በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 19

ታማኝና ልባም ባሪያ ማን ነው?

ታማኝና ልባም ባሪያ ማን ነው?

ሁላችንም ከሚቀርብልን መንፈሳዊ ምግብ ጥቅም እናገኛለን

ኢየሱስ ከመሞቱ ጥቂት ቀደም ብሎ አራት ደቀ መዛሙርቱ ይኸውም ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ዮሐንስና እንድርያስ ወደ እሱ ለብቻቸው መጥተው አነጋግረውት ነበር። ኢየሱስ በመጨረሻው ዘመን የእሱን መገኘት የሚያሳውቀውን ምልክት በሚናገርበት ወቅት እንደሚከተለው በማለት አንድ ወሳኝ ጥያቄ አነሳ፦ “በተገቢው ጊዜ ምግባቸውን እንዲሰጣቸው ጌታው በቤተሰቦቹ ላይ የሾመው ታማኝና ልባም ባሪያ በእርግጥ ማን ነው?” (ማቴዎስ 24:3, 45፤ ማርቆስ 13:3, 4) ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ይህን ጥያቄ ሲያቀርብ ‘ጌታቸው’ እንደመሆኑ መጠን በመጨረሻው ዘመን ለተከታዮቹ ሳያሰልሱ መንፈሳዊ ምግብ የሚያቀርቡ ሰዎችን እንደሚሾም ማረጋገጡ ነበር። ታዲያ እነዚህ ሰዎች እነማን ናቸው?

ጥቂት ቁጥር ያላቸው በመንፈስ የተቀቡ የኢየሱስ ተከታዮችን ያቀፈ ቡድን ነው። ‘ባሪያው’ የይሖዋ ምሥክሮችን የበላይ አካል ያመለክታል። አብረውት ይሖዋን ለሚያመልኩት የእምነት ባልንጀሮቹ ወቅታዊ የሆነ መንፈሳዊ ምግብ ያቀርባል። የሚያስፈልገንን “ምግብ በተገቢው ጊዜ” የምናገኘው ከታማኙ ባሪያ ነው።—ሉቃስ 12:42

የአምላክን ቤተሰብ ያስተዳድራል። (1 ጢሞቴዎስ 3:15) ኢየሱስ፣ የይሖዋ ድርጅት ምድራዊ ክፍል የሚያከናውነውን ሥራ የማስተዳደሩን ከባድ ኃላፊነት የሰጠው ለባሪያው ነው፤ ይህም ቁሳዊ ንብረቶቹን መቆጣጠርን፣ የስብከቱን ሥራ መምራትን እንዲሁም በጉባኤዎች በኩል እኛን ማስተማርን ይጨምራል። “ታማኝና ልባም ባሪያ” በአገልግሎታችን ላይ በምንጠቀምባቸው ጽሑፎች እንዲሁም በጉባኤና በትላልቅ ስብሰባዎቻችን ላይ በሚቀርቡት ትምህርቶች አማካኝነት የሚያስፈልገንን መንፈሳዊ ምግብ በተገቢው ጊዜ እያቀረበልን ነው።

ባሪያው ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችና ምሥራቹን እንዲሰብክ ለተሰጠው ኃላፊነት ታማኝ ሲሆን በምድር ላይ የሚገኘውን የክርስቶስ ንብረት በጥበብ በማስተዳደርም ልባም መሆኑን አሳይቷል። (የሐዋርያት ሥራ 10:42) ይሖዋ የሕዝቦቹ ቁጥር እንዲያድግ በማድረግ እንዲሁም ባሪያው የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ዝግጅት እንዲያቀርብ በመርዳት ይህ ባሪያ የሚያከናውነውን ሥራ እየባረከው ነው።—ኢሳይያስ 60:22፤ 65:13

  • ኢየሱስ፣ ደቀ መዛሙርቱን በመንፈሳዊ እንዲመግብ የሾመው ማንን ነው?

  • ባሪያው፣ ታማኝና ልባም የሆነው በምን መንገዶች ነው?