በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 67

የኢየሩሳሌም ግንብ

የኢየሩሳሌም ግንብ

ዕዝራ በኖረበት ዘመን የንጉሥ አርጤክስስ አገልጋይ የሆነ ነህምያ የሚባል አንድ እስራኤላዊ ነበር። ነህምያ የፋርስ ከተማ በሆነችው በሹሻን ይኖር ነበር። የነህምያ ወንድም ከይሁዳ መጥቶ ይህን አሳዛኝ ወሬ ነገረው፦ ‘ወደ ኢየሩሳሌም የተመለሱት ሰዎች ያሉበት ሁኔታ በጣም አሳሳቢ ነው። ባቢሎናውያን ያፈራረሷቸው የኢየሩሳሌም ግንቦችና በሮች እስካሁን አልተገነቡም።’ ነህምያ ይህን ሲሰማ በጣም አዘነ። የኢየሩሳሌምን አጥር ለመሥራት ወደዚያ መሄድ ፈለገ፤ ስለዚህ ወደ ኢየሩሳሌም እንዲሄድ ንጉሡ እንዲፈቅድለት ወደ ይሖዋ ጸለየ።

ንጉሡም ነህምያ እንዳዘነ አስተዋለ። በመሆኑም እንዲህ አለው፦ ‘እንደዚህ አዝነህ አይቼህ አላውቅም። ምን ሆነህ ነው?’ ነህምያም ‘ኢየሩሳሌም እንዲህ ፈራርሳ እያለ እንዴት አላዝንም?’ በማለት መለሰ። ንጉሡም ‘ምን እንዳደርግልህ ትፈልጋለህ?’ በማለት ጠየቀው። በዚህ ጊዜ ነህምያ ወዲያውኑ በልቡ ጸለየ። ከዚያም ‘እባክህ ወደ ኢየሩሳሌም ሄጄ አጥሩን መልሼ እንድገነባ ፍቀድልኝ’ በማለት ጠየቀ። ንጉሥ አርጤክስስ፣ ነህምያ እንዲሄድ ፈቀደለት፤ ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም በሚጓዝበት ወቅት አደጋ እንዳይደርስበት የጦር አለቆችና ፈረሰኞች አብረውት እንዲሄዱ አደረገ። በተጨማሪም ነህምያን የይሁዳ ገዢ አድርጎ ሾመው፤ የከተማዋን በሮች ለመሥራት የሚሆን እንጨትም ሰጠው።

ነህምያ ኢየሩሳሌም እንደደረሰ የከተማዋን አጥር ተዘዋውሮ ተመለከተ። ከዚያም ካህናቱንና ገዢዎቹን ሰብስቦ እንዲህ አላቸው፦ ‘ከተማዋ ያለችበት ሁኔታ በጣም የሚያሳዝን ነው። አሁኑኑ ሥራ መጀመር አለብን።’ ሕዝቡም በሐሳቡ ተስማሙ፤ አጥሩንም መልሰው መገንባት ጀመሩ።

ሆኖም የእስራኤላውያን ጠላቶች የሆኑ አንዳንድ ሰዎች ‘የምትሠሩት አጥር እኮ ቀበሮ እንኳ ቢወጣበት ይፈርሳል’ እያሉ ያሾፉባቸው ነበር። ሠራተኞቹ ግን የእነሱን ፌዝና ቀልድ ችላ ብለው አጥሩን አጠናክረው መገንባታቸውን ቀጠሉ። ግንቡም እየረዘመ ሄደ።

የእስራኤላውያን ጠላቶች ከተለያየ አቅጣጫ መጥተው በኢየሩሳሌም ላይ ድንገተኛ ጥቃት ለመሰንዘር አሰቡ። አይሁዳውያን ይህን ሲሰሙ በጣም ፈሩ። ነህምያ ግን ‘አትፍሩ። ይሖዋ ከእኛ ጋር ነው’ አላቸው። ከዚያም ሠራተኞቹን የሚጠብቁ ሰዎችን መደበ፤ ጠላቶቻቸውም ሊያጠቋቸው አልቻሉም።

የከተማዋ አጥርና በሮች በ52 ቀናት ውስጥ ተሠርተው ተጠናቀቁ። ነህምያም በምርቃቱ ላይ እንዲገኙ ሌዋውያኑን በሙሉ በኢየሩሳሌም ሰበሰበ። ከዚያም በሁለት የዘማሪዎች ቡድን ከፋፈላቸው። እነሱም በደረጃ ግንቡ ላይ ወጡና አንደኛው ቡድን በአንድ አቅጣጫ ሌላኛው ቡድን ደግሞ በተቃራኒ አቅጣጫ ከተማዋን ዞሩ። በመለከት፣ በሲምባልና በበገና ታጅበው ለይሖዋ ዘመሩ። ዕዝራ ከአንዱ ቡድን ጋር ሄደ፤ ነህምያ ደግሞ ከሌላኛው ቡድን ጋር ሄደ፤ በኋላም ሁለቱ ቡድኖች ቤተ መቅደሱ ጋ ተገናኙ። ወንዶችን፣ ሴቶችንና ልጆችን ጨምሮ ሕዝቡ በሙሉ ለይሖዋ መሥዋዕት አቀረቡ። በጣም ተደስተው ስለነበር ድምፃቸው ከሩቅ ይሰማ ነበር።

“አንቺን ለማጥቃት የተሠራ ማንኛውም መሣሪያ ይከሽፋል።”—ኢሳይያስ 54:17