በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 9

ኤርምያስ ስለ ይሖዋ መናገሩን አላቆመም

ኤርምያስ ስለ ይሖዋ መናገሩን አላቆመም

ሰዎቹ በኤርምያስ ላይ የተቆጡት ለምንድን ነው?

ይሖዋ ኤርምያስን አድኖታል

አንዳንድ ጊዜ ሰዎች ስለ ይሖዋ ስንነግራቸው ያሾፉብናል ወይም ደግሞ ይናደዳሉ። እንዲህ ያለ ሁኔታ ሲያጋጥመን ስለ አምላክ መናገራችንን ማቆም እንፈልግ ይሆናል። አንተስ እንዲህ ተሰምቶህ ያውቃል?— መጽሐፍ ቅዱስ፣ ይሖዋን ቢወድም ስለ እሱ መናገሩን ሊያቆም አስቦ ስለነበረ አንድ ወጣት ይናገራል። ስሙ ኤርምያስ ይባላል። እስቲ የዚህን ወጣት ታሪክ እንመልከት።

ኤርምያስ ወጣት እያለ፣ ሕዝቡ መጥፎ ነገር ማድረጋቸውን እንዲያቆሙ እንዲያስጠነቅቃቸው ይሖዋ ነገረው። ኤርምያስ ይህን ማድረግ በጣም የከበደው ከመሆኑም ሌላ ፈርቶ ነበር። በመሆኑም ‘ገና ትንሽ ልጅ ስለሆንኩ ምን ማለት እንዳለብኝ አላውቅም’ በማለት ለይሖዋ መለሰ። ይሖዋ ግን ‘አይዞህ አትፍራ። እኔ እረዳሃለሁ’ አለው።

በመሆኑም ኤርምያስ፣ ሕዝቡ አካሄዳቸውን ካልለወጡ ይሖዋ እንደሚቀጣቸው ማስጠንቀቅ ጀመረ። ሕዝቡ ኤርምያስን ሰምተው ለውጥ ያደረጉ ይመስልሃል?— በፍጹም! እንዲያውም በኤርምያስ ላይ አሾፉበት፤ ሌሎቹ ደግሞ ተናደዱበት። ሊገድሉት የፈለጉም ነበሩ! ኤርምያስ በዚህ ጊዜ ምን የተሰማው ይመስልሃል?— በጣም ፈርቶ ስለነበር ‘ከአሁን በኋላ ስለ ይሖዋ አልናገርም’ አለ። ይሁን እንጂ ተስፋ ቆርጦ ስለ ይሖዋ መናገሩን አቁሞ ነበር?— አላቆመም። ይሖዋን በጣም ይወድ ስለነበር ስለ እሱ መናገሩን ሊያቆም አልቻለም። ኤርምያስ ተስፋ ስላልቆረጠ ይሖዋ ጥበቃ አድርጎለታል።

ለምሳሌ፣ በአንድ ወቅት አንዳንድ መጥፎ ሰዎች ኤርምያስን ጥልቅ በሆነና በጭቃ በተሞላ ጉድጓድ ውስጥ ጥለውት ነበር። እዚያ ምግብም ሆነ ውኃ አያገኝም። እነዚህ ሰዎች፣ ኤርምያስ እዚያው እንዲሞት ፈልገው ነበር። ይሖዋ ስለረዳው ግን በሕይወት መትረፍ ቻለ!

ከኤርምያስ ምሳሌ ምን ትምህርት አገኘህ?— ኤርምያስ የፈራበት ወቅት ቢኖርም ስለ ይሖዋ መናገሩን አላቆመም። አንተም ስለ ይሖዋ ስትናገር ሰዎች ሊያሾፉብህ ወይም ሊናደዱብህ ይችላሉ። በመሆኑም ታፍር እንዲያውም ትፈራ ይሆናል። ስለ ይሖዋ መናገርህን ግን ፈጽሞ አታቁም። ይሖዋ፣ ኤርምያስን እንደረዳው ሁሉ አንተንም ምንጊዜም ይረዳሃል።

የሚከተሉትን ጥቅሶች አንብቡ