በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 45

በአጋንንት ላይ ያለው ኃይል

በአጋንንት ላይ ያለው ኃይል

ማቴዎስ 8:28-34 ማርቆስ 5:1-20 ሉቃስ 8:26-39

  • አጋንንትን ከሰው ላይ አስወጥቶ አሳሞች ውስጥ እንዲገቡ አደረገ

ደቀ መዛሙርቱ በባሕሩ ላይ ካጋጠማቸው አስፈሪ ሁኔታ በኋላ ወደ ዳርቻው ሲመለሱ ሌላ አስደንጋጭ ነገር ተመለከቱ። አጋንንት ያደሩባቸው ሁለት ኃይለኛ ሰዎች በአቅራቢያው ካለ የመቃብር ቦታ ወጥተው እየሮጡ ወደ ኢየሱስ መጡ! ይበልጥ ትኩረት የተደረገው በአንደኛው ሰው ላይ ነው፤ ይህ የሆነው ግለሰቡ ከሌላው ይበልጥ ኃይለኛ ስለሆነና በአጋንንት ቁጥጥር ሥር ለረጅም ጊዜ ስለቆየ ሳይሆን አይቀርም።

ይህ አሳዛኝ ሰው ራቁቱን ይዘዋወር ነበር። ሌሊትና ቀን “በመቃብር ቦታና በተራሮች ላይ ይጮኽ እንዲሁም ሰውነቱን በድንጋይ ይተለትል ነበር።” (ማርቆስ 5:5) ሰውየው በጣም አስፈሪ ከመሆኑ የተነሳ ማንም ሰው በዚያ ለማለፍ አይደፍርም። አንዳንዶች ሊያስሩት ቢሞክሩም ሰንሰለቱን ይበጣጥሰዋል፣ እግር ብረቱንም ይሰባብረዋል። እሱን በቁጥጥር ሥር ለማዋል የሚያስችል ጉልበት ያለው አንድም ሰው የለም።

ሰውየው ወደ ኢየሱስ ቀርቦ እግሩ ላይ ሲወድቅ፣ በእሱ ላይ ያደሩት አጋንንት “የልዑል አምላክ ልጅ ኢየሱስ ሆይ፣ እኔ ከአንተ ጋር ምን ጉዳይ አለኝ? እንዳታሠቃየኝ በአምላክ ስም አስምልሃለሁ” ብሎ እንዲጮኽ አደረጉት። ኢየሱስም “አንተ ርኩስ መንፈስ ከዚህ ሰው ውጣ” ብሎ በማዘዝ በአጋንንት ላይ ሥልጣን እንዳለው አሳየ።—ማርቆስ 5:7, 8

እርግጥ፣ ሰውየውን የያዙት አጋንንት ብዙ ናቸው። ኢየሱስ “ስምህ ማን ነው?” ብሎ ሲጠይቅ የተሰጠው ምላሽ “ብዙ ስለሆንን ስሜ ሌጌዎን ነው” የሚል ነው። (ማርቆስ 5:9) አንድ የሮማውያን ሌጌዎን በሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን ያቀፈ ነው፤ በመሆኑም በዚህ ሰው ላይ ያደሩት አጋንንት በርካታ ሲሆኑ እሱን በማሠቃየት ይደሰታሉ። አጋንንቱ ኢየሱስን “ወደ ጥልቁ እንዲሄዱ እንዳያዛቸው ተማጸኑት።” እነሱም ሆኑ መሪያቸው ሰይጣን ወደፊት ምን እንደሚጠብቃቸው ሳይገነዘቡ አልቀሩም።—ሉቃስ 8:31

በአቅራቢያው ባለ ተራራ ላይ ወደ 2,000 የሚጠጉ አሳማዎች መንጋ ተሰማርቶ ነበር፤ በሕጉ መሠረት አሳማዎች ርኩስ በመሆናቸው አይሁዳውያን አሳማ ሊኖራቸው አይገባም። አጋንንቱ “አሳማዎቹ ውስጥ እንድንገባ ወደ እነሱ ስደደን” አሉ። (ማርቆስ 5:12) ኢየሱስ እንዲሄዱ ስለፈቀደላቸው አሳማዎቹ ውስጥ ገቡ። በዚህ ጊዜ 2,000 ገደማ የሚሆኑት አሳማዎች በሙሉ ከገደሉ አፋፍ እየተንደረደሩ በመውረድ ባሕሩ ውስጥ ሰጠሙ።

የአሳማዎቹ እረኞች ይሄን ሲያዩ ሮጠው በመሄድ ወሬውን በከተማውና በገጠሩ አዳረሱት። ሕዝቡም የሆነውን ነገር ለማየት መጡ። ወደ ኢየሱስ ሲመጡ አጋንንት የወጡለት ሰው አእምሮው ተመልሶለትና ደህና ሆኖ አገኙት። እንዲያውም ልብስ ለብሶ ኢየሱስ እግር ሥር ተቀምጧል!

ይህን የሰሙ ወይም ሰውየውን ያዩ ሰዎች፣ የተከናወነው ነገር ለእነሱ ምን ትርጉም እንደሚኖረው ስላልገባቸው ታላቅ ፍርሃት አደረባቸው። በመሆኑም አካባቢያቸውን ለቆ እንዲሄድ ኢየሱስን ተማጸኑት። ኢየሱስ ወደ ጀልባው በመውጣት ላይ ሳለ፣ ጋኔን አድሮበት የነበረው ሰው አብሮት ለመሄድ ለመነው። ኢየሱስ ግን “ወደ ቤት ሄደህ ይሖዋ ያደረገልህን ነገር ሁሉና ያሳየህን ምሕረት ለዘመዶችህ ንገራቸው” አለው።—ማርቆስ 5:19

ብዙውን ጊዜ ኢየሱስ፣ የፈወሳቸውን ሰዎች ለማንም እንዳይናገሩ ያዛቸዋል፤ ምክንያቱም ሰዎች ስለ እሱ በሰሟቸው የተጋነኑ ወሬዎች ላይ ተመሥርተው መደምደሚያ ላይ እንዲደርሱ አይፈልግም። በዚህ ጊዜ ግን አጋንንት አድረውበት የነበረው ሰው፣ ኢየሱስ ላለው ኃይል ሕያው ማስረጃ ከመሆኑም ሌላ ኢየሱስ ሊያገኛቸው ለማይችላቸው ሰዎች መመሥከር ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ ሰውየው የሚሰጠው ምሥክርነት፣ አሳማዎቹ ስላለቁበት ምክንያት የተሳሳተ ወሬ እንዳይባዛ ሊያደርግ ይችል ይሆናል። በመሆኑም ሰውየው ሄዶ ኢየሱስ ያደረገለትን ነገር በመላው ዲካፖሊስ ያውጅ ጀመር።