በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 4

ማርያም ሳታገባ ፀነሰች

ማርያም ሳታገባ ፀነሰች

ማቴዎስ 1:18-25 ሉቃስ 1:56

  • ዮሴፍ፣ ማርያም ማርገዟን አወቀ

  • ማርያም የዮሴፍ ሚስት ሆነች

ማርያም ከፀነሰች አራተኛ ወሯን ይዛለች። በእርግዝናዋ የመጀመሪያ ወራት፣ በስተ ደቡብ በይሁዳ ኮረብቶች የምትገኘውን ዘመዷን ኤልሳቤጥን ለመጠየቅ ሄዳ እንደነበር ታስታውስ ይሆናል። አሁን ግን ናዝሬት ወደሚገኘው ቤቷ ተመልሳለች። ብዙም ሳይቆይ የአካባቢዋ ሰዎች መፀነሷን ሊያውቁ ነው። ሁኔታው ማርያምን ምን ያህል እንደሚያስጨንቃት መገመት አያዳግትም!

ነገሩን ይበልጥ ከባድ የሚያደርገው ደግሞ ማርያም ለአናጺው ለዮሴፍ የታጨች መሆኗ ነው። አምላክ ለእስራኤላውያን በሰጠው ሕግ መሠረት ለአንድ ወንድ የታጨች ሴት ከሌላ ወንድ ጋር በፈቃደኝነት የፆታ ግንኙነት ከፈጸመች በድንጋይ ተወግራ እንደምትሞት ማርያም ታውቃለች። (ዘዳግም 22:23, 24) በመሆኑም ማርያም የሥነ ምግባር ብልግና ባትፈጽምም እንኳ ማርገዟን ለዮሴፍ እንዴት ብላ እንደምትገልጽለትና ከዚያ በኋላ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ሳያሳስባት አይቀርም።

ማርያም ሦስት ወር ቆይታ ስለመጣች ዮሴፍ እሷን ለማየት እንደናፈቀ ጥርጥር የለውም። ሲገናኙ ማርያም ሁኔታውን እንደምትነግረው የታወቀ ነው፤ የፀነሰችው በአምላክ ቅዱስ መንፈስ አማካኝነት እንደሆነ ለማስረዳት የተቻላትን ማድረጓ አይቀርም። ሆኖም ዮሴፍ ይህን መረዳትና ማመን በጣም እንደሚከብደው መገመት ትችላለህ።

ማርያም፣ መልካም ስም ያላት ጥሩ ሴት እንደሆነች ዮሴፍ ያውቃል። ከዚህም በላይ በጣም ይወዳታል። ማርያም የፀነሰችው በመንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ብትናገርም ዮሴፍ ከሌላ ሰው እንዳረገዘች ተሰምቶታል። ያም ሆኖ ዮሴፍ፣ ተወግራ እንድትሞት ወይም በሕዝብ ፊት እንድትዋረድ አልፈለገም፤ ስለዚህ በሚስጥር ሊፈታት ወሰነ። በዚያ ዘመን የተጫጩ ሰዎች እንደተጋቡ ይቆጠሩ ነበር፤ እነዚህ ሰዎች መለያየት ከፈለጉ መፋታት ነበረባቸው።

ዮሴፍ ጉዳዩን ሲያወጣና ሲያወርድ ቆይቶ ተኛ። በዚህ ጊዜ የይሖዋ መልአክ በሕልም ተገለጠለትና እንዲህ አለው፦ “ሚስትህ ማርያም የፀነሰችው በመንፈስ ቅዱስ ስለሆነ እሷን ወደ ቤት ለመውሰድ አትፍራ። ወንድ ልጅ ትወልዳለች፤ እሱንም ኢየሱስ ብለህ ትጠራዋለህ፤ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና።”—ማቴዎስ 1:20, 21

ዮሴፍ ሲነቃ፣ ጉዳዩ ይበልጥ ግልጽ ስለሆነለት ምንኛ ተደስቶ ይሆን! ምንም ጊዜ ሳያጠፋ መልአኩ ያለውን አደረገ። ማርያምን ወደ ቤቱ ወሰዳት። በሕዝብ ፊት የተፈጸመው ይህ ድርጊት እንደ ጋብቻ ሥነ ሥርዓት የሚቆጠር ሲሆን ዮሴፍና ማርያም እንደተጋቡ የሚያሳይ ነው። ሆኖም ኢየሱስን እስክትወልድ ድረስ ዮሴፍ ከማርያም ጋር የፆታ ግንኙነት አልፈጸመም።

ከወራት በኋላ፣ የመውለጃ ጊዜዋ የተቃረበው ማርያም እንዲሁም ዮሴፍ በናዝሬት ከሚገኘው ቤታቸው ተነስተው ረጅም ጉዞ ለማድረግ እየተዘጋጁ ነው። ማርያም ለመውለድ በተቃረበችበት በዚህ ጊዜ ወዴት ሊሄዱ ይሆን?