በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 12

የመንግሥቱን ምሥራች የምንሰብከው እንዴት ነው?

የመንግሥቱን ምሥራች የምንሰብከው እንዴት ነው?

ስፔን

ቤላሩስ

ሆንግ ኮንግ

ፔሩ

ኢየሱስ ከመሞቱ ጥቂት ቀደም ብሎ “ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለብሔራት ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል፤ ከዚያም መጨረሻው ይመጣል” በማለት ተናግሮ ነበር። (ማቴዎስ 24:14) ይሁን እንጂ ይህ ዓለም አቀፍ የስብከት ሥራ የሚከናወነው እንዴት ነው? ኢየሱስ ምድር ሳለ የተወውን ምሳሌ በመከተል ነው።—ሉቃስ 8:1

ሰዎችን ቤታቸው ሄደን ለማነጋገር ጥረት እናደርጋለን። ኢየሱስ ምሥራቹን ከቤት ወደ ቤት እየሄዱ እንዲሰብኩ ደቀ መዛሙርቱን አሠልጥኗቸው ነበር። (ማቴዎስ 10:11-13፤ የሐዋርያት ሥራ 5:42፤ 20:20) በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት እነዚህ ወንጌላውያን የሚሰብኩበት ክልል ተመድቦላቸው ነበር። (ማቴዎስ 10:5, 6፤ 2 ቆሮንቶስ 10:13) ዛሬም በተመሳሳይ የስብከት ሥራችን በሚገባ የተደራጀ ሲሆን እያንዳንዱ ጉባኤም ሊሸፍነው የሚገባ የራሱ ክልል ተመድቦለታል። ይህም “ለሰዎች እንድንሰብክና በተሟላ ሁኔታ እንድንመሠክር” የሚያዝዘውን የኢየሱስን መመሪያ ለመፈጸም ያስችለናል።—የሐዋርያት ሥራ 10:42

ሰዎች በሚገኙበት ቦታ ሁሉ ለመስበክ ጥረት እናደርጋለን። ኢየሱስ ብዙ ሕዝብ በሚገኝባቸው ቦታዎችም ለምሳሌ በባሕር ዳርቻዎችና በውኃ ጉድጓዶች አቅራቢያ በመስበክ አርዓያ ትቶልናል። (ማርቆስ 4:1፤ ዮሐንስ 4:5-15) እኛም ሰዎችን ማግኘት በምንችልበት ቦታ ሁሉ ይኸውም በመንገድ ላይ፣ በንግድ አካባቢዎችና በመናፈሻ ቦታዎች አሊያም ደግሞ በስልክ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እናወያያቸዋለን። በተጨማሪም አመቺ አጋጣሚ በምናገኝበት ጊዜ ለጎረቤቶቻችን፣ ለሥራ ባልደረቦቻችን፣ አብረውን ለሚማሩ ልጆችና ለዘመዶቻችን ሁሉ እንመሠክራለን። ምሥራቹን ለመስበክ የምናደርገው ይህ ሁሉ ጥረት በዓለም ዙሪያ የሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች “የማዳኑን ምሥራች” እንዲሰሙ አስችሏል።—መዝሙር 96:2

ስለ አምላክ መንግሥትና ወደፊት ስለሚያመጣቸው ነገሮች የሚገልጸውን ምሥራች ልትነግረው የምትፈልገው ሰው አለ? ይህን አስደሳች ተስፋ ሚስጥር አድርገህ አትያዘው። ዛሬ ነገ ሳትል ይህን ምሥራች ለሌሎች ተናገር!

  • መሰበክ ያለበት “ምሥራች” የትኛው ነው?

  • የይሖዋ ምሥክሮች፣ ኢየሱስ ምሥራቹን የሰበከበትን መንገድ የሚኮርጁት እንዴት ነው?