በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 42

ዮናታን ደፋርና ታማኝ ነበር

ዮናታን ደፋርና ታማኝ ነበር

የንጉሥ ሳኦል የመጀመሪያ ልጅ የሆነው ዮናታን ደፋር ተዋጊ ነበር። ዳዊት ራሱ ዮናታን ከንስር ይበልጥ ፈጣንና ከአንበሳ ይበልጥ ጠንካራ እንደሆነ ተናግሯል። አንድ ቀን ዮናታን የተወሰኑ ፍልስጤማውያን ወታደሮችን አንድ ተራራ ላይ አየ። ከዚያም አገልጋዩን ‘የምንዋጋው ይሖዋ ምልክት ከሰጠን ብቻ ነው። ፍልስጤማውያኑ ኑና ግጠሙን ካሉን ሄደን እንዋጋለን’ አለው። ፍልስጤማውያኑም ‘ወደ እኛ ኑና እንጋጠም!’ ብለው ጮኹ። ስለዚህ ዮናታንና አገልጋዩ ወደ ተራራው ወጥተው ከፍልስጤማውያኑ ጋር በመዋጋት አሸነፏቸው።

ዮናታን የሳኦል የመጀመሪያ ልጅ በመሆኑ ቀጣዩ ንጉሥ የሚሆነው እሱ ነበር። ሆኖም ዮናታን ቀጣዩ የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን ይሖዋ የመረጠው ዳዊትን እንደሆነ ያውቅ ነበር፤ ቢሆንም በዳዊት አልቀናም። እንዲያውም ዮናታንና ዳዊት የቅርብ ጓደኛሞች ሆኑ። አንዳቸው ሌላውን ለመጠበቅና እርስ በርስ ለመረዳዳት ቃል ገቡ። ዮናታን ዳዊትን በጣም እንደሚወደው ለማሳየት ልብሱን፣ ሰይፉን፣ ቀስቱንና ቀበቶውን ሰጠው።

ዳዊት ከሳኦል እየሸሸ በነበረበት ወቅት ዮናታን ወደ ዳዊት ሄዶ ‘በርታ፤ ደፋር ሁን። ይሖዋ ንጉሥ እንድትሆን መርጦሃል። አባቴም ቢሆን ይህን ያውቃል’ አለው። አንተም እንደ ዮናታን ያለ ጥሩ ጓደኛ ቢኖርህ ደስ አይልህም?

ዮናታን ጓደኛውን ለመርዳት ሲል በተደጋጋሚ ሕይወቱን አደጋ ላይ ጥሏል። ንጉሥ ሳኦል ዳዊትን መግደል እንደሚፈልግ ያውቅ ነበር፤ ስለዚህ አባቱን እንዲህ አለው፦ ‘ዳዊትን ብትገድል ኃጢአት ይሆንብሃል፤ ዳዊት ምንም መጥፎ ነገር አልሠራም።’ በዚህ ጊዜ ሳኦል በዮናታን በጣም ተበሳጨ።

ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ ሳኦልና ዮናታን ጦርነት ላይ ሞቱ። ዮናታን ከሞተ በኋላ ዳዊት የዮናታንን ልጅ ሜፊቦስቴን ፈልጎ ለማግኘት ጥረት አደረገ። ዳዊት ሜፊቦስቴን ካገኘው በኋላ እንዲህ አለው፦ ‘አባትህ በጣም ጥሩ ጓደኛዬ ስለነበር ከአሁን በኋላ እኔ እንከባከብሃለሁ። ቤተ መንግሥቴ ውስጥ ትኖራለህ፤ እንዲሁም ከእኔ ጋር ትበላለህ።’ ዳዊት ጓደኛውን ዮናታንን ፈጽሞ አልረሳውም።

“እኔ እንደወደድኳችሁ እናንተም እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ። ሕይወቱን ለወዳጆቹ ሲል አሳልፎ ከሚሰጥ ሰው የበለጠ ፍቅር ያለው ማንም የለም።”—ዮሐንስ 15:12, 13