። እንግዳው ገብርኤል የተባለው መልአክ ሲሆን ማርያም ድንግል ብትሆንም በአምላክ ቅዱስ መንፈስ አማካኝነት ወንድ ልጅ እንደምትወልድ ነገራት። ይህ ልጅ ከረጅም ጊዜ በፊት ተስፋ የተሰጠበት ለዘላለም የሚገዛው ንጉሥ ይሆናል! ማርያም የምትወልደው የአምላክን ልጅ ነው፤ አምላክ በሰማይ ይኖር የነበረውን የልጁን ሕይወት ወደ ማርያም ማህፀን ያዛውረዋል።

ማርያም ይህንን ታላቅ ኃላፊነት እንደ መብት በመቁጠር በትሕትና ተቀበለችው። አምላክ፣ መልአኩን ልኮ ማርያም እንዴት እንዳረገዘች አናፂ ለሆነው ለእጮኛዋ ለዮሴፍ ከነገረው በኋላ ዮሴፍ ማርያምን ሚስቱ አድርጎ ወሰዳት። ይሁንና መሲሑ በቤተልሔም እንደሚወለድ የተነገረው ትንቢት የሚፈጸመው እንዴት ነው? (ሚክያስ 5:2) ይህች ትንሽ ከተማ የምትገኘው ከናዝሬት 140 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ነበር!

በዚያ ዘመን የሮም ንጉሥ የሕዝብ ቆጠራ እንዲካሄድ አዋጅ አወጣ። ሕዝቡ ወደ ትውልድ ስፍራቸው ሄደው እንዲመዘገቡ ይጠበቅባቸው ነበር። ዮሴፍም ሆነ ማርያም የመጡት ከቤተልሔም ሳይሆን አይቀርም፤ በመሆኑም ዮሴፍ ነፍሰ ጡር የሆነችውን ሚስቱን ይዞ ወደ ቤተልሔም ሄደ። (ሉቃስ 2:3) ማርያም ልጇን የተገላገለችው በጋጣ ውስጥ ሲሆን ሕፃኑን በግርግም አስተኛችው። በዚህ ወቅት አምላክ፣ የተወለደው ሕፃን ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ ወይም ክርስቶስ መሆኑን በጎቻቸውን ይጠብቁ ለነበሩ እረኞች እንዲያበስሩ በርካታ መላእክትን ላከ።

ኢየሱስ ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ እንደሆነ ከጊዜ በኋላ ሌሎችም መሥክረዋል። ነቢዩ ኢሳይያስ መሲሑ ለሚያከናውነው በጣም አስፈላጊ ሥራ መንገዱን የሚያዘጋጅ አንድ ሰው እንደሚነሳ ትንቢት ተናግሮ ነበር። (ኢሳይያስ 40:3) ይህ መንገድ ጠራጊ መጥምቁ ዮሐንስ ነው። ዮሐንስ ኢየሱስን ባየው ጊዜ “የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግደው የአምላክ በግ ይኸውላችሁ!” በማለት ተናገረ። ከዮሐንስ ደቀ መዛሙርት አንዳንዶቹ ወዲያውኑ ኢየሱስን ተከተሉት። ከእነሱ አንዱ “መሲሑን አገኘነው” ብሎ ተናግሯል።—ዮሐንስ 1:29, 36, 41

ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን የሚያረጋግጥ ሌላም ማስረጃ አለ። ዮሐንስ ኢየሱስን ባጠመቀው ጊዜ ይሖዋ ራሱ ከሰማይ ተናግሯል። ይሖዋ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት ኢየሱስን መሲሕ አድርጎ የቀባው ሲሆን “በእሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ብሏል። (ማቴዎስ 3:16, 17) በእርግጥም ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የቆየው መሲሕ መጥቷል!

ይህ የሆነው መቼ ነበር? በዳንኤል ትንቢት ላይ የተነገሩት 483 ዓመታት ልክ ሲያበቁ ማለትም በ29 ዓ.ም. ነበር። ይህም ኢየሱስ መሲሕ ወይም ክርስቶስ መሆኑን ከሚያረጋግጡት የማያሻሙ ማስረጃዎች መካከል አንዱ ነው። ይሁንና መሲሑ በምድር ላይ በኖረበት ጊዜ ያወጀው መልእክት ምንድን ነው?

በማቴዎስ ምዕራፍ 1 እስከ ምዕራፍ 3፤ በማርቆስ ምዕራፍ 1፤ በሉቃስ ምዕራፍ 2፤ በዮሐንስ ምዕራፍ 1 ላይ የተመሠረተ።