በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 52

የይሖዋ የእሳት ፈረሶችና የጦር ሠረገሎች

የይሖዋ የእሳት ፈረሶችና የጦር ሠረገሎች

የሶርያ ንጉሥ ቤንሃዳድ በእስራኤል ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት ይሰነዝር ነበር። ሆኖም ጥቃት በሚሰነዝርበት ጊዜ ሁሉ ነቢዩ ኤልሳዕ የእስራኤልን ንጉሥ አስቀድሞ ያስጠነቅቀው ስለነበር ከጥቃቱ ያመልጥ ነበር። ስለዚህ ቤንሃዳድ ኤልሳዕን ለመያዝ ወሰነ። ኤልሳዕ ዶታን የሚባል ከተማ ውስጥ እንዳለ ስለሰማ እሱን ለመያዝ የሶርያን ሠራዊት ወደዚያ ላከ።

ሶርያውያን ሌሊት ላይ ዶታን ደረሱ። በቀጣዩ ቀን ጠዋት የኤልሳዕ አገልጋይ ወደ ውጭ ሲወጣ ከተማዋ በብዙ ሠራዊት እንደተከበበች አየ። እሱም በጣም ስለፈራ ‘ኤልሳዕ፣ ምን ብናደርግ ይሻላል?’ በማለት ጮኸ። ኤልሳዕም ‘ከእነሱ ጋር ካሉት ከእኛ ጋር ያሉት ይበልጣሉ’ አለው። ወዲያውኑም ይሖዋ የኤልሳዕ አገልጋይ በከተማዋ ዙሪያ ያሉት ተራሮች በሙሉ በእሳት ፈረሶችና የጦር ሠረገሎች እንደተሞሉ እንዲያይ አደረገው።

የሶርያ ወታደሮች ኤልሳዕን ለመያዝ ሲሞክሩ ኤልሳዕ ‘እባክህ ይሖዋ እነዚህን ሰዎች አሳውራቸው’ በማለት ጸለየ። በዚህ ጊዜ ዓይናቸው ማየት ቢችልም እንኳ የት እንዳሉ ግራ ገባቸው። ኤልሳዕ ወታደሮቹን እንዲህ አላቸው፦ ‘የመጣችሁት ወደተሳሳተ ቦታ ነው። ተከተሉኝና ወደምትፈልጉት ሰው እወስዳችኋለሁ።’ እነሱም ኤልሳዕን ተከትለው የእስራኤል ንጉሥ እስከሚኖርባት እስከ ሰማርያ ድረስ ሄዱ።

ሶርያውያኑ የት እንዳሉ የገባቸው ሰማርያ ውስጥ ከገቡ በኋላ ነበር። የእስራኤል ንጉሥም ‘ልግደላቸው?’ በማለት ኤልሳዕን ጠየቀው። ኤልሳዕ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም ሊጎዱት ሞክረው የነበሩትን ሰዎች ይበቀል ይሆን? በፍጹም። ኤልሳዕ እንዲህ አለ፦ ‘አትግደላቸው። የሚበሉት ምግብ ስጣቸውና አሰናብታቸው።’ ስለዚህ ንጉሡ ትልቅ ድግስ አዘጋጅቶላቸው ከበሉና ከጠጡ በኋላ ወደ ቤታቸው ሄዱ።

“በእሱ ላይ ያለን ትምክህት ይህ ነው፤ የምንጠይቀው ነገር ምንም ይሁን ምን ከፈቃዱ ጋር በሚስማማ ሁኔታ እስከለመንን ድረስ ይሰማናል።”—1 ዮሐንስ 5:14