በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 10

የቤተሰብ አምልኮ ምንድን ነው?

የቤተሰብ አምልኮ ምንድን ነው?

ደቡብ ኮሪያ

ብራዚል

አውስትራሊያ

ጊኒ

ይሖዋ ከጥንት ዘመን ጀምሮ የቤተሰብ አባላት አንድ ላይ ጊዜ በማሳለፍ መንፈሳዊነታቸውን እንዲያጠናክሩና እርስ በርስ ይበልጥ እንዲቀራረቡ እንደሚፈልግ ገልጿል። (ዘዳግም 6:6, 7) የይሖዋ ምሥክር የሆኑ ቤተሰቦችም በየሳምንቱ የቤተሰብ አምልኮ የሚያደርጉበት ጊዜ የሚመድቡት ለዚህ ነው፤ በእነዚህ ወቅቶች ቤተሰቦች በሚያስፈልጓቸው መንፈሳዊ ነገሮች ላይ ዘና ባለ መንፈስ ይወያያሉ። ብቻህን የምትኖር ቢሆንም እንኳ እንዲህ ያለው ፕሮግራም በምትፈልገው ርዕሰ ጉዳይ ላይ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በማድረግ ከአምላክ ጋር ያለህን ዝምድና ለማጠናከር አጋጣሚ ይፈጥርልሃል።

ወደ ይሖዋ ይበልጥ ለመቅረብ ያስችላል። “ወደ አምላክ ቅረቡ፤ እሱም ወደ እናንተ ይቀርባል።” (ያዕቆብ 4:8) በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ስለ ይሖዋ ባሕርያትና ስላደረጋቸው ነገሮች በጥልቀት መማራችን ስለ እሱ ይበልጥ ለማወቅ ያስችለናል። ለመጀመሪያ ጊዜ የቤተሰብ አምልኮ ስታደርጉ መጽሐፍ ቅዱስን አብራችሁ ማንበብ ትችላላችሁ፤ ለምሳሌ በክርስቲያናዊ ሕይወትና አገልግሎት ስብሰባ ላይ የሚወጣውን ሳምንታዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ፕሮግራም መከተል ይቻላል። በምታነብቡበት ጊዜ ሁሉም የቤተሰብ አባል የተወሰነ ክፍል እንዲደርሰው ማድረግ ትችላላችሁ፤ ከዚያም ከንባቡ ባገኛችሁት ነገር ላይ ተወያዩ።

የቤተሰብ አባላት እርስ በርሳቸው እንዲቀራረቡ ያደርጋል። ባሎችና ሚስቶች እንዲሁም ወላጆችና ልጆች መጽሐፍ ቅዱስን በቤተሰብ ማጥናታቸው ይበልጥ እንዲቀራረቡ ያደርጋቸዋል። የአምልኮ ፕሮግራማቸው ሁሉም በጉጉት የሚጠብቁት እንዲሁም አስደሳችና ሰላማዊ ሊሆን ይገባል። ወላጆች የልጆቻቸውን ዕድሜ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ሊወያዩባቸው የሚችሉ ጠቃሚ ርዕሶችን ሊመርጡ ይችላሉ፤ ምናልባትም በመጠበቂያ ግንብ እና በንቁ! መጽሔቶች ላይ ወይም jw.org በተባለው ድረ ገጻችን ላይ የሚወጡ ዓምዶችን መጠቀም ይፈልጉ ይሆናል። ልጆቻችሁ በትምህርት ቤት ስላጋጠማቸው ችግር አንስታችሁ እንዴት ሊቋቋሙት እንደሚችሉ መወያየት ትችላላችሁ። በJW ብሮድካስት (tv.pr418.com) ላይ የሚተላለፈውን ፕሮግራም ከተመለከታችሁ በኋላ ለምን አትወያዩበትም? እንዲሁም በስብሰባዎች ላይ የሚዘመሩ መዝሙሮችን መለማመድ የምትችሉ ሲሆን ከቤተሰብ አምልኮው በኋላም ቀለል ያሉ ምግቦችን በማቅረብ አብራችሁ ጊዜ ልታሳልፉ ትችላላችሁ።

በየሳምንቱ አብራችሁ ይሖዋን በማምለክ የምታሳልፉት ይህ ልዩ ጊዜ የቤተሰባችሁ አባላት በሙሉ በአምላክ ቃል እንዲደሰቱ ያደርጋል፤ ይሖዋም ጥረታችሁን አብዝቶ ይባርክላችኋል።—መዝሙር 1:1-3

  • ለቤተሰብ አምልኮ ጊዜ የምንመድበው ለምንድን ነው?

  • ወላጆች ይህ ጊዜ ለሁሉም የቤተሰብ አባላት አስደሳች እንዲሆን ምን ማድረግ ይችላሉ?