በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 39

የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ

የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ

ይሖዋ ለእስራኤላውያን የሚመሯቸው መሳፍንት ሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም እስራኤላውያን ግን በዚህ አልተደሰቱም። በመሆኑም ሳሙኤልን እንዲህ አሉት፦ ‘በዙሪያችን ያሉት አገሮች በሙሉ ንጉሥ አላቸው። እኛም ንጉሥ እንዲሾምልን እንፈልጋለን።’ ሳሙኤል እንዲህ ብለው መጠየቃቸው ተገቢ እንዳልሆነ ስለተሰማው ስለ ጉዳዩ ወደ ይሖዋ ጸለየ። ይሖዋም እንዲህ አለው፦ ‘ሕዝቡ አልቀበልም ያሉት አንተን ሳይሆን እኔን ነው። ስለዚህ ንጉሥ የሚሾምላቸው ቢሆንም ንጉሡ ከእነሱ ብዙ ነገር እንደሚጠብቅ ንገራቸው።’ ሕዝቡ ግን ይህን ቢነግራቸውም አልሰሙትም፤ ከዚህ ይልቅ ‘ምንም ችግር የለውም። ብቻ ንጉሥ ሹምልን!’ አሉት።

ይሖዋ፣ ሳኦል የተባለ ሰው የመጀመሪያው ንጉሥ እንደሚሆን ለሳሙኤል ነገረው። ሳኦል ሳሙኤልን ለማግኘት ወደ ራማ ሄደ፤ በዚህ ጊዜ ሳሙኤል በሳኦል ራስ ላይ ዘይት በማፍሰስ ንጉሥ አድርጎ ቀባው።

በኋላም ሳሙኤል አዲሱን ንጉሣቸውን ሊያሳያቸው እስራኤላውያንን ሰበሰበ። ግን ሳኦልን ሊያገኙት አልቻሉም። ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? ሳኦል ዕቃ መካከል ተደብቆ ስለነበር ነው። በመጨረሻም ሳኦልን ሲያገኙት አምጥተው ሕዝቡ መካከል አቆሙት። ሳኦል ከሌሎች ሰዎች ሁሉ ይበልጥ ረጅም ነበር፤ እንዲሁም በጣም ቆንጆ ነበር። ሳሙኤልም ‘ይሖዋ የመረጠው ሰው ይኸውላችሁ’ አላቸው። ሕዝቡም ‘ንጉሡ ለዘላለም ይኑር!’ ብለው ጮኹ።

ንጉሥ ሳኦል መጀመሪያ ላይ ሳሙኤል የሚለውን ይሰማ እንዲሁም ይሖዋን ይታዘዝ ነበር። በኋላ ግን ተለወጠ። በአንድ ወቅት ንጉሥ ሳኦል መሥዋዕት አቅርቦ ነበር፤ ሆኖም እንዲህ ማድረግ አልተፈቀደለትም ነበር። ሳሙኤል እሱ እስኪመጣ ድረስ እንዲጠብቀው ለሳኦል ነግሮት የነበረ ቢሆንም ቶሎ አልመጣም። ስለዚህ ሳኦል ራሱ መሥዋዕቱን ለማቅረብ ወሰነ። በዚህ ጊዜ ሳሙኤል ምን አደረገ? ሳኦልን ‘ይሖዋን መታዘዝ ነበረብህ’ አለው። ታዲያ ሳኦል ከስህተቱ ይማር ይሆን?

ከጊዜ በኋላ ሳኦል ከአማሌቃውያን ጋር ለመዋጋት በሄደ ጊዜ፣ ሳሙኤል ሳኦልን አንድም ሰው ሳያስቀር ሁሉንም እንዲያጠፋ ነግሮት ነበር። ሳኦል ግን ንጉሥ አጋግን ሳይገድለው ቀረ። ይሖዋም ሳሙኤልን ‘ሳኦል እኔን መስማት ትቷል’ አለው። ሳሙኤልም በጣም አዝኖ ሳኦልን ‘ይሖዋን መታዘዝ ስለተውክ ሌላ ንጉሥ ይመርጣል’ አለው። ሳሙኤል ከሳኦል ተለይቶ ሊሄድ ሲል ሳኦል ሳሙኤልን ያዘው፤ በዚህ ጊዜ የሳሙኤል ልብስ ተቀደደ። ከዚያም ሳሙኤል ሳኦልን ‘ይሖዋም መንግሥቱን ልክ እንደዚህ ልብስ ከአንተ ቀዶታል’ አለው። ይሖዋ መንግሥቱን እሱን ለሚወድና ለሚታዘዝ ሰው ለመስጠት ወሰነ።

“መታዘዝ ከመሥዋዕት . . . ይበልጣል።”—1 ሳሙኤል 15:22