በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 18

ኢየሱስ ተአምራት ፈጸመ

ኢየሱስ ተአምራት ፈጸመ

ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት ንጉሥ በሚሆንበት ጊዜ ኃይሉን እንዴት እንደሚጠቀምበት ያሳያሉ

አምላክ ሌሎች ሰዎች ማድረግ የማይችሏቸውን ነገሮች ለማከናወን የሚያስችል ኃይል ለኢየሱስ ሰጥቶታል። ኢየሱስ እጅግ ብዙ ተአምራት የፈጸመ ሲሆን አብዛኛውን ጊዜም ይህን ያደረገው በበርካታ የዓይን ምሥክሮች ፊት ነበር። እነዚያ ተአምራት፣ ፍጹም ያልሆኑ ሰዎች ሊያጠፏቸው ያልቻሏቸውን ችግሮችና ጠላቶች ኢየሱስ የማስወገድ ኃይል እንዳለው አሳይተዋል። እስቲ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት።

ረሃብና ጥማት። ኢየሱስ የፈጸመው የመጀመሪያው ተአምር ውኃውን ግሩም ወደሆነ የወይን ጠጅ መለወጥ ነበር። በሌሎች ሁለት ወቅቶች ደግሞ ርቧቸው የነበሩ በሺህ የሚቆጠሩ ሰዎችን በጥቂት ዳቦና ዓሣ መግቧል። በሁለቱም አጋጣሚዎች ሕዝቡ ሁሉ በልተው ከጠገቡ በኋላ ምግቡ ተርፎ ነበር።

በሽታ። ኢየሱስ “ማንኛውንም ዓይነት በሽታና ማንኛውንም ዓይነት ሕመም” ፈውሷል። (ማቴዎስ 4:23) ዓይነ ስውሮችን፣ ደንቆሮዎችን እንዲሁም የሥጋ ደዌና የሚጥል በሽታ የነበረባቸውን ሰዎች አድኗል። እንዲሁም አንካሶችን፣ ሽባዎችንና የተለያየ የአካል ጉዳት የነበረባቸውን ሰዎች ፈውሷል። ኢየሱስ መፈወስ ያቃተው አንዳችም በሽታ አልነበረም።

አደገኛ የአየር ሁኔታ። ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ የገሊላን ባሕር በጀልባ እየተሻገሩ እያለ ኃይለኛ አውሎ ነፋስ ተነሳ። በዚህ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ በፍርሃት ተዋጡ። ኢየሱስ ግን “ጸጥ በል! ረጭ በል!” በማለት ማዕበሉን ገሠጸው። በዚህ ጊዜ ታላቅ ጸጥታ ሰፈነ። (ማርቆስ 4:37-39) በሌላ ጊዜ ደግሞ ባሕሩ አስፈሪ በሆነ ሞገድ እየተናወጠ በነበረበት ወቅት ኢየሱስ በውኃው ላይ እየተራመደ ሄዷል።—ማቴዎስ 14:24-33

ክፉ መናፍስት። ክፉ መናፍስት ከሰዎች የበለጠ ኃይል አላቸው። ብዙ ሰዎች ክፉ ከሆኑት ከእነዚህ የአምላክ ጠላቶች ቁጥጥር ራሳቸውን ማላቀቅ ያቅታቸዋል። ሆኖም በተደጋጋሚ ጊዜያት ኢየሱስ፣ በክፉ መናፍስት ቁጥጥር ሥር የነበሩ ሰዎችን ከአጋንንቱ ጥቃት ነፃ አውጥቷቸዋል። ኢየሱስ እነዚህን መናፍስት አይፈራቸውም። በተቃራኒው ክፉ መናፍስቱ እሱ ያለውን ሥልጣን ስለሚያውቁ ይፈሩት ነበር።

ሞት። “የመጨረሻው ጠላት” የሚል ተስማሚ ስያሜ የተሰጠው ሞት ማንም ሰው ሊያሸንፈው የማይችል ጠላት ነው። (1 ቆሮንቶስ 15:26) ኢየሱስ ግን ሙታንን አስነስቷል፤ እናቱ መበለት የሆነች አንድ ወጣት እንዲሁም አንዲት ትንሽ ልጅ በሞቱበት ወቅት እነዚህን ልጆች በማስነሳት ከወላጆቻቸው ጋር እንዲገናኙ አድርጓል። ኢየሱስ፣ ከሞተ አራት ቀናት ሆኖት የነበረውን አልዓዛር የሚባለውን ወዳጁን ብዙ ሐዘንተኞች በተገኙበት ከሞት በማስነሳትም በጣም አስገራሚ የሆነ ነገር አከናውኗል! የኢየሱስ ቀንደኛ ጠላቶችም እንኳ ይህ ተአምር መፈጸሙን አልካዱም።—ዮሐንስ 11:38-48፤ 12:9-11

ኢየሱስ እነዚያን ሁሉ ተአምራት የፈጸመው ለምን ነበር? ደግሞስ በተአምራዊ መንገድ የረዳቸው ሰዎች በሙሉ ከጊዜ በኋላ ሞተው የለም? አዎን ሞተዋል፤ ይሁን እንጂ ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት ዘላቂነት ያለው ነገር አከናውነዋል። እነዚያ ተአምራት ስለ መሲሐዊው ንጉሥ አገዛዝ የተነገሩት አስደናቂ ትንቢቶች እንደሚፈጸሙ አረጋግጠዋል። አምላክ የሾመው ንጉሥ ረሃብን፣ በሽታን፣ አደገኛ የአየር ሁኔታን፣ ክፉ መናፍስትንና ሌላው ቀርቶ ሞትንም ጭምር ማስወገድ እንደሚችል ምንም አያጠራጥርም። አምላክ ይህን ሁሉ ለማድረግ የሚያስችለውን ኃይል እንደሰጠው ኢየሱስ በምድር ላይ በነበረበት ወቅት አሳይቷል።

በማቴዎስ፣ በማርቆስ፣ በሉቃስና በዮሐንስ መጻሕፍት ላይ የተመሠረተ።