በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 67

“ማንም ሰው እንደዚህ ተናግሮ አያውቅም”

“ማንም ሰው እንደዚህ ተናግሮ አያውቅም”

ዮሐንስ 7:32-52

  • ኢየሱስን ለመያዝ የቤተ መቅደስ ጠባቂዎች ተላኩ

  • ኒቆዲሞስ ኢየሱስን ደግፎ ተናገረ

ኢየሱስ በኢየሩሳሌም የዳስ በዓልን እያከበረ ነው። ‘ከሕዝቡ መካከል ብዙዎች በእሱ ማመናቸው’ አስደስቶታል። ይሁንና የሃይማኖት መሪዎቹ በዚህ አልተደሰቱም። በመሆኑም ይይዙት ዘንድ የቤተ መቅደስ ጠባቂዎችን ላኩ። (ዮሐንስ 7:31, 32) ያም ቢሆን ኢየሱስ ለመደበቅ አልሞከረም።

ከዚህ ይልቅ በኢየሩሳሌም በሕዝብ ፊት ማስተማሩን ቀጠለ፤ “ከእናንተ ጋር የምቆየው ለጥቂት ጊዜ ነው፤ ከዚያም ወደ ላከኝ እሄዳለሁ። እናንተ ትፈልጉኛላችሁ፤ ግን አታገኙኝም፤ ወደምሄድበትም ልትመጡ አትችሉም” አለ። (ዮሐንስ 7:33, 34) አይሁዳውያን የተናገረው ነገር ስላልገባቸው እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ፦ “ይህ ሰው ልናገኘው የማንችለው ወዴት ሊሄድ ቢያስብ ነው? በግሪካውያን መካከል ተበታትነው ወደሚገኙት አይሁዳውያን ሄዶ ግሪካውያንን ሊያስተምር አስቦ ይሆን እንዴ? ‘ትፈልጉኛላችሁ፤ ግን አታገኙኝም፤ ወደምሄድበትም ልትመጡ አትችሉም’ ሲል ምን ማለቱ ይሆን?” (ዮሐንስ 7:35, 36) ኢየሱስ ግን ስለ ሞቱ እና ትንሣኤ አግኝቶ ወደ ሰማይ ስለሚሄድበት ጊዜ እየተናገረ ነው፤ ጠላቶቹ ተከትለውት ወደ ሰማይ መሄድ አይችሉም።

ሰባተኛው የበዓሉ ቀን ደረሰ። በእያንዳንዱ የበዓሉ ቀን ጠዋት ላይ አንድ ካህን ከሰሊሆም መጥመቂያ ውኃ አምጥቶ ሲያፈስስ ውኃው ወደ መሠዊያው ሥር ይወርዳል። ኢየሱስ እንደሚከተለው በማለት ጮክ ብሎ ሲናገር ሕዝቡ ይህን ሥርዓት ሳያስታውሱ አይቀሩም፦ “የተጠማ ካለ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ። በእኔ የሚያምን ሁሉ ቅዱስ መጽሐፉ እንደሚለው ‘ሕይወት የሚሰጥ የውኃ ጅረት ከውስጡ ይፈስሳል።’”—ዮሐንስ 7:37, 38

ኢየሱስ ይህን ሲል፣ ደቀ መዛሙርቱ በመንፈስ ቅዱስ ሲቀቡና ሰማያዊ ጥሪ ለማግኘት ሲመረጡ የሚሆነውን ነገር መግለጹ ነው። ደቀ መዛሙርቱ በዚህ መንገድ የተቀቡት ኢየሱስ ከሞተ በኋላ ነው። በቀጣዩ ዓመት ከዋለው የጴንጤቆስጤ በዓል አንስቶ፣ በመንፈስ የተቀቡት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት እውነትን ለሰዎች ሲያስተምሩ ሕይወት የሚሰጠው የውኃ ጅረት መፍሰስ ጀመረ።

አንዳንዶች ኢየሱስ የተናገረውን ሲሰሙ “ይህ ሰው በእርግጥ ነቢዩ ነው” ይሉ ጀመር፤ ይህን ያሉት ሙሴ ከእሱ የሚበልጥ ነቢይ እንደሚነሳ የተነገረውን ትንቢት አስታውሰው መሆን አለበት። ሌሎችም “ይህ ክርስቶስ ነው” አሉ። አንዳንዶች ግን እንዲህ በማለት ተናገሩ፦ “ክርስቶስ የሚመጣው ከገሊላ ነው እንዴ? ቅዱስ መጽሐፉ ክርስቶስ ከዳዊት ዘርና ዳዊት ከኖረበት መንደር ከቤተልሔም እንደሚመጣ ይናገር የለም?”—ዮሐንስ 7:40-42

ስለዚህ በሕዝቡ መካከል ክፍፍል ተፈጠረ። አንዳንዶች ኢየሱስ ተይዞ እንዲታሰር ቢፈልጉም አንድም ሰው አልያዘውም። የቤተ መቅደሱ ጠባቂዎች ኢየሱስን ሳይዙት በተመለሱ ጊዜ የካህናት አለቆቹና ፈሪሳውያኑ “ለምን ይዛችሁት አልመጣችሁም?” አሏቸው። ጠባቂዎቹም “ማንም ሰው እንደዚህ ተናግሮ አያውቅም” ብለው መለሱ። የሃይማኖት መሪዎቹ ተበሳጭተው መተቸትና መሳደብ ጀመሩ፤ “እናንተም ተታለላችሁ? ከገዢዎች ወይም ከፈሪሳውያን መካከል በእሱ ያመነ አለ? ሕጉን የማያውቀው ይህ ሕዝብ ግን የተረገመ ነው” አሉ።—ዮሐንስ 7:45-49

በዚህ ጊዜ ኒቆዲሞስ የተባለ አንድ ፈሪሳዊና የሳንሄድሪን አባል ኢየሱስን በመደገፍ በድፍረት ተናገረ። ከሁለት ዓመት ተኩል ገደማ በፊት ኒቆዲሞስ በማታ ወደ ኢየሱስ መጥቶ በእሱ እንደሚያምን ገልጾለት ነበር። አሁን ደግሞ ኒቆዲሞስ “ሕጋችን በመጀመሪያ ግለሰቡ የሚለውን ሳይሰማና ምን እያደረገ እንዳለ ሳያውቅ ይፈርድበታል?” አለ። የሃይማኖት መሪዎቹ ምን ምላሽ ሰጡ? “አንተም ደግሞ ከገሊላ ነህ? ከገሊላ አንድም ነቢይ እንደማይነሳ ቅዱሳን መጻሕፍትን መርምረህ ተረዳ” አሉት።—ዮሐንስ 7:51, 52

ቅዱሳን መጻሕፍት ነቢይ ከገሊላ እንደሚነሳ በቀጥታ አይናገሩም። ያም ቢሆን የአምላክ ቃል ክርስቶስ የሚመጣው ከዚያ እንደሆነ ይገልጻል፤ “የአሕዛብ ገሊላ” “ታላቅ ብርሃን” እንደሚያይ ትንቢት ተነግሯል። (ኢሳይያስ 9:1, 2፤ ማቴዎስ 4:13-17) ከዚህም በላይ አስቀድሞ እንደተነገረው ኢየሱስ የተወለደው በቤተልሔም ነው፤ እንዲሁም የዳዊት ዘር ነው። ፈሪሳውያን ይህን ሳያውቁ አይቀሩም፤ ስለ ኢየሱስ በሕዝቡ መካከል የተሳሳተ አስተሳሰብ እንዲስፋፋ ያደረጉት እነሱ መሆን አለባቸው።