በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ አሥራ ዘጠኝ

ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት አጠናክር

ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት አጠናክር

1, 2. በዛሬው ጊዜ ጥበቃ የምናገኘው ከየት ነው?

በእግርህ እየተጓዝክ ሳለ ኃይለኛ ነፋስ መንፈስ ጀመረ እንበል። ሰማዩ እየጠቆረ መጥቷል፤ መብረቅ ብልጭ ይላል እንዲሁም የነጎድጓድ ድምፅ ይሰማል። ብዙም ሳይቆይ ከባድ ዝናብ መዝነብ ጀመረ። ከዝናቡ የምትጠለልበት ቦታ መፈለግ ጀመርክ። በመጨረሻም ጥሩ መጠለያ አገኘህ፤ በዚህ ጊዜ በጣም እንደምትደሰት ጥርጥር የለውም!

2 እኛ የምንገኝበት ሁኔታም ተመሳሳይ ነው። የዓለም ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ ነው። በመሆኑም ‘ጥበቃ ማግኘት የምችለው ከየት ነው?’ ብለህ ታስብ ይሆናል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰው መዝሙራዊ “ይሖዋን ‘አንተ መጠጊያዬና ምሽጌ፣ የምታመንብህም አምላኬ ነህ’ እለዋለሁ” በማለት ጽፏል። (መዝሙር 91:2) ይሖዋ በዛሬው ጊዜ ባለው በችግር የተሞላ ዓለም ውስጥ ጥበቃ ያደርግልናል፤ ለወደፊቱ ጊዜ ደግሞ አስደሳች ተስፋ ሰጥቶናል።

3. ይሖዋን መጠጊያችን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

3 ይሖዋ ጥበቃ የሚያደርግልን እንዴት ነው? ይሖዋ የሚያጋጥመንን ማንኛውንም ችግር መቋቋም እንድንችል ይረዳናል፤ ደግሞም በእኛ ላይ ጉዳት ለማድረስ ከሚሞክር ከማንኛውም አካል የበለጠ ኃይል አለው። አሁን መጥፎ ነገር ቢያጋጥመንም እንኳ ወደፊት ይሖዋ ከደረሰብን ችግር ሊገላግለን እንደሚችል እርግጠኞች መሆን እንችላለን። አስቸጋሪ ሁኔታ ሲያጋጥመን ይሖዋ እንዲረዳንና መጠጊያ እንዲሆነን ከፈለግን ከእሱ ጋር ተቀራርበን መኖር አለብን። መጽሐፍ ቅዱስ ‘ከአምላክ ፍቅር ሳትወጡ ኑሩ’ በማለት ያበረታታናል። (ይሁዳ 21) ይሁንና እንዲህ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

አምላክ ላሳየህ ፍቅር አመስጋኝ ሁን

4, 5. ይሖዋ ለእኛ ያለውን ፍቅር ያሳየው እንዴት ነው?

4 ከይሖዋ ጋር ያለንን ወዳጅነት ማጠናከር እንድንችል እሱ ምን ያህል እንደሚወደን መገንዘባችን በጣም አስፈላጊ ነው። ይሖዋ ስላደረገልን ነገሮች እስቲ ቆም ብለህ አስብ። ውብ የሆነች ምድር ሰጥቶናል፤ እንዲሁም ምድርን በሚያማምሩ ተክሎችና እንስሳት ሞልቷታል። በተጨማሪም የምንበላው ጣፋጭ ምግብና የምንጠጣው ንጹሕ ውኃ ሰጥቶናል። ይሖዋ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ስሙንና ግሩም የሆኑ ባሕርያቱን ገልጾልናል። ከሁሉ በላይ ደግሞ የሚወደውን ልጁን ኢየሱስን ወደ ምድር በመላክ ለእኛ ሲል ሕይወቱን እንዲሰጥ አድርጓል፤ ይህም ለእኛ ያለውን ፍቅር ያሳያል። (ዮሐንስ 3:16) ኢየሱስ ለእኛ ሲል መሞቱ ለወደፊቱ ጊዜ አስደሳች ተስፋ እንዲኖረን አድርጓል።

5 ይሖዋ መሲሐዊውን መንግሥት አቋቁሟል፤ ይህ መንግሥት መከራን ሁሉ ከዓለም ላይ የሚያስወግድ በሰማይ የተቋቋመ መስተዳድር ነው። መሲሐዊው መንግሥት፣ ምድር ሰዎች ሁሉ በሰላምና በደስታ ለዘላለም የሚኖሩባት ገነት እንድትሆን ያደርጋል። (መዝሙር 37:29) ይሖዋ ለእኛ ያለውን ፍቅር ያሳየበት ሌላው መንገድ ደግሞ በዛሬው ጊዜም እንኳ ከሁሉ በተሻለ ሁኔታ መኖር የምንችልበትን መንገድ በማስተማር ነው። በተጨማሪም ወደ እሱ እንድንጸልይ ግብዣ ያቀረበልን ከመሆኑም በላይ ጸሎታችንን ለመስማት ምንጊዜም ዝግጁ ነው። በእርግጥም ይሖዋ ለእያንዳንዳችን ያለውን ፍቅር በግልጽ አሳይቷል።

6. ይሖዋ ላሳየህ ፍቅር ምን ምላሽ መስጠት አለብህ?

6 ይሖዋ ላሳየህ ፍቅር ምን ምላሽ መስጠት አለብህ? ላደረገልህ ነገር ሁሉ አመስጋኝ እንደሆንክ አሳይ። የሚያሳዝነው፣ በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች አመስጋኝ አይደሉም። ኢየሱስ ምድር ላይ በኖረበት ዘመንም ሁኔታው ተመሳሳይ ነበር። በአንድ ወቅት ኢየሱስ በሥጋ ደዌ በሽታ የተያዙ አሥር ሰዎችን የፈወሰ ቢሆንም ለተደረገለት ነገር ያመሰገነው አንዱ ብቻ ነበር። (ሉቃስ 17:12-17) እኛ ኢየሱስን እንዳመሰገነው ሰው መሆን እንደምንፈልግ የታወቀ ነው። ይሖዋ ላደረገልን ነገር ምንጊዜም አመስጋኞች መሆን ይኖርብናል።

7. ይሖዋን ምን ያህል ልንወደው ይገባል?

7 በተጨማሪም ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ማሳየት አለብን። ኢየሱስ፣ ደቀ መዛሙርቱ በሙሉ ልባቸው፣ በሙሉ ነፍሳቸውና በሙሉ አእምሯቸው ይሖዋን መውደድ እንዳለባቸው ነግሯቸው ነበር። (ማቴዎስ 22:37ን አንብብ።) ይህ ምን ማለት ነው?

8, 9. ይሖዋን እንደምንወደው ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

8 ‘ይሖዋን እወደዋለሁ’ ብሎ መናገር ብቻ በቂ ነው? አይደለም። ይሖዋን በሙሉ ልባችን፣ ነፍሳችንና አእምሯችን የምንወደው ከሆነ ለእሱ ያለንን ፍቅር በተግባር እናሳያለን። (ማቴዎስ 7:16-20) መጽሐፍ ቅዱስ፣ አምላክን የምንወደው ከሆነ ትእዛዛቱን መጠበቅ እንዳለብን በግልጽ ይናገራል። እንዲህ ማድረግ ከባድ ነው? በፍጹም፤ ምክንያቱም የይሖዋ ‘ትእዛዛት ከባድ አይደሉም።’—1 ዮሐንስ 5:3ን አንብብ።

9 ይሖዋን የምንታዘዝ ከሆነ ሕይወታችን አስደሳችና አርኪ ይሆናል። (ኢሳይያስ 48:17, 18) ይሁንና ከይሖዋ ጋር ያለንን ወዳጅነት ለማጠናከር ምን ሊረዳን ይችላል? ምን ሊረዳን እንደሚችል እስቲ እንመልከት።

ወደ ይሖዋ ይበልጥ ለመቅረብ ጥረት አድርግ

10. ስለ ይሖዋ መማርህን መቀጠል ያለብህ ለምንድን ነው?

10 የይሖዋ ወዳጅ መሆን የቻልከው እንዴት ነው? መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናትህ ይሖዋን ይበልጥ እንድታውቀውና ከእሱ ጋር ወዳጅነት እንድትመሠርት አስችሎሃል። ይህ ወዳጅነት ከእሳት ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ያቀጣጠልከው እሳት መንደዱን እንዲቀጥል ከፈለግክ እንጨት መጨመር አለብህ፤ ከይሖዋ ጋር የመሠረትከው ወዳጅነትም ምንጊዜም ጠንካራ እንዲሆን ከፈለግክ ስለ ይሖዋ መማርህን መቀጠል ይኖርብሃል።—ምሳሌ 2:1-5

ለይሖዋ ያለህ ፍቅር እንዳይጠፋ ልክ እንደ እሳት መንደዱን እንዲቀጥል የሚያደርግ ነገር ያስፈልገዋል

11. መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናትህን ስትቀጥል ምን ጥቅም ታገኛለህ?

11 መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናትህን ስትቀጥል ልብህን የሚነኩ ተጨማሪ ነገሮች ትማራለህ። ሁለት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት፣ ኢየሱስ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶችን ሲያብራራላቸው ምን እንደተሰማቸው እስቲ ተመልከት። ደቀ መዛሙርቱ “በመንገድ ላይ ሲያነጋግረንና ቅዱሳን መጻሕፍትን በሚገባ ሲገልጥልን ልባችን እንደ እሳት ይቃጠልብን አልነበረም?” በማለት ተናግረዋል።—ሉቃስ 24:32

12, 13. (ሀ) ለአምላክ ያለን ፍቅር ከጊዜ በኋላ ምን ሊሆን ይችላል? (ለ) ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ማጠናከር የምንችለው እንዴት ነው?

12 የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በቅዱሳን መጻሕፍት ላይ የሚገኘውን ሐሳብ ሲረዱ ልባቸው በጣም ተነክቶ ነበር፤ አንተም የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ግልጽ ሲሆንልህ ተመሳሳይ ስሜት ተሰምቶህ ሊሆን ይችላል። ይህም ይሖዋን ይበልጥ እንድታውቀውና እሱን እንድትወደው አስችሎሃል። ይህ ፍቅርህ እንዲቀዘቅዝ አትፍቀድ።—ማቴዎስ 24:12

13 ከአምላክ ጋር ወዳጅነት ከመሠረትክ በኋላ ይህን ወዳጅነት ለማጠናከር ከፍተኛ ጥረት ማድረግ አለብህ። ስለ ይሖዋና ስለ ኢየሱስ ይበልጥ ማወቅ፣ በተማርከው ነገር ላይ ማሰላሰል እንዲሁም ትምህርቱን ተግባራዊ ልታደርግ የምትችለው እንዴት እንደሆነ ማሰብ ይኖርብሃል። (ዮሐንስ 17:3) መጽሐፍ ቅዱስን በምታነብበትና በምታጠናበት ጊዜ ራስህን የሚከተሉትን ጥያቄዎች ጠይቅ፦ ‘ይህ ስለ ይሖዋ አምላክ ምን ያስተምረኛል? በሙሉ ልቤና በሙሉ ነፍሴ ልወደው የሚገባኝ ለምንድን ነው?’—1 ጢሞቴዎስ 4:15

14. ጸሎት፣ ለይሖዋ ያለን ፍቅር ምንጊዜም ጠንካራ እንዲሆን የሚረዳን እንዴት ነው?

14 አንድ የምትቀርበው ጓደኛ ቢኖርህ ከእሱ ጋር በየጊዜው እንደምታወራ ግልጽ ነው፤ ይህም ጓደኝነታችሁ ጠንካራ ሆኖ እንዲቀጥል ያስችላል። በተመሳሳይም አዘውትረን ወደ ይሖዋ በመጸለይ ከእሱ ጋር የምንነጋገር ከሆነ ለእሱ ያለን ፍቅር ምንጊዜም ጠንካራ ይሆናል። (1 ተሰሎንቄ 5:17ን አንብብ።) ጸሎት ከሰማዩ አባታችን ያገኘነው ውድ ስጦታ ነው። የልባችንን ስሜት በመግለጽ ከእሱ ጋር ዘወትር መነጋገር ይኖርብናል። (መዝሙር 62:8) ጸሎታችን የተሸመደደ መሆን የለበትም፤ ከዚህ ይልቅ ከልብ የመነጨ መሆን አለበት። አዎ፣ አዘውትረን መጽሐፍ ቅዱስን የምናጠናና ከልባችን የምንጸልይ ከሆነ ለይሖዋ ያለን ፍቅር ምንጊዜም ጠንካራ ይሆናል።

ለሌሎች ስለ ይሖዋ ተናገር

15, 16. ስለ ስብከቱ ሥራ ምን ይሰማሃል?

15 ከይሖዋ ጋር ያለንን ወዳጅነት ማጠናከር የምንፈልግ ከሆነ ማድረግ የሚኖርብን ሌላው ነገር፣ ስለ እምነታችን ለሌሎች መናገር ነው። ለሌሎች ስለ ይሖዋ መናገር ትልቅ መብት ነው። (ሉቃስ 1:74) በተጨማሪም ኢየሱስ ለእውነተኛ ክርስቲያኖች በሙሉ የሰጠው ኃላፊነት ነው። ሁላችንም የአምላክን መንግሥት ምሥራች መስበክ አለብን። አንተስ ምሥራቹን መስበክ ጀምረሃል?—ማቴዎስ 24:14፤ 28:19, 20

16 ሐዋርያው ጳውሎስ የስብከቱን ሥራ ከፍ አድርጎ ይመለከተው ስለነበር “ውድ ሀብት” በማለት ጠርቶታል። (2 ቆሮንቶስ 4:7) ስለ ይሖዋና ስለ ዓላማው ለሌሎች መናገር ከማንኛውም ሥራ የበለጠ ቦታ የሚሰጠው ነው። ይህ ሥራ፣ ይሖዋን ለማገልገል ያስችልሃል፤ ይሖዋ ደግሞ ለእሱ ስትል የምታደርገውን ነገር ከፍ አድርጎ ይመለከታል። (ዕብራውያን 6:10) በተጨማሪም የስብከቱ ሥራ ለአንተም ሆነ ለሚሰሙህ ሰዎች ከፍተኛ ጥቅም ያስገኛል፤ ምክንያቱም በዚህ ሥራ አማካኝነት አንተም ሆንክ የምትሰብክላቸው ሰዎች ከይሖዋ ጋር መቀራረብና የዘላለም ሕይወት ማግኘት ትችላላችሁ። (1 ቆሮንቶስ 15:58ን አንብብ።) ታዲያ ከዚህ በላይ አርኪ የሆነ ሥራ አለ?

17. የስብከቱ ሥራ አጣዳፊ የሆነው ለምንድን ነው?

17 የስብከቱ ሥራ በጣም አጣዳፊ ነው። ‘ቃሉን መስበክ’ እንዲሁም ‘በጥድፊያ ስሜት ማገልገል’ ይኖርብናል። (2 ጢሞቴዎስ 4:2) ሰዎች ስለ አምላክ መንግሥት መስማት ያስፈልጋቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ “ታላቁ የይሖዋ ቀን ቅርብ ነው! ቅርብ ነው፤ ደግሞም በፍጥነት እየቀረበ ነው!” ይላል፤ እንዲሁም መጨረሻው “አይዘገይም!” በማለት ይናገራል። (ሶፎንያስ 1:14፤ ዕንባቆም 2:3) አዎ፣ በቅርቡ ይሖዋ የሰይጣንን ክፉ ዓለም ያጠፋል። በመሆኑም ሰዎች ጥፋቱ ከመምጣቱ በፊት ማስጠንቀቂያ ሊሰጣቸው ይገባል፤ ይህም ይሖዋን ለማገልገል ሊያነሳሳቸው ይችላል።

18. ይሖዋን ከሌሎች እውነተኛ ክርስቲያኖች ጋር ማምለክ ያለብን ለምንድን ነው?

18 ይሖዋ፣ ከሌሎች እውነተኛ ክርስቲያኖች ጋር አብረን እንድናመልከው ይፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “እርስ በርስ ለፍቅርና ለመልካም ሥራዎች መነቃቃት እንድንችል አንዳችን ለሌላው ትኩረት እንስጥ፤ አንዳንዶች ልማድ እንዳደረጉት መሰብሰባችንን ቸል አንበል፤ ከዚህ ይልቅ እርስ በርስ እንበረታታ፤ ደግሞም ቀኑ እየቀረበ መምጣቱን ስናይ ከበፊቱ ይበልጥ ይህን እናድርግ።” (ዕብራውያን 10:24, 25) በሁሉም ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ ለመገኘት የቻልነውን ያህል ጥረት ማድረግ አለብን። እነዚህ ስብሰባዎች እርስ በርስ የምንበረታታበትና የምንተናነጽበት አጋጣሚ ይከፍቱልናል።

19. ክርስቲያን ወንድሞቻችንንና እህቶቻችንን ለመውደድ ምን ሊረዳን ይችላል?

19 በስብሰባዎች ላይ ስትካፈል ይሖዋን እንድታመልክ የሚረዱ ጥሩ ጓደኞች ታገኛለህ። እነዚህ ወንድሞችና እህቶች ልክ እንደ አንተ ይሖዋን ለማገልገል የቻሉትን ጥረት የሚያደርጉ ናቸው። በተጨማሪም ልክ እንደ አንተ ፍጹም ያልሆኑና ስህተት የሚሠሩ ናቸው። በመሆኑም ስህተት ሲሠሩ ይቅር ለማለት ፈቃደኛ ሁን። (ቆላስይስ 3:13ን አንብብ።) ምንጊዜም ክርስቲያን ወንድሞችህና እህቶችህ ባሏቸው መልካም ባሕርያት ላይ አተኩር፤ እንዲህ ማድረግህ እነሱን ለመውደድና ወደ ይሖዋ ይበልጥ ለመቅረብ ይረዳሃል።

እውነተኛው ሕይወት

20, 21. ‘እውነተኛው ሕይወት’ የተባለው ምንድን ነው?

20 ይሖዋ፣ ወዳጆቹ ከሁሉ የተሻለ ሕይወት እንዲኖራቸው ይፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ ወደፊት የሚኖረን ሕይወት አሁን ካለን ሕይወት በጣም የተለየ እንደሚሆን ይናገራል።

ይሖዋ “እውነተኛ የሆነውን ሕይወት” እንድታገኝ ይፈልጋል። ለዚህ ትበቃ ይሆን?

21 ወደፊት ለ70 ወይም ለ80 ዓመታት ብቻ ሳይሆን ለዘላለም እንኖራለን። የተሟላ ጤንነት፣ ሰላምና ደስታ አግኝተን ውብ በሆነች ገነት ውስጥ ‘ለዘላለም’ እንኖራለን። መጽሐፍ ቅዱስ ‘እውነተኛው ሕይወት’ በማለት የሚጠራው እንዲህ ያለውን ሕይወት ነው። ይሖዋ ይህን ሕይወት ሊሰጠን ቃል ገብቷል፤ ሆኖም እውነተኛውን ሕይወት ለማግኘት ዛሬውኑ ይህን ሕይወት ‘አጥብቀን ለመያዝ’ የተቻለንን ያህል ጥረት ማድረግ አለብን።—1 ጢሞቴዎስ 6:12, 19

22. (ሀ) ‘እውነተኛውን ሕይወት አጥብቀን መያዝ’ የምንችለው እንዴት ነው? (ለ) የዘላለም ሕይወት ይገባናል የምንለው ነገር ያልሆነው ለምንድን ነው?

22 ‘እውነተኛውን ሕይወት አጥብቀን መያዝ’ የምንችለው እንዴት ነው? ‘መልካም ነገር በማድረግ’ እንዲሁም ‘በመልካም ሥራዎች ባለጸጋ በመሆን’ ነው። (1 ጢሞቴዎስ 6:18) ከመጽሐፍ ቅዱስ የተማርነውን ትምህርት ተግባራዊ ማድረግ አለብን ማለት ነው። ሆኖም እውነተኛውን ሕይወት የምናገኘው በእኛ ጥረት አይደለም። የዘላለም ሕይወት ይገባናል የምንለው ነገር አይደለም። ከዚህ ይልቅ ይሖዋ ለታማኝ አገልጋዮቹ የሚሰጠው ነፃ ስጦታ ወይም የእሱ “ጸጋ” መግለጫ ነው። (ሮም 5:15) በሰማይ ያለው አባታችን ይህን ስጦታ ለታማኝ አገልጋዮቹ ሊሰጣቸው ይፈልጋል።

23. አሁን ትክክለኛ ምርጫ ማድረግ ያለብህ ለምንድን ነው?

23 እንግዲያው ‘አምላክን እሱ በሚፈልገው መንገድ እያመለክሁት ነው?’ ብለህ ራስህን መጠየቅህ አስፈላጊ ነው። አንዳንድ ለውጦችን ማድረግ እንዳለብህ ከተገነዘብክ ወዲያውኑ እርምጃ ውሰድ። በይሖዋ ስንታመንና እሱን ለመታዘዝ የቻልነውን ያህል ጥረት ስናደርግ መጠጊያችን ይሆንልናል። የሰይጣን ክፉ ሥርዓት ሊጠፋ በተቃረበባቸው በመጨረሻዎቹ ቀናት ውስጥ ይሖዋ ለታማኝ አገልጋዮቹ ጥበቃ ያደርጋል። ከዚያም ይሖዋ ቃል በገባው መሠረት ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የዘላለም ሕይወት ይሰጠናል። አዎ፣ አሁን ትክክለኛ ምርጫ ካደረግክ እውነተኛውን ሕይወት ልታገኝ ትችላለህ!