በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 27

ማቴዎስ ተጠራ

ማቴዎስ ተጠራ

ማቴዎስ 9:9-13 ማርቆስ 2:13-17 ሉቃስ 5:27-32

  • ኢየሱስ ቀረጥ ሰብሳቢውን ማቴዎስን ጠራው

  • ክርስቶስ ኃጢአተኞችን ለመርዳት ከእነሱ ጋር ጊዜ አሳለፈ

ኢየሱስ ሽባውን ሰው ከፈወሰ በኋላ በገሊላ ባሕር አቅራቢያ በምትገኘው በቅፍርናሆም ለጥቂት ጊዜ ቆየ። በዚህ ጊዜም ብዙ ሰዎች ወደ እሱ ስለመጡ ያስተምራቸው ጀመር። ከዚያ ተነስቶ ሲሄድ ማቴዎስን በቀረጥ መሰብሰቢያው ቦታ ተቀምጦ አየው፤ ማቴዎስ፣ ሌዊ ተብሎም ይጠራል። ኢየሱስ “ተከታዬ ሁን” የሚል ልዩ ግብዣ አቀረበለት።—ማቴዎስ 9:9

እንደ ጴጥሮስ፣ እንድርያስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ሁሉ ማቴዎስም ስለ ኢየሱስ ትምህርትና በአካባቢው ስላከናወናቸው ነገሮች አስቀድሞ ሳይሰማ አይቀርም። ማቴዎስ ልክ እንደነሱ ጥሪውን ወዲያውኑ ተቀበለ። ማቴዎስ በጻፈው ወንጌል ላይ ይህን ሲገልጽ ማቴዎስ “በዚህ ጊዜ ተነስቶ [ኢየሱስን] ተከተለው” ብሏል። (ማቴዎስ 9:9) በዚህ መንገድ ማቴዎስ የቀረጥ ሰብሳቢነት ኃላፊነቱን ትቶ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ሆነ።

ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ማቴዎስ በቤቱ ትልቅ ግብዣ አደረገ፤ ይህን ያደረገው ኢየሱስ ላቀረበለት ልዩ ጥሪ አድናቆቱን ለመግለጽ ሊሆን ይችላል። ከኢየሱስና ከደቀ መዛሙርቱ ሌላ እነማን ተጠርተዋል? ቀረጥ ሰብሳቢዎች የሆኑ በርካታ የማቴዎስ የቀድሞ የሥራ ባልደረቦች በግብዣው ላይ ተገኝተዋል። እነዚህ ሰዎች፣ አይሁዶች ለሚጠሏቸው የሮም ባለሥልጣናት ቀረጥ ይሰበስባሉ፤ ከሚሰበስቡት ግብር መካከል ወደ ወደብ በሚመጡት መርከቦች፣ በዋናዎቹ መንገዶች በሚጠቀሙ ሰዎች እንዲሁም ከውጭ በሚገቡ ዕቃዎች ላይ የሚጣለው ቀረጥ ይገኝበታል። ለመሆኑ አብዛኞቹ አይሁዳውያን ለእነዚህ ቀረጥ ሰብሳቢዎች ምን አመለካከት አላቸው? ከተለመደው የቀረጥ ዋጋ በላይ በማስከፈል ብዙውን ጊዜ ስለሚያጭበረብሩ ሕዝቡ ይጠላቸዋል። ከቀረጥ ሰብሳቢዎቹ ሌላ፣ መጥፎ ነገር በማድረግ የሚታወቁ ‘ኃጢአተኞችም’ በግብዣው ላይ ተገኝተዋል።—ሉቃስ 7:37-39

ራሳቸውን የሚያመጻድቁት ፈሪሳውያን፣ ኢየሱስን በግብዣው ላይ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ሲያዩት ደቀ መዛሙርቱን “መምህራችሁ ከቀረጥ ሰብሳቢዎችና ከኃጢአተኞች ጋር የሚበላው ለምንድን ነው?” ብለው ጠየቋቸው። (ማቴዎስ 9:11) ኢየሱስ የተናገሩትን ሰምቶ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ “ሐኪም የሚያስፈልጋቸው ሕመምተኞች እንጂ ጤነኞች አይደሉም። እንግዲያው ሄዳችሁ ‘እኔ የምፈልገው ምሕረትን እንጂ መሥዋዕትን አይደለም’ የሚለውን ቃል ትርጉም አስተውሉ። እኔ የመጣሁት ጻድቃንን ሳይሆን ኃጢአተኞችን ልጠራ ነውና።” (ማቴዎስ 9:12, 13፤ ሆሴዕ 6:6) ፈሪሳውያን፣ ኢየሱስን ‘መምህር’ ብለው የጠሩት ከልባቸው አምነውበት አይደለም፤ ትክክል ስለሆነው ነገር ከእሱ መማር የሚችሉት ነገር ቢኖርም ለመማር አይፈልጉም።

ማቴዎስ ቀረጥ ሰብሳቢዎችንና ኃጢአተኞችን ወደ ቤቱ የጋበዛቸው ኢየሱስን አዳምጠው መንፈሳዊ ፈውስ ማግኘት እንዲችሉ ብሎ ሳይሆን አይቀርም፤ ምክንያቱም ከእነሱ መካከል “ብዙዎቹ እሱን መከተል ጀምረው ነበር።” (ማርቆስ 2:15) ኢየሱስ፣ እነዚህ ሰዎች ከአምላክ ጋር ጥሩ ግንኙነት እንዲኖራቸው ሊረዳቸው ይፈልጋል። ራሳቸውን ከሚያመጻድቁት ፈሪሳውያን በተለየ ኢየሱስ እነዚህን ሰዎች አልናቃቸውም። ከዚህ ይልቅ ርኅራኄና ምሕረት አሳይቷቸዋል፤ በእርግጥም በመንፈሳዊ ሁኔታ ለታመሙ ሁሉ መንፈሳዊ ሐኪም መሆን ይችላል።

ኢየሱስ ለቀረጥ ሰብሳቢዎችና ለኃጢአተኞች ምሕረት ያሳየው የኃጢአት ድርጊታቸውን ስለሚደግፍ ሳይሆን አካላዊ ሕመም ላለባቸው ሰዎች የተሰማው ዓይነት ከአንጀት የመራራት ስሜት ስላለው ነው። ለምሳሌ ያህል፣ በሥጋ ደዌ ተይዞ የነበረውን ሰው “እፈልጋለሁ! ንጻ” በማለት በርኅራኄ ስሜት እንደዳሰሰው አስታውስ። (ማቴዎስ 8:3) እኛስ እንዲህ ያለ የምሕረት ዝንባሌ ማዳበር እንዲሁም የተቸገሩ ሰዎችን በተለይ በመንፈሳዊ ሁኔታ መርዳት አይኖርብንም?