በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 5

ኢየሱስ ተወለደ—የትና መቼ?

ኢየሱስ ተወለደ—የትና መቼ?

ሉቃስ 2:1-20

  • ኢየሱስ በቤተልሔም ተወለደ

  • እረኞች ሕፃኑን ኢየሱስን ለማየት ሄዱ

የሮም ንጉሠ ነገሥት የሆነው አውግስጦስ ቄሳር እያንዳንዱ ሰው እንዲመዘገብ አዋጅ አወጣ። በመሆኑም ዮሴፍና ማርያም ከኢየሩሳሌም በስተ ደቡብ ወደምትገኘው የዮሴፍ የትውልድ ከተማ ይኸውም ወደ ቤተልሔም መጓዝ አለባቸው።

ለመመዝገብ ወደ ቤተልሔም ብዙ ሰዎች መጥተዋል። በዚህም ምክንያት ዮሴፍና ማርያም፣ አህዮችና ሌሎች እንስሳት በሚያድሩበት ጋጣ ውስጥ ከማረፍ ሌላ አማራጭ አላገኙም። ኢየሱስ የተወለደው በዚህ ቦታ ነው። ማርያምም በጨርቅ ጠቅልላ ለእንስሳቱ ምግብ በሚሰጥበት ግርግም ውስጥ አስተኛችው።

አውግስጦስ ቄሳር ሕዝቡ እንዲመዘገብ የሚያዝዝ ሕግ እንዲያወጣ ያደረገው አምላክ መሆን አለበት። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው? ምክንያቱም ይህ አዋጅ መውጣቱ ኢየሱስ በቤተልሔም እንዲወለድ ሁኔታዎችን አመቻችቷል፤ ቤተልሔም የኢየሱስ ቅድመ አያት የሆነው የንጉሥ ዳዊት የትውልድ ከተማ ናት። ተስፋ የተሰጠበት ገዢ በዚህች ከተማ እንደሚወለድ ቅዱሳን መጻሕፍት ከረጅም ዘመናት በፊት ተናግረው ነበር።—ሚክያስ 5:2

ይህ እንዴት ያለ ታላቅ ምሽት ነው! በሜዳ ላይ ተሰብስበው የነበሩ እረኞች በዙሪያቸው ደማቅ ብርሃን ታያቸው። ይህ ብርሃን የይሖዋ ክብር ነው! አንድ የይሖዋ መልአክ እረኞቹን እንዲህ አላቸው፦ “አትፍሩ፤ እነሆ፣ ለሰዎች ሁሉ ታላቅ ደስታ የሚያስገኝ ምሥራች እነግራችኋለሁ፤ በዛሬው ዕለት በዳዊት ከተማ አዳኝ ተወልዶላችኋልና፤ እሱም ጌታ ክርስቶስ ነው። ይህም ምልክት ይሁናችሁ፦ አንድ ሕፃን በጨርቅ ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኛላችሁ።” በድንገት ሌሎች በርካታ መላእክት ተገልጠው “በሰማያት ለአምላክ ክብር ይሁን፤ በምድርም አምላክ ሞገስ ለሚያሳያቸው ሰዎች ሰላም ይሁን” አሉ።—ሉቃስ 2:10-14

መላእክቱ ሲሄዱ እረኞቹ “አሁኑኑ ወደ ቤተልሔም ሄደን ይሖዋ በገለጠልን መሠረት በዚያ የተፈጸመውን ነገር ማየት አለብን” ተባባሉ። (ሉቃስ 2:15) ከዚያም በፍጥነት ሄዱ፤ መልአኩ በነገራቸው ቦታ ሕፃኑን ኢየሱስን አገኙት። እረኞቹ፣ መልአኩ ምን እንደነገራቸው ሲያወሩ የሰሟቸው ሰዎች ሁሉ ተደነቁ። ማርያምም የተባለውን ነገር ሁሉ በውስጧ ይዛ በልቧ ማሰላሰል ጀመረች።

በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች፣ ኢየሱስ የተወለደው በታኅሣሥ ወር እንደሆነ ያምናሉ። ሆኖም በቤተልሔም ታኅሣሥ የዝናብና የቅዝቃዜ ወቅት ነው። እንዲያውም አልፎ አልፎ አመዳይ ይጥላል። በዚያ ወቅት እረኞች ከመንጎቻቸው ጋር ውጭ አያድሩም። በተጨማሪም የሮም ንጉሠ ነገሥት፣ በወቅቱ በእሱ ላይ ለማመፅ ቋፍ ላይ የነበሩት ሕዝቦች በጣም በሚቀዘቅዘው በዚህ ወቅት ለበርካታ ቀናት ተጉዘው እንዲመዘገቡ ያዝዛል ብሎ ማሰብ የማይመስል ነገር ነው። ከሁኔታው መረዳት እንደሚቻለው ኢየሱስ የተወለደው በጥቅምት ወር ነው