በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 57

ኢየሱስ አንዲትን ልጅና መስማት የተሳነውን ሰው ፈወሰ

ኢየሱስ አንዲትን ልጅና መስማት የተሳነውን ሰው ፈወሰ

ማቴዎስ 15:21-31 ማርቆስ 7:24-37

  • ኢየሱስ የፊንቄያዊቷን ልጅ ፈወሳት

  • መስማትና መናገር የማይችልን ሰው ፈወሰ

ኢየሱስ፣ ጥቅማቸውን የሚያራምዱ ወጎችን በማውጣታቸው ፈሪሳውያንን ካወገዛቸው በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ሄደ። የተጓዘው በስተ ሰሜን ምዕራብ በርካታ ኪሎ ሜትሮች ርቆ ባለው በፊንቄ ወደሚገኙት የጢሮስና የሲዶና ክልሎች ነው።

በዚያም የሚያርፍበት ቤት አገኘ፤ ሆኖም ያለበትን ቦታ ማንም እንዲያውቅ አልፈለገም። ከሰዎች ሊሰወር ግን አልቻለም። በዚህ አካባቢ የተወለደች አንዲት ግሪካዊት ወደ ኢየሱስ መጥታ እንዲህ በማለት ለመነችው፦ “ጌታ ሆይ፣ የዳዊት ልጅ፣ ምሕረት አድርግልኝ። ልጄን ጋኔን ስለያዛት ክፉኛ እየተሠቃየች ነው።”—ማቴዎስ 15:22፤ ማርቆስ 7:26

ብዙም ሳይቆይ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን “ይህች ሴት ከኋላችን እየተከተለች ስለምትጮኽ እባክህ አሰናብታት” እያሉ ይለምኑት ጀመር። እሱም “እኔ የተላክሁት ከእስራኤል ቤት ለጠፉት በጎች እንጂ ለሌላ ለማንም አይደለም” በማለት ለሴትየዋ ምላሽ ያልሰጠበትን ምክንያት ገለጸ። ሴትየዋ ግን ተስፋ አልቆረጠችም። ወደ እሱ ቀርባ “ጌታ ሆይ፣ እርዳኝ!” እያለች ሰገደችለት።—ማቴዎስ 15:23-25

ኢየሱስ፣ አይሁዳውያን ለሌሎች ብሔራት ያላቸውን አሉታዊ አመለካከት በማንጸባረቅ “የልጆችን ዳቦ ወስዶ ለቡችሎች መጣል ተገቢ አይደለም” አላት፤ ይህን ያለው የሴትየዋን እምነት ለመፈተን ሳይሆን አይቀርም። (ማቴዎስ 15:26) ኢየሱስ “ቡችሎች” የሚለውን አገላለጽ መጠቀሙ አይሁዳውያን ላልሆኑ ሰዎች ያለውን የርኅራኄ ስሜት ያሳያል። ፊቱ ላይ የሚነበበው ስሜትና የድምፁ ቃና ጭምር ይህን አመለካከቱን የሚያንጸባርቅ መሆን አለበት።

ሴትየዋ ቅር ከመሰኘት ይልቅ አይሁዳውያን ካላቸው መሠረተ ቢስ ጥላቻ ጋር በተያያዘ ኢየሱስ በሰጠው ሐሳብ ላይ በመመርኮዝ “አዎ ጌታ ሆይ፣ ግን እኮ ቡችሎችም ከጌቶቻቸው ማዕድ የሚወድቀውን ፍርፋሪ ይበላሉ” በማለት በትሕትና ተናገረች። ኢየሱስ ጥሩ ልብ እንዳላት ስላስተዋለ “አንቺ ሴት፣ እምነትሽ ታላቅ ነው፤ በይ እንደ ፍላጎትሽ ይሁንልሽ” አላት። (ማቴዎስ 15:27, 28) ልጅቷ እዚያ ባትሆንም ኢየሱስ እንዳለው ሆነ! ሴትየዋ ወደ ቤቷ ስትመለስ ልጇ አልጋ ላይ ተኝታ፣ “ጋኔኑም ወጥቶላት አገኘቻት”፤ ልጅቷ ሙሉ በሙሉ ድናለች!—ማርቆስ 7:30

ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ከፊንቄ ክልል ተነስተው አገሩን በማቋረጥ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ መነሻ አቀኑ። ከዚያም ወደ ዲካፖሊስ ክልል ገቡ፤ ወደዚያ ሲሄዱ ከገሊላ ባሕር በስተ ሰሜን በኩል የዮርዳኖስን ወንዝ የተሻገሩ ይመስላል። እዚያም ወደ አንድ ተራራ ወጡ፤ ሆኖም ሕዝቡ ወደ እነሱ መምጣቱ አልቀረም። ሰዎቹ አንካሶችን፣ ሽባዎችን፣ ዓይነ ስውሮችንና ዱዳዎችን ወደ ኢየሱስ ይዘው መጡ። እነዚህን ሕመምተኞች እግሩ ሥር አስቀመጧቸው፤ እሱም ፈወሳቸው። ሕዝቡም እጅግ ተደንቀው የእስራኤልን አምላክ አከበሩ።

ኢየሱስ መስማት ለተሳነውና የመናገር እክል ላለበት አንድ ሰው ልዩ ትኩረት ሰጠ። ግለሰቡ በብዙ ሕዝብ መሃል በሚሆንበት ጊዜ ምን እንደሚሰማው መገመት ይቻላል። ኢየሱስ ይህ ሰው እንደተጨነቀ አስተውሎ ሳይሆን አይቀርም ከሕዝቡ ለይቶ ለብቻው ወሰደው። ብቻቸውን ሲሆኑም ምን ሊያደርግለት እንደሆነ በምልክት አሳየው። ጣቶቹን በሰውየው ጆሮዎች ውስጥ አስገባ፤ እንትፍ ካለ በኋላም የሰውየውን ምላስ ዳሰሰ። ከዚያም ወደ ሰማይ ተመለከተና “ኤፈታ” አለው፤ ይህም “ተከፈት” ማለት ነው። በዚህ ጊዜ የሰውየው ጆሮዎች ተከፈቱ፤ አጥርቶ መናገርም ቻለ። ኢየሱስ፣ ሰዎች ራሳቸው ባዩትና በሰሙት ነገር ላይ ተመሥርተው በእሱ እንዲያምኑ ስለሚፈልግ ይህን ሰው ስለተደረገለት ነገር ለሌሎች እንዳያወራ አዘዘው።—ማርቆስ 7:32-36

ሕዝቡ የኢየሱስን የመፈወስ ችሎታ ሲመለከቱ ‘ከመጠን በላይ ተደነቁ።’ በመሆኑም “ያደረገው ነገር ሁሉ መልካም ነው። ሌላው ቀርቶ መስማት የተሳናቸው ሰዎች እንዲሰሙ፣ ዱዳዎችም እንዲናገሩ ያደርጋል” አሉ።—ማርቆስ 7:37