በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 11

በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ የምንገኘው ለምንድን ነው?

በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ የምንገኘው ለምንድን ነው?

ሜክሲኮ

ጀርመን

ቦትስዋና

ኒካራጉዋ

ጣሊያን

በእነዚህ ሰዎች ፊት ላይ የደስታ ስሜት የሚነበበው ለምንድን ነው? የይሖዋ ምሥክሮች በሚያደርጉት አንድ ትልቅ ስብሰባ ላይ ስለተገኙ ነው። በዓመት ውስጥ ሦስት ጊዜ እንዲሰበሰቡ ታዘው እንደነበሩት እንደ ጥንቶቹ የአምላክ ሕዝቦች ሁሉ እኛም ብዙ ሆነን የምንሰበሰብ ሲሆን ልክ እንደ እነሱ እኛም ይህን ጊዜ በጉጉት እንጠብቃለን። (ዘዳግም 16:16) በየዓመቱ ሦስት ትላልቅ ስብሰባዎች የምናደርግ ሲሆን ሁለት ጊዜ የአንድ ቀን የወረዳ ስብሰባ እንዲሁም አንድ ጊዜ የሦስት ቀን የክልል ስብሰባ እናደርጋለን። ከእነዚህ ስብሰባዎች ምን ጥቅም እናገኛለን?

ክርስቲያናዊ ወንድማማችነታችንን ያጠናክሩልናል። እስራኤላውያን ይሖዋን “በታላቅ ጉባኤ መካከል” ማወደስ ያስደስታቸው እንደነበረ ሁሉ እኛም በእነዚህ ልዩ ወቅቶች አንድ ላይ ሆነን እሱን ማምለክ ያስደስተናል። (መዝሙር 26:12፤ 111:1) እነዚህ ስብሰባዎች ከሌሎች ጉባኤዎች አልፎ ተርፎም ከሌሎች አገራት ከመጡ የይሖዋ ምሥክሮች ጋር ለመገናኘትና አብረን ጊዜ ለማሳለፍ አጋጣሚ ይፈጥሩልናል። እኩለ ቀን ሲሆን ከስብሰባው ቦታ ሳንወጣ ምሳችንን መመገባችን እነዚህ መንፈሳዊ ዝግጅቶች አስደሳች እንዲሆኑ አስተዋጽኦ ያበረክታል። (የሐዋርያት ሥራ 2:42) ከዚህም ሌላ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የይሖዋ ሕዝቦችን ያቀፈውን “የወንድማማች ማኅበር” አንድ የሚያደርገውን ፍቅር ለመቅመስ የሚያስችል አጋጣሚ እናገኛለን።—1 ጴጥሮስ 2:17

መንፈሳዊ እድገት ለማድረግ ያስችሉናል። እስራኤላውያን በስብሰባዎች ላይ ቅዱሳን መጻሕፍት ይብራሩላቸው ስለነበር ‘ቃሉን መረዳት’ ችለዋል። (ነህምያ 8:8, 12) እኛም ብንሆን በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ከመጽሐፍ ቅዱስ የምናገኛቸውን ማሳሰቢያዎች ከፍ አድርገን እንመለከታቸዋለን። እያንዳንዱ ፕሮግራም ከቅዱሳን መጻሕፍት በተወሰደ ጭብጥ ላይ የተመሠረተ ነው። በስብሰባው ላይ የሚቀርቡት ግሩም ንግግሮች፣ ሲምፖዚየሞችና ሠርቶ ማሳያዎች የአምላክን ፈቃድ በሕይወታችን ውስጥ እንዴት መፈጸም እንደምንችል ያስተምሩናል። ባለንበት አስቸጋሪ ጊዜ፣ ክርስቲያኖች በመሆናቸው የሚያጋጥሟቸውን ተፈታታኝ ሁኔታዎች በጽናት የተወጡ የእምነት ባልንጀሮቻችንን ተሞክሮ ስንሰማ እንበረታታለን። በክልል ስብሰባዎች ላይ የሚኖሩት ድራማዎች የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪኮች ሕያው አድርገው በማቅረብ ከዘገባው ትምህርት እንድናገኝ ይረዱናል። ራሳቸውን ለአምላክ መወሰናቸውን ለሕዝብ ለማሳየት ለሚፈልጉ በሙሉ በሁሉም ትላልቅ ስብሰባዎች ላይ የጥምቀት ሥነ ሥርዓት ይዘጋጃል።

  • ትላልቅ ስብሰባዎች አስደሳች ወቅት የሆኑት ለምንድን ነው?

  • በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ በመገኘት ምን ጥቅም ማግኘት ትችላለህ?