በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 36

ዮፍታሔ የገባው ቃል

ዮፍታሔ የገባው ቃል

እስራኤላውያን በድጋሚ ይሖዋን ትተው የሐሰት አማልክትን ማምለክ ጀመሩ። አሞናውያን ጥቃት ሰንዝረውባቸው ከእነሱ ጋር በተዋጉበት ወቅት እነዚህ የሐሰት አማልክት ምንም አልረዷቸውም። እስራኤላውያን ለብዙ ዓመታት ሥቃይ ደረሰባቸው። በመጨረሻም ይሖዋን ‘ኃጢአት ሠርተናል። እባክህ ከጠላቶቻችን አድነን’ ብለው ለመኑት። እስራኤላውያን ጣዖቶቻቸውን አስወግደው ይሖዋን ማምለክ ጀመሩ። ይሖዋም ሲሠቃዩ ማየት አልፈለገም።

በመሆኑም ዮፍታሔ የተባለ አንድ ተዋጊ ሕዝቡን እየመራ ከአሞናውያን ጋር እንዲዋጋ ተመረጠ። ዮፍታሔ ለይሖዋ እንዲህ በማለት ቃል ገባ፦ ‘ይህን ጦርነት እንድናሸንፍ ከረዳኸን፣ ወደ ቤት ስመለስ ሊቀበለኝ የሚወጣውን የመጀመሪያ ሰው ለአንተ እሰጥሃለሁ።’ ይሖዋም የዮፍታሔን ጸሎት ሰምቶ በጦርነቱ እንዲያሸንፍ ረዳው።

ዮፍታሔ ወደ ቤቱ ሲመለስ በመጀመሪያ ልትቀበለው የወጣችው ልጁ ነበረች፤ ዮፍታሔ ከእሷ ሌላ ልጅ አልነበረውም። እየጨፈረችና ከበሮ እየመታች ልትቀበለው ወጣች። ዮፍታሔ ምን ያደርግ ይሆን? ለይሖዋ የገባውን ቃል አስታወሰና እንዲህ አለ፦ ‘ወይኔ፣ ልጄ! ልቤን ሰበርሽው። ለይሖዋ ቃል ገብቻለሁ። የገባሁትን ቃል ለመጠበቅ ደግሞ በሴሎ ባለው የማደሪያ ድንኳን እንድታገለግዪ አንቺን መላክ አለብኝ።’ በዚህ ጊዜ ልጁ እንዲህ አለችው፦ ‘አባዬ፣ ለይሖዋ ቃል ከገባህ ቃልህን መጠበቅ አለብህ። ብቻ ወደ ተራሮች ሄጄ ከሴት ጓደኞቼ ጋር ለሁለት ወር ያህል አብሬ ጊዜ እንዳሳልፍ ፍቀድልኝ። ከዚያ እሄዳለሁ።’ ከዚያ በኋላ የዮፍታሔ ልጅ ዕድሜዋን በሙሉ በማደሪያ ድንኳኑ በታማኝነት አገልግላለች። ጓደኞቿም በየዓመቱ ወደ ሴሎ እየሄዱ ይጠይቋት ነበር።

“ከእኔ ይልቅ ወንድ ልጁን ወይም ሴት ልጁን የሚወድ ሁሉ ለእኔ ሊሆን አይገባም።”—ማቴዎስ 10:37