በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 13

ያዕቆብና ኤሳው ታረቁ

ያዕቆብና ኤሳው ታረቁ

ይሖዋ አብርሃምንና ይስሐቅን እንደጠበቃቸው ሁሉ ያዕቆብንም እንደሚጠብቀው ቃል ገባለት። ያዕቆብ ካራን በሚባል ቦታ መኖር ጀመረ፤ በዚያም አግብቶ ትልቅ ቤተሰብ መሠረተ፤ እንዲሁም በጣም ሀብታም ሆነ።

ከጊዜ በኋላ ይሖዋ ያዕቆብን ‘ወደ አገርህ ተመልሰህ ሂድ’ አለው። ስለዚህ ያዕቆብ ቤተሰቡን ይዞ ወደተወለደበት አገር መጓዝ ጀመረ። መንገድ ላይ ሳሉ የያዕቆብ አገልጋዮች ወደ እሱ መጥተው ‘ወንድምህ ኤሳው እየመጣ ነው፤ 400 ሰዎችም አብረውት አሉ!’ አሉት። ያዕቆብ፣ ኤሳው በእሱና በቤተሰቡ ላይ ጉዳት እንዳያደርስ ፈራ። በመሆኑም ‘እባክህ ከወንድሜ እጅ አድነኝ’ በማለት ወደ ይሖዋ ጸለየ። በቀጣዩ ቀን ያዕቆብ ለኤሳው ብዙ በጎችን፣ ፍየሎችን፣ ላሞችን፣ ግመሎችንና አህዮችን ስጦታ አድርጎ ላከለት።

በዚያ ሌሊት ያዕቆብ ብቻውን እያለ አንድ መልአክ አየ! መልአኩ ከያዕቆብ ጋር መታገል ጀመረ። እስኪነጋ ድረስ ሲታገሉ ቆዩ። ያዕቆብ ጉዳት ቢደርስበትም መታገሉን አላቆመም። በዚህ ጊዜ መልአኩ ‘ልቀቀኝና ልሂድ’ አለው። ያዕቆብ ግን ‘ካልባረክኸኝ አልለቅህም’ አለው።

በመጨረሻም መልአኩ ያዕቆብን ባረከው። በዚህ ጊዜ ያዕቆብ ይሖዋ እንደሚረዳውና ኤሳው እሱን እንዲጎዳው እንደማይፈቅድ ተገነዘበ።

ያን ቀን ጠዋት ያዕቆብ ከርቀት ሲመለከት ኤሳውንና ከእሱ ጋር የነበሩትን 400 ሰዎች አያቸው። ያዕቆብ ከቤተሰቦቹ ቀድሞ በመሄድ በወንድሙ ፊት ሰባት ጊዜ ሰገደ። ኤሳውም ወደ ያዕቆብ እየሮጠ መጥቶ አቀፈው። ሁለቱ ወንድማማቾች ተላቀሱ፤ በዚህ መንገድ ኤሳውና ያዕቆብ ታረቁ። ይሖዋ፣ ያዕቆብ ያደረገውን ሲመለከት ምን የተሰማው ይመስልሃል?

ከዚህ በኋላ ኤሳው ወደ ቤቱ ተመለሰ፤ ያዕቆብ ደግሞ መንገዱን ቀጠለ። ያዕቆብ 12 ወንዶች ልጆች ነበሩት። ስማቸው ሮቤል፣ ስምዖን፣ ሌዊ፣ ይሁዳ፣ ዳን፣ ንፍታሌም፣ ጋድ፣ አሴር፣ ይሳኮር፣ ዛብሎን፣ ዮሴፍ እና ቢንያም ይባላል። ከጊዜ በኋላ ይሖዋ ዮሴፍን በመጠቀም ሕዝቡን አድኗል። ይህን ያደረገው እንዴት እንደሆነ ታውቃለህ? እስቲ እንመልከት።

“ጠላቶቻችሁን ውደዱ እንዲሁም ስደት ለሚያደርሱባችሁ ጸልዩ፤ ይህን ብታደርጉ በሰማያት ላለው አባታችሁ ልጆች ትሆናላችሁ።”—ማቴዎስ 5:44, 45