በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 23

ጽሑፎቻችን የሚዘጋጁትና የሚተረጎሙት እንዴት ነው?

ጽሑፎቻችን የሚዘጋጁትና የሚተረጎሙት እንዴት ነው?

የጽሑፍ ዝግጅት ክፍል፣ ዩናይትድ ስቴትስ

ደቡብ ኮሪያ

አርሜንያ

ቡሩንዲ

ስሪ ላንካ

‘ለብሔር፣ ለነገድ፣ ለቋንቋና ለሕዝብ ሁሉ ምሥራቹን’ በማወጁ ሥራ የተቻለንን ለማድረግ ስንል ከ750 በላይ በሚሆኑ ቋንቋዎች ጽሑፎችን እናዘጋጃለን። (ራእይ 14:6) ይህን ከባድ ሥራ የምንወጣው እንዴት ነው? በዓለም ዙሪያ በተለያዩ ቦታዎች በሚገኙ ጸሐፊዎችና በርካታ ተርጓሚዎች እገዛ ሲሆን በሥራው ላይ የሚካፈሉት በሙሉ የይሖዋ ምሥክሮች ናቸው።

ዋናው ጽሑፍ በእንግሊዝኛ ይዘጋጃል። የበላይ አካሉ በዋናው መሥሪያ ቤታችን የሚገኘውን የጽሑፍ ዝግጅት ክፍል እንቅስቃሴ በበላይነት ይቆጣጠራል። ይህ ክፍል፣ በዋናው መሥሪያ ቤትና በአንዳንድ ቅርንጫፍ ቢሮዎች ውስጥ ሆነው የሚሠሩት ጸሐፊዎች የሚያከናውኑትን ሥራ ይከታተላል። የተለያየ ባሕልና አስተዳደግ ያላቸው ጸሐፊዎች መኖራቸው ጽሑፎቻችን በልዩ ልዩ ባሕሎች ውስጥ ያሉ ሰዎችን የሚማርኩ ርዕሰ ጉዳዮችን የሚዳስሱ እንዲሆኑ አድርጓል፤ ይህም ጽሑፎቹ ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት እንዲያገኙ አስተዋጽኦ አበርክቷል።

ጽሑፉ ለተርጓሚዎች ይላካል። የተዘጋጀው ጽሑፍ ከታረመና እንዲወጣ ከጸደቀ በኋላ በምድር ዙሪያ ወደሚገኙ የትርጉም ቡድኖች በኤሌክትሮኒክ ፋይል ይላካል፤ እነዚህ ቡድኖች ጽሑፉን የሚተረጉሙ፣ ትርጉሙን ከእንግሊዝኛው ጋር እያመሳከሩ የሚያርሙና የማጣሪያ ንባብ የሚያከናውኑ ተርጓሚዎችን ያቀፉ ናቸው። ተርጓሚዎቹ የእንግሊዝኛውን መልእክት፣ በሚተረጉሙበት ቋንቋ ሙሉ በሙሉ ለማስተላለፍ የሚያስችላቸውን ‘ትክክለኛውን ቃል’ ለመምረጥ ጥረት ያደርጋሉ።—መክብብ 12:10

ኮምፒውተር ሥራውን ያቀላጥፈዋል። ኮምፒውተር፣ ጸሐፊዎችና ተርጓሚዎች የሚያከናውኑትን ሥራ መተካት አይችልም። ይሁን እንጂ ተርጓሚዎች፣ መዝገበ ቃላቶችንና ለትርጉም ሥራ የሚያግዙ ሌሎች ጽሑፎችን በኮምፒውተር ማግኘታቸው ሥራቸውን ለማፋጠን ይረዳቸዋል። በተጨማሪም የይሖዋ ምሥክሮች መልቲላንጉዌጅ ኤሌክትሮኒክ ፐብሊሺንግ ሲስተም (ሜፕስ) የተባለ የኮምፒውተር ፕሮግራም ሠርተዋል፤ ይህ ፕሮግራም ትርጉሙን በመቶዎች በሚቆጠሩ ቋንቋዎች ለመጻፍ፣ ጽሑፉን ከሥዕሉ ጋር ለማቀናበርና ለሕትመት ለማዘጋጀት ያስችላል።

በጥቂት ሺዎች የሚቆጠሩ ተናጋሪዎች ብቻ ባሏቸው ቋንቋዎች እንኳ ጽሑፎቻችንን ለመተርጎም ይህን ያህል ጥረት የምናደርገው ለምንድን ነው? ምክንያቱም የይሖዋ ፈቃድ “ሁሉም ዓይነት ሰዎች እንዲድኑና የእውነትን ትክክለኛ እውቀት እንዲያገኙ” ስለሆነ ነው።—1 ጢሞቴዎስ 2:3, 4

  • ጽሑፎቻችን የሚዘጋጁት እንዴት ነው?

  • ጽሑፎቻችንን በበርካታ ቋንቋዎች የምንተረጉመው ለምንድን ነው?