በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 28

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የማይጾሙት ለምንድን ነው?

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የማይጾሙት ለምንድን ነው?

ማቴዎስ 9:14-17 ማርቆስ 2:18-22 ሉቃስ 5:33-39

  • የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስን ስለ ጾም ጠየቁት

መጥምቁ ዮሐንስ የታሰረው ኢየሱስ በ30 ዓ.ም. በፋሲካ በዓል ላይ ከተገኘ ብዙም ሳይቆይ ነው፤ አሁንም ከእስር አልተፈታም። ዮሐንስ፣ ደቀ መዛሙርቱ የኢየሱስ ተከታዮች እንዲሆኑ ቢፈልግም እሱ ከታሰረ በኋላ ባሉት ወራት ይህን ያደረጉት ሁሉም አይደሉም።

በ31 ዓ.ም. የሚከበረው የፋሲካ በዓል እየተቃረበ ነው፤ በዚህ ወቅት አንዳንድ የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ወደ ኢየሱስ መጡና “እኛና ፈሪሳውያን ዘወትር ስንጾም የአንተ ደቀ መዛሙርት ግን የማይጾሙት ለምንድን ነው?” ብለው ጠየቁት። (ማቴዎስ 9:14) ፈሪሳውያን ጾምን እንደ አንድ የሃይማኖት ሥርዓት ይመለከቱታል። እንዲያውም ኢየሱስ ከጊዜ በኋላ በተናገረው አንድ ምሳሌ ላይ የተጠቀሰው ራሱን የሚያመጻድቅ ፈሪሳዊ “አምላክ ሆይ፣ እንደ ሌላው ሰው . . . ስላልሆንኩ አመሰግንሃለሁ። በሳምንት ሁለቴ እጾማለሁ” ብሎ እንደጸለየ ገልጿል። (ሉቃስ 18:11, 12) የዮሐንስ ደቀ መዛሙርትም የሚጾሙት አንድን የሃይማኖት ሥርዓት ለመከተል ብለው ሊሆን ይችላል። አሊያም የሚጾሙት ዮሐንስ በመታሰሩ ስላዘኑ ይሆናል። ስለዚህ አንዳንዶች፣ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርትም በዮሐንስ ላይ በደረሰው ነገር ማዘናቸውን ለማሳየት ለምን እንደማይጾሙ ጥያቄ ተፈጥሮባቸው ሊሆን ይችላል።

ኢየሱስ በምሳሌ በመጠቀም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ “የሙሽራው ጓደኞች ሙሽራው ከእነሱ ጋር እስካለ ድረስ የሚያዝኑበት ምን ምክንያት አለ? ሆኖም ሙሽራው ከእነሱ የሚወሰድበት ጊዜ ይመጣል፤ በዚያን ጊዜ ይጾማሉ።”—ማቴዎስ 9:15

ዮሐንስ ራሱ፣ ኢየሱስ ሙሽራ መሆኑን ተናግሯል። (ዮሐንስ 3:28, 29) ስለዚህ ኢየሱስ አብሯቸው እስካለ ድረስ ደቀ መዛሙርቱ አይጾሙም። ከጊዜ በኋላ ኢየሱስ ሲሞት ግን ደቀ መዛሙርቱ ስለሚያዝኑ መብላት አይፈልጉም። ሆኖም ከሞት ሲነሳ ሁኔታው ይለወጣል! ከዚያ በኋላ በሐዘን ምክንያት መጾም አያስፈልጋቸውም።

ኢየሱስ በመቀጠል የሚከተሉትን ሁለት ምሳሌዎች ተናገረ፦ “በአሮጌ ልብስ ላይ ውኃ ያልነካው አዲስ ጨርቅ የሚጥፍ ሰው የለም፤ አዲሱ ጨርቅ ሲሸበሸብ ልብሱን ስለሚስበው ቀዳዳው የባሰ ይሰፋልና። ደግሞም ሰዎች ባረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ አያስቀምጡም። እንዲህ ቢያደርጉ አቁማዳው ይፈነዳል፤ ወይኑ ይፈስሳል፤ አቁማዳውም ከጥቅም ውጭ ይሆናል። ነገር ግን ሰዎች አዲስ የወይን ጠጅ የሚያስቀምጡት በአዲስ አቁማዳ ነው።” (ማቴዎስ 9:16, 17) ኢየሱስ ሊያጎላ የፈለገው ነጥብ ምንድን ነው?

ኢየሱስ፣ በአይሁድ እምነት ውስጥ ያሉ ያረጁ ሥርዓቶችን ለምሳሌ በዘልማድ የሚደረገውን ጾም የእሱ ደቀ መዛሙርት እንዲከተሉ ማንም ሊጠብቅባቸው እንደማይገባ ለመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ማስረዳቱ ነው። እሱ ወደ ምድር የመጣው፣ ያረጀውንና የነተበውን እንዲሁም በቅርቡ የሚወገደውን የአምልኮ ሥርዓት ለመጣፍና ዕድሜውን ለማራዘም አይደለም። በዘመኑ የነበረውንና በሰው ወጎች የተሞላውን የአይሁድ እምነት መከተልን እያበረታታም አይደለም። ባረጀ ልብስ ላይ አዲስ ጨርቅ ለመጣፍ ወይም ባረጀና በደረቀ አቁማዳ ውስጥ አዲስ የወይን ጠጅ ለማስቀመጥ አልሞከረም።