በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 36

አንድ መቶ አለቃ ትልቅ እምነት አሳየ

አንድ መቶ አለቃ ትልቅ እምነት አሳየ

ማቴዎስ 8:5-13 ሉቃስ 7:1-10

  • የአንድ የጦር መኮንን ባሪያ ተፈወሰ

  • እምነት ያላቸው ይባረካሉ

ኢየሱስ የተራራውን ስብከት ከሰጠ በኋላ ወደ ቅፍርናሆም ከተማ ሄደ። እዚያም አንዳንድ አይሁዳውያን ሽማግሌዎች ወደ እሱ ቀረቡ። እነዚህን ሰዎች የላካቸው አይሁዳዊ ያልሆነ ሰው ሲሆን ግለሰቡ በሮም ሠራዊት ውስጥ መቶ አለቃ ነው።

የጦር መኮንኑ በጣም የሚወደው አገልጋዩ በጠና ታሞ ሞት አፋፍ ላይ ነው። መቶ አለቃው ከአሕዛብ ወገን ቢሆንም የኢየሱስን እርዳታ ፈልጓል። አይሁዳውያኑ፣ የዚህ ሰው አገልጋይ ‘ሽባ ሆኖ ቤት እንደተኛና በጣም እየተሠቃየ እንደሆነ’ ለኢየሱስ ነገሩት። (ማቴዎስ 8:6) አይሁዳውያኑ ሽማግሌዎች፣ ኢየሱስ ይህን መቶ አለቃ ሊረዳው የሚገባው ለምን እንደሆነ ሲገልጹ “ሕዝባችንን ይወዳል፤ ምኩራባችንንም ያሠራልን እሱ ነው” አሉ።—ሉቃስ 7:4, 5

ብዙም ሳይቆይ ኢየሱስ ከሽማግሌዎቹ ጋር በመሆን ወደ መኮንኑ ቤት መሄድ ጀመረ። ወደ ቤቱ ሲቃረቡ መኮንኑ ወዳጆቹን እንዲህ ሲል ወደ ኢየሱስ ላከ፦ “ጌታዬ፣ በቤቴ ጣሪያ ሥር ልትገባ የሚገባኝ ሰው ስላልሆንኩ አትድከም። ከዚህም የተነሳ አንተ ፊት መቅረብ የሚገባኝ ሰው እንደሆንኩ አልተሰማኝም።” (ሉቃስ 7:6, 7) ሌሎችን ማዘዝ የለመደው ይህ ሰው እንዲህ ብሎ የተናገረው ምን ያህል ትሑት ቢሆን ነው! ይህ ሰው፣ ባሪያዎችን ከሚያጎሳቁሉት ሌሎች ሮማውያን ምንኛ የተለየ ነው!—ማቴዎስ 8:9

አይሁዳውያን፣ አይሁዳዊ ካልሆኑ ሰዎች ጋር መቀራረብ እንደማይፈልጉ መቶ አለቃው ሳይገነዘብ አልቀረም። (የሐዋርያት ሥራ 10:28) መኮንኑ፣ “አንተ አንድ ቃል ተናገርና አገልጋዬ ይፈወስ” በማለት ወዳጆቹን ወደ ኢየሱስ የላከው ይህን በአእምሮው ይዞ መሆን አለበት።—ሉቃስ 7:7

ኢየሱስ ይህን ሲሰማ በጣም ስለተደነቀ “እላችኋለሁ፣ በእስራኤል ውስጥ እንኳ እንዲህ ዓይነት ታላቅ እምነት አላገኘሁም” አለ። (ሉቃስ 7:9) የመቶ አለቃው ወዳጆች ወደ እሱ ቤት ሲመለሱ በጠና ታሞ የነበረው ባሪያ ተሽሎት አገኙት።

ኢየሱስ ይህን ተአምር ከፈጸመ በኋላ፣ አይሁዳውያን ያልሆኑ እምነት ያሳዩ ሰዎች በረከት እንደሚያገኙ ለመግለጽ ይህን አጋጣሚ ተጠቀመበት፤ “ብዙዎች ከምሥራቅና ከምዕራብ ይመጣሉ፤ በመንግሥተ ሰማያትም ከአብርሃም፣ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር በማዕድ ይቀመጣሉ” አለ። እምነት የጎደላቸው አይሁዳውያንስ ምን ያጋጥማቸዋል? ኢየሱስ “ውጭ ወዳለው ጨለማ ይጣላሉ። በዚያም ያለቅሳሉ፤ ጥርሳቸውንም ያፋጫሉ” በማለት ተናገረ።—ማቴዎስ 8:11, 12

አይሁዳውያን ከክርስቶስ ጋር የመግዛት አጋጣሚ መጀመሪያ ቢቀርብላቸውም ይህን አጋጣሚ ስላልተጠቀሙበት ተቀባይነት ያጣሉ። አሕዛብ ግን ተቀባይነት የሚያገኙ ሲሆን “በመንግሥተ ሰማያት” ከኢየሱስ ጋር በአንድ ማዕድ የመቀመጥ አጋጣሚ ይሰጣቸዋል ሊባል ይችላል።