በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 24

በዓለም ዙሪያ ለምናከናውነው ሥራ የሚያስፈልገውን ገንዘብ የምናገኘው እንዴት ነው?

በዓለም ዙሪያ ለምናከናውነው ሥራ የሚያስፈልገውን ገንዘብ የምናገኘው እንዴት ነው?

ኔፓል

ቶጎ

ብሪታንያ

ድርጅታችን በየዓመቱ በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ መጽሐፍ ቅዱሶችንና ሌሎች ጽሑፎችን አትሞ ያለ ምንም ክፍያ ያሰራጫል። የስብሰባ አዳራሾችንና ቅርንጫፍ ቢሮዎችን እንገነባለን እንዲሁም እንጠግናለን። በሺዎች የሚቆጠሩት ቤቴላውያንና ሚስዮናውያን የሚያስፈልጓቸው ነገሮች እንዲሟሉላቸው እናደርጋለን፤ እንዲሁም አደጋ በሚደርስበት ጊዜ እርዳታ እንሰጣለን። ‘ታዲያ ለእነዚህ ሁሉ ነገሮች የሚሆን ገንዘብ የሚገኘው ከየት ነው?’ ብለህ ትጠይቅ ይሆናል።

አሥራት ወይም የአባልነት ክፍያ አንጠይቅም፤ ሙዳየ ምጽዋትም አናዞርም። የወንጌላዊነት ሥራችንን ማከናወን ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ ቢሆንም የገንዘብ እርዳታ አንጠይቅም። ከአንድ መቶ ዓመት በፊት የወጣው የመጠበቂያ ግንብ መጽሔት ሁለተኛ እትም፣ ‘ይሖዋ እንደሚደግፈን ስለምናምን ከሰዎች ድጋፍ ለማግኘት በፍጹም እንደማንለምን ወይም እንደማንማጠን’ ገልጾ ነበር፤ ደግሞም እንዲህ አድርገን አናውቅም!—ማቴዎስ 10:8

ለሥራችን የገንዘብ ድጋፍ የምናገኘው በፈቃደኝነት ከሚሰጥ መዋጮ ነው። ብዙ ሰዎች ለምናከናውነው መጽሐፍ ቅዱስን የማስተማር ሥራ አድናቆት ስላላቸው የገንዘብ መዋጮ ያደርጋሉ። የይሖዋ ምሥክሮችም በመላው ምድር ለሚከናወነው የአምላክን ፈቃድ የመፈጸም ሥራ ጊዜያቸውን፣ ጉልበታቸውን፣ ገንዘባቸውንና ሌላ ጥሪታቸውን በደስታ ይሰጣሉ። (1 ዜና መዋዕል 29:9) በስብሰባ አዳራሾች ውስጥ እንዲሁም በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ መዋጮ ለማድረግ የሚፈልጉ ሰዎች መዋጯቸውን የሚያስገቡባቸው ሣጥኖች ይገኛሉ። መዋጮ ለማድረግ jw.org/am የተባለውን ድረ ገጻችንንም መጠቀም ይቻላል። መዋጮ ሣጥኖች ውስጥ ከሚገኘው ገንዘብ አብዛኛውን የሚያዋጡት፣ ሁለት ትናንሽ ሳንቲሞች በቤተ መቅደሱ መዋጮ ዕቃ ውስጥ በመጨመሯ ኢየሱስ እንዳመሰገናት ድሃ መበለት ያሉ ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ያላቸው ሰዎች ናቸው። (ሉቃስ 21:1-4) ከዚህ ለማየት እንደሚቻለው ማንኛውም ሰው “በልቡ ያሰበውን” መስጠት እንዲችል በየጊዜው ‘የተወሰነ ገንዘብ ማስቀመጥ’ ይችላል።—1 ቆሮንቶስ 16:2፤ 2 ቆሮንቶስ 9:7

የተለያዩ ሰዎች፣ በሚያደርጉት መዋጮ አማካኝነት የመንግሥቱን ስብከት ሥራ በመደገፍ የአምላክ ፈቃድ እንዲፈጸም አስተዋጽኦ ያበረክታሉ፤ ይሖዋም ‘ባሏቸው ውድ ነገሮች እሱን ማክበር’ የሚፈልጉትን የእነዚህን ሰዎች ልብ ማነሳሳቱን እንደሚቀጥል እርግጠኞች ነን።—ምሳሌ 3:9

  • ድርጅታችንን ከሌሎች ሃይማኖቶች የሚለየው ምንድን ነው?

  • በፈቃደኝነት የሚደረጉትን መዋጮዎች የምንጠቀምባቸው እንዴት ነው?