በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 7

የባቤል ግንብ

የባቤል ግንብ

ከጥፋት ውኃው በኋላ የኖኅ ልጆችና ሚስቶቻቸው ብዙ ልጆች ወለዱ። የቤተሰባቸው ቁጥር እየጨመረ ሲመጣ ልክ ይሖዋ እንደነገራቸው ወደተለያዩ ቦታዎች ተበታትነው መኖር ጀመሩ።

አንዳንድ ቤተሰቦች ግን ይሖዋን አልታዘዙም። እንዲህ አሉ፦ ‘አንድ ከተማ ገንብተን እዚሁ እንኑር። ቁመቱ ሰማይ የሚደርስ ረጅም ግንብ እንገነባለን። ከዚያም ታዋቂ እንሆናለን።’

ይሖዋ እነዚህ ሰዎች በሚያደርጉት ነገር አልተደሰተም፤ ስለዚህ ሥራቸውን ለማስቆም ወሰነ። ይህን ያደረገው እንዴት እንደሆነ ታውቃለህ? የተለያየ ቋንቋ እንዲናገሩ አደረጋቸው። በዚህ የተነሳ እርስ በርስ መግባባት ስላልቻሉ የግንባታ ሥራቸውን አቆሙ። እየገነቡት የነበረው ከተማ ባቤል ተባለ፤ ባቤል ማለት “ዝብርቅ” ማለት ነው። በመሆኑም ሰዎች ወደተለያዩ አካባቢዎች ተበታትነው በመላው ዓለም መኖር ጀመሩ። ነገር ግን በሄዱባቸው ቦታዎችም መጥፎ ነገር ማድረጋቸውን ቀጠሉ። ታዲያ በዚያ ጊዜ ይሖዋን የሚወድ ሰው አልነበረም ማለት ነው? በሚቀጥለው ምዕራፍ ላይ ይህን እንመለከታለን።

“ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳል፤ ራሱን ዝቅ የሚያደርግ ሁሉ ግን ከፍ ይደረጋል።”—ሉቃስ 18:14