በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 66

ዕዝራ የአምላክን ሕግ አስተማረ

ዕዝራ የአምላክን ሕግ አስተማረ

አብዛኞቹ እስራኤላውያን ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ 70 ዓመት ገደማ ሆኗቸው የነበረ ቢሆንም እንኳ አንዳንዶቹ እዚያው በፋርስ መንግሥት ውስጥ በተለያዩ ከተሞች ተበታትነው ይኖሩ ነበር። ከእነሱም መካከል የይሖዋን ሕግ ያስተምር የነበረው ካህኑ ዕዝራ ይገኝበታል። ዕዝራ በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ሰዎች የአምላክን ሕግ እየታዘዙ እንዳልሆነ ሲሰማ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ እነሱን ለመርዳት አሰበ። የፋርሱ ንጉሥ አርጤክስስ ዕዝራን እንዲህ አለው፦ ‘አምላክ ሕጉን ለማስተማር የሚያስችል ጥበብ ሰጥቶሃል። ወደ ኢየሩሳሌም መሄድ የሚፈልጉ ሰዎችን በሙሉ ይዘህ ሂድ።’ ዕዝራም ወደ ኢየሩሳሌም መመለስ የሚፈልጉ ሰዎችን ሁሉ ሰበሰበ። ይህን ረጅም ጉዞ ሲያደርጉ ከአደጋ እንዲጠብቃቸው ወደ ይሖዋ ጸለዩ፤ ከዚያም ጉዞ ጀመሩ።

ከአራት ወራት በኋላ ኢየሩሳሌም ደረሱ። በዚያ ያሉት መኳንንት ‘እስራኤላውያን የይሖዋን ትእዛዝ ጥሰው የሐሰት አማልክት የሚያመልኩ ሴቶችን አግብተዋል’ በማለት ለዕዝራ ነገሩት። ታዲያ ዕዝራ ምን አደረገ? በሕዝቡ ፊት ተንበርክኮ እንዲህ በማለት ጸለየ፦ ‘ይሖዋ፣ አንተ ለእኛ ብዙ ነገር አድርገህልናል፤ እኛ ግን በአንተ ላይ ኃጢአት ሠርተናል።’ ሕዝቡ ንስሐ ገቡ፤ ሆኖም ትክክል ያልሆነ ነገር ማድረጋቸውን ሙሉ በሙሉ አላቆሙም ነበር። በመሆኑም ዕዝራ ጉዳዩን የሚያጣሩ ሽማግሌዎችና ፈራጆች መረጠ። በቀጣዮቹ ሦስት ወራት ይሖዋን የማያመልኩ ሰዎች በሙሉ ከኢየሩሳሌም እንዲወጡ ተደረገ።

ከአሥራ ሁለት ዓመት በኋላ ዕዝራ የሕጉ መጽሐፍ ሲነበብ እንዲያዳምጡ ሕዝቡን አደባባይ ላይ ሰበሰባቸው። በወቅቱ በኢየሩሳሌም ዙሪያ ያለው አጥር በድጋሚ ተገንብቶ ነበር። ዕዝራ መጽሐፉን ሲከፍት የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተነስተው ቆሙ። ከዚያም ዕዝራ ይሖዋን አመሰገነ፤ ሕዝቡም መስማማታቸውን ለመግለጽ እጃቸውን ወደ ላይ ዘረጉ። ከዚያም ዕዝራ ሕጉን አንብቦ አብራራላቸው፤ እነሱም በትኩረት አዳመጡ። ይሖዋን መታዘዝ ትተው እንደነበረም አመኑ፤ በዚህም ምክንያት አለቀሱ። በቀጣዩም ቀን ዕዝራ ሕጉን ማንበቡን ቀጠለ። ሕዝቡ የሕጉ መጽሐፍ ሲነበብላቸው የዳስ በዓል የሚከበርበት ጊዜ እንደተቃረበ ተገነዘቡ። ወዲያውኑም ለበዓሉ መዘጋጀት ጀመሩ።

ከዚያም ሕዝቡ በዓሉን ለሰባት ቀን በደስታ አከበሩ፤ እንዲሁም ብዙ እህል ማምረት በመቻላቸው ይሖዋን አመሰገኑ። ከኢያሱ ዘመን ጀምሮ እስከዚያ ቀን ድረስ የዳስ በዓል በዚህ መንገድ ተከብሮ አያውቅም ነበር። ከበዓሉ በኋላ ሕዝቡ ተሰብስበው እንዲህ በማለት ጸለዩ፦ ‘ይሖዋ፣ ከባርነት ነፃ አውጥተኸናል፤ በበረሃ መግበኸናል፤ እንዲሁም ይህን የሚያምር መሬት ሰጥተኸናል። እኛ ግን በተደጋጋሚ ዓመፅንብህ። የሚያስጠነቅቁን ነቢያት ልከህልናል፤ እኛ ግን አልሰማናቸውም። ያም ሆኖ በትዕግሥት ይዘኸናል። ለአብርሃም የገባኸውን ቃል ጠብቀሃል። እንግዲህ እኛም አንተን ለመታዘዝ ቃል እንገባለን።’ ከዚያም የገቡትን ቃል ጻፉት፤ መኳንንቱ፣ ሌዋውያኑና ካህናቱም ማኅተማቸውን አደረጉበት።

“ደስተኞችስ የአምላክን ቃል ሰምተው የሚጠብቁት ናቸው!”—ሉቃስ 11:28