በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ አሥራ አራት

ቤተሰብህ ደስተኛ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው?

ቤተሰብህ ደስተኛ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው?

1, 2. ይሖዋ ቤተሰቦች ምን ዓይነት ሕይወት እንዲኖራቸው ይፈልጋል?

ትዳርን የመሠረተው ይሖዋ አምላክ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክ የመጀመሪያዋን ሴት ከፈጠረ በኋላ “ወደ ሰውየው አመጣት” በማለት ይናገራል። አዳም በጣም ከመደሰቱ የተነሳ “እሷ የአጥንቶቼ አጥንት፣ የሥጋዬም ሥጋ ናት” ብሎ ነበር። (ዘፍጥረት 2:22, 23) ከዚህ መረዳት እንደምንችለው ይሖዋ ባለትዳሮች ደስተኛ እንዲሆኑ ይፈልጋል።

2 የሚያሳዝነው ግን ብዙ ሰዎች በቤተሰባቸው ሕይወት ደስተኛ አይደሉም። ይሁንና መጽሐፍ ቅዱስ ቤተሰብ ደስተኛ እንዲሆን የሚረዱ ብዙ መሠረታዊ ሥርዓቶችን ይዟል፤ በዚህ ረገድ እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ምን ድርሻ ሊያበረክት እንደሚችል እንመለከታለን።—ሉቃስ 11:28

ባሎች ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል?

3, 4. (ሀ) አንድ ባል ሚስቱን እንዴት መያዝ አለበት? (ለ) ባልና ሚስት እርስ በርስ ይቅር መባባላቸው አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

3 መጽሐፍ ቅዱስ፣ አንድ ጥሩ ባል ሚስቱን መውደድና ማክበር እንዳለበት ይናገራል። እባክህ ኤፌሶን 5:25-29ን አንብብ። አንድ ባል ምንጊዜም ሚስቱን በፍቅር መያዝ ይኖርበታል። በተጨማሪም ጥበቃና እንክብካቤ ሊያደርግላት እንዲሁም እሷን የሚጎዳ ነገር ከማድረግ ሊቆጠብ ይገባል።

4 አንድ ባል፣ ሚስቱ ስህተት በምትሠራበት ጊዜስ ምን ማድረግ ይኖርበታል? ባሎች “ሚስቶቻችሁን መውደዳችሁን ቀጥሉ፤ መራራ ቁጣም አትቆጧቸው” የሚል መመሪያ ተሰጥቷቸዋል። (ቆላስይስ 3:19) ባሎች፣ እነሱም ስህተት እንደሚሠሩ ማስታወስ ይኖርባቸዋል። አምላክ በደላቸውን ይቅር እንዲላቸው የሚፈልጉ ከሆነ እነሱም ሚስቶቻቸውን ይቅር ማለት አለባቸው። (ማቴዎስ 6:12, 14, 15) ባልና ሚስት እርስ በርስ ይቅር የሚባባሉ ከሆነ ትዳራቸው ደስታ የሰፈነበት ይሆናል።

5. አንድ ባል ሚስቱን ማክበር ያለበት ለምንድን ነው?

5 ይሖዋ፣ ባሎች ሚስቶቻቸውን እንዲያከብሩ ይጠብቅባቸዋል። አንድ ባል የሚስቱን ቁሳዊና ስሜታዊ ፍላጎቶች ለማሟላት ጥረት ማድረግ አለበት። ይህ በቁም ነገር ሊታሰብበት የሚገባ ጉዳይ ነው። ምክንያቱም አንድ ባል ሚስቱን በተገቢው መንገድ የማይዝ ከሆነ ይሖዋ ጸሎቱን ላይሰማው ይችላል። (1 ጴጥሮስ 3:7) ይሖዋ ወንዶችን ከሴቶች አስበልጦ አይመለከትም። ይሖዋን የሚወዱ ሰዎች ሁሉ በእሱ ፊት ውድ ናቸው።

6. ባልና ሚስት “አንድ ሥጋ ናቸው” ሲባል ምን ማለት ነው?

6 ኢየሱስ፣ ባልና ሚስት “አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ሁለት አይደሉም” ብሏል። (ማቴዎስ 19:6) እንዲህ ሲባል አንዳቸው ለሌላው ምንጊዜም ታማኝ መሆን አለባቸው ማለት ነው። (ምሳሌ 5:15-21፤ ዕብራውያን 13:4) ባሎችም ሆኑ ሚስቶች ራስ ወዳድ መሆን የለባቸውም፤ ከዚህ ይልቅ አንዳቸው የሌላውን የፆታ ፍላጎት ማሟላት ይኖርባቸዋል። (1 ቆሮንቶስ 7:3-5) አንድ ባል የሚከተለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ማስታወስ ይኖርበታል፦ “የገዛ አካሉን የሚጠላ ማንም ሰው የለምና፤ ከዚህ ይልቅ ይመግበዋል እንዲሁም ይሳሳለታል።” ስለሆነም ሚስቱን ሊወዳትና ሊሳሳላት ይገባል። ሚስቶች ከምንም በላይ ባሎቻቸው ደጎችና አፍቃሪዎች እንዲሆኑ ይፈልጋሉ።—ኤፌሶን 5:29

ሚስቶች ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል?

7. አንድ ቤተሰብ፣ የቤተሰብ ራስ የሚያስፈልገው ለምንድን ነው?

7 እያንዳንዱ ቤተሰብ አመራር የሚሰጥ ራስ ያስፈልገዋል፤ ይህም የቤተሰቡ አባላት ተስማምተው እንዲኖሩ ይረዳቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ በ1 ቆሮንቶስ 11:3 ላይ “የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣ የሴትም ራስ ወንድ፣ የክርስቶስ ራስ ደግሞ አምላክ [ነው]” ይላል።

8. አንዲት ሚስት ለባሏ ጥልቅ አክብሮት እንዳላት ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?

8 የትኛውም ባል ስህተት ይሠራል። ሆኖም አንዲት ሚስት የባሏን ውሳኔ የምትደግፍና ከእሱ ጋር ተባብራ የምትሠራ ከሆነ መላው ቤተሰብ ይጠቀማል። (1 ጴጥሮስ 3:1-6) መጽሐፍ ቅዱስ “ሚስት ባሏን በጥልቅ ታክብር” ይላል። (ኤፌሶን 5:33) ይሁንና ባሏ ከእሷ የተለየ እምነት ቢኖረውስ? በዚህ ጊዜም ቢሆን ለባሏ ጥልቅ አክብሮት ሊኖራት ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “እናንተ ሚስቶች፣ ለቃሉ የማይታዘዙ ባሎች ካሉ ያለ ቃል በሚስቶቻቸው ምግባር እንዲማረኩ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ሊማረኩ የሚችሉትም ንጹሕ ምግባራችሁንና የምታሳዩትን ጥልቅ አክብሮት ሲመለከቱ ነው።” (1 ጴጥሮስ 3:1, 2) አንዲት ሚስት ጥሩ ምሳሌ መሆኗ ባሏ ስለ እምነቷ በቂ ግንዛቤ እንዲኖረው ሊያደርግ ይችላል፤ ይህም እምነቷን እንዲያከብርላት ያነሳሳው ይሆናል።

9. (ሀ) አንዲት ሚስት በባሏ ሐሳብ በማትስማማበት ጊዜ ምን ማድረግ ይኖርባታል? (ለ) ቲቶ 2:4, 5 ለሚስቶች ምን ምክር ይሰጣል?

9 አንዲት ሚስት በባሏ ሐሳብ በማትስማማበት ጊዜ ምን ማድረግ ይኖርባታል? ሐሳቧን በአክብሮት መግለጽ አለባት። ለምሳሌ ሣራ በአንድ ወቅት፣ የተሰማትን ስሜት ለአብርሃም ገልጻ ነበር፤ አብርሃም ሣራ ባቀረበችው ሐሳብ ቅር ተሰኝቶ የነበረ ቢሆንም ይሖዋ “የምትልህን ስማ” ብሎታል። (ዘፍጥረት 21:9-12) አብዛኛውን ጊዜ፣ አንድ ክርስቲያን ባል የሚያደርገው ውሳኔ ከመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር አይጋጭም፤ በመሆኑም ሚስቱ ባለቤቷ የሚያደርገውን ውሳኔ ልትደግፍ ይገባል። (የሐዋርያት ሥራ 5:29፤ ኤፌሶን 5:24) ጥሩ ሚስት ቤተሰቧን ትንከባከባለች። (ቲቶ 2:4, 5ን አንብብ።) ባለቤቷና ልጆቿ ለእነሱ ስትል ምን ያህል እንደምትለፋ ሲመለከቱ ለእሷ ያላቸው ፍቅርና አክብሮት ይጨምራል።—ምሳሌ 31:10, 28

ሣራ ለሚስቶች ጥሩ ምሳሌ የምትሆነው እንዴት ነው?

10. መጽሐፍ ቅዱስ መለያየትንና ፍቺን በተመለከተ ምን ይላል?

10 አንዳንድ ጊዜ ባለትዳሮች ለመለያየት አሊያም ለመፋታት ይቸኩላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን “ሚስት ከባሏ አትለያይ። . . . ባልም ሚስቱን መተው የለበትም” ይላል። (1 ቆሮንቶስ 7:10, 11) ባለትዳሮች ለመለያየት ሊወስኑ የሚችሉባቸው አንዳንድ ከባድ ሁኔታዎች ቢኖሩም ይህ በጥንቃቄ ሊታሰብበት የሚገባ ውሳኔ ነው። ፍቺን በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? ለፍቺ ሊያበቃ የሚችለው ብቸኛው ምክንያት ከሁለት አንዳቸው የትዳር ጓደኛቸው ካልሆነ ሰው ጋር የፆታ ግንኙነት ከፈጸሙ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል።—ማቴዎስ 19:9

ወላጆች ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል?

ኢየሱስ ለእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ጥሩ ምሳሌ ነው

11. ልጆች ከምንም በላይ የሚያስፈልጋቸው ነገር ምንድን ነው?

11 ወላጆች፣ ከልጆቻችሁ ጋር ረዘም ያለ ጊዜ ለማሳለፍ ጥረት አድርጉ። ልጆቻችሁ የሚፈልጉት እናንተን ነው፤ ከምንም በላይ ደግሞ ስለ ይሖዋ እንድታስተምሯቸው ይፈልጋሉ።—ዘዳግም 6:4-9

12. ወላጆች ልጆቻቸውን ከአደጋ ለመጠበቅ ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል?

12 የሰይጣን ዓለም በክፋት እየተሞላ ሄዷል፤ አንዳንድ ሰዎች፣ በልጆቻችሁ ላይ ጉዳት ለማድረስ እንዲሁም ፆታዊ ጥቃት ለመፈጸም ይሞክሩ ይሆናል። አንዳንድ ወላጆች ስለዚህ ጉዳይ ከልጆቻቸው ጋር ማውራት ይከብዳቸዋል። ሆኖም ወላጆች፣ ልጆቻቸው እንዲህ ካሉ ሰዎች ራሳቸውን እንዲጠብቁ ማስጠንቀቂያ ሊሰጧቸው እንዲሁም ይህን ማድረግ የሚችሉት እንዴት እንደሆነ ሊያስተምሯቸው ይገባል። ወላጆች፣ ለልጆቻችሁ ጥበቃ ማድረግ ይኖርባችኋል። *1 ጴጥሮስ 5:8

13. ወላጆች ልጆቻቸውን ማስተማር ያለባቸው እንዴት ነው?

13 ወላጆች፣ ልጆቻቸው ሥርዓታማ እንዲሆኑ የማስተማር ኃላፊነት አለባቸው። ልጆቻችሁን ማስተማር የምትችሉት እንዴት ነው? ልጆቻችሁ ሥልጠና ያስፈልጋቸዋል፤ ሆኖም የሚሰጣቸው እርማት ጭካኔ የሚንጸባረቅበትና ርኅራኄ የጎደለው መሆን የለበትም። (ኤርምያስ 30:11) በመሆኑም ተበሳጭታችሁ ባላችሁበት ሰዓት ልጆቻችሁን መገሠጽ የለባችሁም። ምክንያቱም በዚህ ጊዜ የምትናገሩት ነገር ‘እንደ ሰይፍ ሊወጋቸውና’ ሊጎዳቸው ይችላል። (ምሳሌ 12:18) ልጆቻችሁ ታዛዥ መሆን ያለባቸው ለምን እንደሆነ እንዲገነዘቡ እርዷቸው።—ኤፌሶን 6:4፤ ዕብራውያን 12:9-11ተጨማሪ ሐሳብ 30⁠ን ተመልከት።

ልጆች ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል?

14, 15. ልጆች ወላጆቻቸውን መታዘዝ ያለባቸው ለምንድን ነው?

14 ኢየሱስ አስቸጋሪ ሁኔታ በሚያጋጥመው ጊዜም እንኳ አባቱን ይታዘዝ ነበር። (ሉቃስ 22:42፤ ዮሐንስ 8:28, 29) ይሖዋ፣ ልጆች ወላጆቻቸውን እንዲታዘዙ ይፈልጋል።—ኤፌሶን 6:1-3

15 አንዳንድ ጊዜ ወላጆቻችሁን መታዘዝ ሊከብዳችሁ ይችላል፤ ሆኖም ታዛዦች ከሆናችሁ ይሖዋንም ሆነ ወላጆቻችሁን ታስደስታላችሁ። *ምሳሌ 1:8፤ 6:20፤ 23:22-25

ወጣቶች ተገቢ ያልሆነ ነገር እንዲያደርጉ ሲፈተኑ ለአምላክ ታማኝ ለመሆን ምን ሊረዳቸው ይችላል?

16. (ሀ) ሰይጣን፣ ወጣቶች ተገቢ ያልሆነ ነገር እንዲፈጽሙ ለማድረግ የሚሞክረው እንዴት ነው? (ለ) ይሖዋን የሚወዱ ጓደኞች መምረጥህ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

16 ዲያብሎስ ጓደኞችህን አሊያም ሌሎች ወጣቶችን ተጠቅሞ ተገቢ ያልሆነ ነገር እንድትፈጽም ሊፈትንህ ይችላል። እንዲህ ያለውን ተጽዕኖ መቋቋም ሊከብድህ እንደሚችል ያውቃል። ለምሳሌ የያዕቆብ ልጅ ዲና ይሖዋን የማይወዱ ጓደኞች ነበሯት። ይህም በእሷም ሆነ በቤተሰቦቿ ላይ ብዙ ችግር አስከትሏል። (ዘፍጥረት 34:1, 2) ጓደኞችህ ይሖዋን የማይወዱ ከሆነ ይሖዋ የሚጠላውን ነገር እንድታደርግ ሊፈትኑህ ይችላሉ፤ እንዲህ ያለውን ነገር ካደረግክ ችግር ላይ ልትወድቅ ትችላለህ፤ ይህ ደግሞ አምላክም ሆነ ወላጆችህ እንዲያዝኑ ሊያደርግ ይችላል። (ምሳሌ 17:21, 25) ይሖዋን የሚወዱ ጓደኞች መምረጥ ያለብህ ለዚህ ነው።—1 ቆሮንቶስ 15:33

ቤተሰብህ ደስተኛ ሊሆን የሚችለው እንዴት ነው?

17. እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ምን ኃላፊነት አለበት?

17 እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል የአምላክን መመሪያዎች የሚከተል ከሆነ ብዙ ችግሮች ሊወገዱ ይችላሉ። በመሆኑም ባል ከሆንክ ሚስትህን ውደድ፤ እንዲሁም ደግነትና አሳቢነት በሚንጸባረቅበት መንገድ ያዛት። ሚስት ከሆንሽ ባልሽን አክብሪ እንዲሁም ለእሱ ተገዢ፤ በተጨማሪም በምሳሌ 31:10-31 ላይ የተገለጸችውን ሚስት ምሳሌ ለመከተል ጥረት አድርጊ። ወላጅ ከሆንክ ልጆችህ አምላክን እንዲወዱ አስተምራቸው። (ምሳሌ 22:6) አባት ከሆንክ ቤተሰብህን “በተገቢው ሁኔታ” ምራ። (1 ጢሞቴዎስ 3:4, 5፤ 5:8) ልጆች ደግሞ ለወላጆቻችሁ ታዘዙ። (ቆላስይስ 3:20) የትኛውም የቤተሰብ አባል ስህተት ሊሠራ እንደሚችል አስታውሱ፤ በመሆኑም ስህተት ከሠራችሁ በትሕትና ይቅርታ ጠይቁ። በእርግጥም ይሖዋ ለእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል የሰጠው መመሪያ ጠቃሚ ነው።

^ አን.12 ለልጆቻችሁ ጥበቃ ማድረግ የምትችሉበትን መንገድ በተመለከተ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ከታላቁ አስተማሪ ተማር የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 32 ተመልከቱ።

^ አን.15 አንድ ልጅ፣ ወላጆቹ ከአምላክ ሕግ ጋር የሚጋጭ ነገር እንዲያደርግ ካዘዙት እነሱን መታዘዝ አይኖርበትም።—የሐዋርያት ሥራ 5:29